Pages

Saturday, December 17, 2011

ጨርቆስና ቦሌ - ሕይወትን እኛ እንደኖርነው!


ጨርቆስና ቦሌን ምን አገናኛቸው? በርግጥ ለዚህ ጥያቄ መልሱ ቀላል ነው፡፡ ምክንያቱም ጨርቆስና ቦሌ ተለያይተው አያውቁም - በቀልድም በድንበርም፡፡ በኑሮ መቀለድ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የኑሮአችን አካል ነው፡፡ የጨርቆስ እና የቦሌ ጉርብትናም በኢትዮጵያ እየሰፋ ለመጣው የኑሮ ደረጃ ልዩነት በርካታ አዳዲስ ቀልዶችን አበርክቷል፡፡ ምንም እንኳን የጫወታዬ ዓላማ ቀልዶቹን ለአደባባይ ማብቃት ባይሆንም አንድ ስሜቴን የነካ ቀልድ ግን ሳላስታውስ ማለፍ አይቻለኝም፡፡ ቀልዱ የተነገረው ወንድማማቾቹ የኢትዮጵያና የኤርትራ ወታደሮች ጦርነት ላይ በነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡ መንግስታችን በወቅቱ ‹‹ፈንጂ ማክሸፊያ›› ወጣቶች ያስፈልጉት ነበርና‹ወዶ ዘማች› የሚለው ቃል ወረት ሆኖ ነበር፡፡ እናም የሃገራቸው መወረር ያስቆጣቸው የቦሌ ልጆች ገንዘብ አዋጥተው ለጨርቆስ ሰፈር ‹ወዶ ዘማቾች› ደሞዝ እንዲከፈል አበረከቱ ተብሎ ተቀለደ፡፡

ከዚህ ቀልድ በኋላ ግን አንድ ጥያቄ በጭንቅላቴ ሲጉላላ ከረመ፡፡ ‹‹የሃብታምና የድሃ ሕይወት የዋጋ ልዩነት ስንት ነው?››

Saturday, December 3, 2011

የዳዊት ከበደ እና የተመስገን ደሳለኝ ወጎች

From Addis Ababa, Ethiopia

“Every newspaper that's rented instead of being sold is a further challenge for those few trying to survive in the tough Ethiopian media environment,” ይህን የተናገረው የአውራምባ ታይምሱ ዳዊት ከበደ ለሲኤንኤን ነበር፡፡ በአዲስ አበባ የጋዜጣ ኪራይን በተመለከተ ነበር፤ የጋዜጣ ኪራይ በአዲስ አበባ ቀድሞ ለታመመው የግሉ ሚዲያ ተጨማሪ ተግዳሮት መሆኑን ሲገልፅ፡፡ (የጋዜጣ ‹‹ኪራይ ሰብሳቢዎችን›› ዳዊት እንዴት እንደማይወዳቸው ይታያችሁ! እኔ ግን አታስዋሹኝ እወዳቸዋለሁ፡፡ እስኪ አስቡት ሳምንት ሙሉ የሚታተሙትን ጋዜጦች እየገዛሁ ባነብ ደሞዜ ይበቃኛል? ጋዜጣ በልቼ፣ በጋዜጣ ተሳፍሬ፣ በጋዜጣ የቤት ኪራይ ከፍዬ፣ በጋዜጣ ሁሉን ነገር አድርጌ መኖር ይቻለኛል?)

ዳዊት ከበደ አሁን ዋሽንግተን፣ አሜሪካ ነው ያለው፡፡ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ መንግስት ዕድሜ ልክ ተፈርዶበት ‹‹በይቅርታ›› መፈታቱ ይታወሳል፡፡ እንግዴህ ያ ‹‹ይቅርታ›› እንደሰኞ ሊሰረዝ እሱ ቅዳሜ ወደአሜሪካ በርሯል፡፡ ይመስለኛል፤ ዳዊት ይቅርታው እንደሚሰረዝ ከመስማቱ በፊት ገምቶ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአሜሪካ ቪዛ የማግኘቱ ጉዳይ ቀላል ባለመሆኑ ቀድሞ መጀመርን ይጠይቃልና እሱም ይህንኑ ቀድሞ ማሳካት ችሎ ነበር ማለት ነው፡፡

Saturday, November 26, 2011

“ኢትዮጵያውያን፣ ኢትዮጵያ እያለች ሃገር የላቸውም”


“በዓለም አንደኛ ነው፤” በሚል በገዛ ጓደኞቼ ተጠቁሜ፣ ሲኒማ ኢትዮጵያ ገብቼ ያየሁት “ዘመቻ ድንግልን ፍለጋ” የተሰኘ ፊልም አንደኝነቱን ለደረጃ አጣሪ ኮሚቴ ሰጥቼና እምባዬን ወደሰማይ ረጭቼ ከውስጡ ያገኘሁትን ዓረፍተ ነገር ለወጌ ርዕስነት መርጬዋለሁ፡፡ ዓረፍተ ነገሩ “7ተኛው ሰው” የተባለ ሌላ “በዓለም አንደኛ” ፊልም አስታወሰኝ፡፡ ሰባተኛው ሰው ወደአሜሪካ ለዎርክሾፕ ከሄዱት ሰባት ሰዎች መካከል ወደሃገሩ ተመልሶ የመጣው እና በፊልሙ ዓለም ውስጥ በነበሩ ምሁራን፣ ተቃዋሚ እና ገዢ ፖለቲከኞች ብሎም በቤተሰቦቹ ሳይቀር የመገለል ዕጣ የደረሰበት ነበር፡፡ ለምን ተመለስክ በሚል፡፡

እዚህ ፊልም ላይ የታየው ታሪክ እንዳልተጋነነ ለማወቅ ከፈለጋችሁ አንድ የእውነተኛ ታሪክ ልጨምርላችሁ፡፡ ፋንታሁን ሸዋንቆጨኝ በብሔራዊ ቲያትር አንጋፋ ድምፃዊ ነበር፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በባለሙያዎች የተወደሰ አልበም አውጥቶ ብዙም አድማጭ አላገኘም ነበር፡፡ በርግጥ ዜማዎቹ ለአሸሸ ገዳሜ የማይመቹ ስለሆኑ፣ የዘመኑን መስፈርት አያሟሉም ነበር፡፡ ብዙዎቻችሁ ከጂጂ ጋር በማሲንቆ ያዜማቸውን እና ከሸገር ሬዲዮ በቀር በሌላ ሬዲዮ ጣቢያ እምብዛም በማይደመጡት ዜማዎቹ ታውቁታላችሁ፡፡ ስለርሱ ነው የምነግራችሁ፡፡

Tuesday, November 22, 2011

የኢሕአዴግ ‹‹ትርፍ›› እና ኪሳራ


ኢሕአዴግን ፀሃዩ መንግስት እያለ በሽሙጥ የሚያንቆለጳጵሰው አበበ ቶላ በካድሬዎች ሽንቆጣ ብዛት ኮበለለ፣ የአውራምባ ታይምስ ማኔጂንግ ኤዲተርና የ2010 CPJ ፕሬስ ነፃነት ተሸላሚው ዳዊት ከበደም እያሻቀበ በመጣበት ትንኮሳና (እንደራሱ ገለፃ ‹‹ማክሰኞ፤ ሕዳር 12፤ 2004›› ሊታሰር ስለነበር) ወደ ሃገረ አሜሪካ እግሬ አውጪኝ አለ፡፡ የምንወዳቸው፣ ጽሁፎቻቸውን የምንናፍቅላቸው ጋዜጠኞች በሙሉ ከፊሎቹ ተሰደዱ፣ ከፊሎቹ አቋማቸውን አለዘቡ፣ ከፊሎቹ ብዕራቸውን ሰቀሉ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ታሰሩ፡፡ ‹‹ሂስ ቀረበብን ብለው ሃገር ጥለው ፈረጠጡ›› በሚል በጠቅላይ ሚኒስቴሩ የተተቹት እነ ዐቢይ ተክለማርያም እና መስፍን ነጋሽ በአሸባሪነት በሌሉበት በተከሰሱበት በዚህ ቀውጢ ሰዓት የሃገራችን የፕሬስ ነጻነት በአስተማማኝ ሁኔታ ላይ እንዳለ አቶ በረከት ስምዖንን፣ ሚሚ ስብሃቱን፣ ሳምሶን ማሞን ወይም የኢቴቪ ሚዲያ ዳሰሳ አዘጋጆችን ጠይቆ መረዳት ይቻላል፡፡

በተቃራኒው WorldPress Freedom Index 2010 የኢትዮጵያን የፕሬስ ነፃነት ‹‹አስቸጋሪ ሁኔታ›› (ለመጨረሻ ሩብ ጉዳይ) ላይ እንዳለ ይነግረናል፡፡ የ2011 ውጤት ሲታወቅ ደግሞ ‹‹በጣም አሳሳቢ ደረጃ ላይ›› (የመጨረሻ ደረጃ ላይ) ነው ብሎ እንደሚፈርጀው መገመት አይከብድም፡፡ በFreedom of the Press Global Status ላይ ደግሞ ኢትዮጵያ ‹‹ነፃ ያልሆነች›› ተብላለች፡፡ ጋዜጠኞችንም በማሰር ቢሆን ኢትዮጵያን ከኤርትራ በቀር የሚበልጣት እንደሌለ chartsbin.com በዝርዝር ያስነብበናል፡፡ እኛ ማንን እንመን? በመንግስት ቲፎዞነታቸው የምናውቃቸውን እኒያን ግለሰቦች ወይስ በጥናት ላይ ተመርኩዘው የሚነግሩንን እኒህ ኃላፊነት የሚሰማቸውን ድርጅቶች? ግዴለም የምናየውን እንመን፤ የታሰሩትንና እየተሰደዱ ያሉትን ጋዜጠኞች አይተን እንፍረድ፡፡

Thursday, November 10, 2011

“Every nation deserves its government” - ኦቶ ቮን ቢስማርክ

ሠላም ሰፍኗል፡፡ ሠላም የሚያሰፍን ግን አንዳችም ነገር የለም፡፡ የኑሮ ዋጋ ከሕይወት ዋጋ በልጧል፣ በቂ ቀርቶ ግማሽ ነፃነት የለም፤ ሕዝቡ ግን አይበሳጭም ወይም ብስጭቱን አፍኖ ተቀምጧል፡፡ ‹‹የባሰ አታምጣ›› እያለ የምድራዊውን ገዢ በደል ‹‹በሰማያዊው›› ላይ ያሳብባል (‹‹የቄሳርን ለቄሳር›› መባሉ ተዘንግቷል!) - የኢትዮጵያ ሕዝብ የኢሕአዴግን መንግስት እንደሚጠላው እና እንደተማረረበት ቢታወቅም - ‹በቃኸኝ› ሊለው ግን አልፈለገም ወይም አልደፈረም፡፡

ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ ኢትዮጵያውያን ለአብዮት የሚያበቃ ብስጭት ላይ ደርሰዋል? ባሉት ጽሁፋቸው ላይ ‹‹ሕዝባዊ አመጽ በኢትዮጵያ የመነሳት ዕድሉ በብዙሐኑ ስነልቦናዊ ዝግጅት ላይ የተመረኮዘ ነው›› በማለት የስነልቡናው ዝግጅት አናሳ በመሆኑ በኢትዮጵያ ሕዝባዊ አመጽ፣ በቅርቡ ይቀሰቀሳል ብሎ መጠበቅ እንደማያዋጣ አመልክተዋል፡፡

ሕዝባዊ አመጽ ያስጠላል፡፡ ሁሉም ሰው በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት ይወዳል፡፡ ነገር ግን ከጊዜያዊ ሰላም ይልቅ ዘላቂ ለውጥ ይበልጥ አስፈላጊ ነው፡፡ የማንበላ መብላት፣ የታረዝን መልበስ፣ የታሰርን መፈታት ያምረናል፡፡ እንዳምና ካቻምናው ሁሉ ከመሰረታዊ ፍላጎቶቻችን ጋር ተጣብቀነ በምግብ ራስን ስለመቻል እና የነፃነት አየር ስለመተንፈስ ማውራት ያሰለቻል፤ እንደሌሎች ሃገራት ስለዓለም ዓቀፍ ገበያ፣ ስለኅዋ ሳይንስ እና ስለሁለተኛ ፍላጎቶቻችን የማውራት ወግ ያምረናል፡፡ አምሮታችንን ለመወጣት ደግሞ እንቅፋት ከፊት ለፊታችን ተደቅኖ ይታየናል - ለውጡ ባይመጣስ ብለን እንፈራለን ወይም ደግሞ የለውጥ ሒደቱን ከወዲሁ ስናስበው ይደክመናል፡፡

Monday, November 7, 2011

In T1me - ጊዜ ገንዘብ (ገንዘብ ጊዜ) ቢሆን ኖሮ!

From Addis Ababa, Ethiopia
“Occupy Wall Street” በሚል መፈክር አንድ በመቶ የሚሆኑ ባለፀጎች የሚመሩትን የኢኮኖሚ ፖለቲካ 99 በመቶዎቹ ሊንዱት እየተፍጨረጨሩ ባለበት በዚህ ቀውጢ ሰዓት፣ In Time የተሰኘ ፊልም ወጥቷል፡፡ ፊልሙ ጊዜን መገበያያ ገንዘብ አድርጎ አምጥቶታል፡፡ መገበያያ ብቻ ግን አይደለም፤ ሕይወትም ጭምር ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ያለው ሰው ሃብታም፣ ትንሽ ጊዜ ያለው ሰው ደግሞ ድሃ ነው፡፡ ድሃው ቶሎ ይሞታል፣ ሃብታሙ ግን ዘላለም የመኖርም ዕድል አለው - በስህተት ካልሞተ፡፡

የፊልሙ ዓለም ውስጥ ያሉ ሰዎች ሃብታቸውና ሕይወታቸው (ጊዜ) እጃቸው ላይ ታትሞ/በተፈጥሮ መሆኑ ነው/ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ማኪያቶ ለመጠጣት 5 ደቂቃ ሲከፍሉ፣ መኪና ለመግዛት ደግሞ ዓመታትን ያወጣሉ፡፡ ስጦታ ይሰጣጣሉ፣ ይሰራረቃሉ፣ ያተርፋሉ ይከስራሉ፡፡ ብዙዎቹ ድሆች ከሰዓታት የበለጠ ስለሌላቸው ሕይወታቸውን ለማሳደር ሲሉ ይዋከባሉ፡፡ ሃብታሞቹ ደግሞ ከእጃቸው ተርፎ ማዕከላዊ ቁጥጥር ሲስተም ውስጥ የሚያጠራቅሙት ዓመታት አላቸው፡፡

በፊልሙ ውስጥ ፖሊስ - ጊዜ ጠባቂ፣ ድንበር - የጊዜ ዞን፣ ባንክ - የጊዜ ማበደሪያ በመባል ይታወቃል፡፡

In Time ሊያስተላልፍ የሞከረው ነገር ሃብታሞች ብዙ ገንዘብ ባካበቱ ቁጥር የሚያካብቱት ከድሃው የተቆነጣጠረ መሆኑን ነው፡፡ ገንዘብ ዕድሜን ቢቀጥል ኖሮ (በርግጥም ይቀጥላል) እነርሱ እየኖሩ ድሃው ይሞታል እንደማለትም ነው፡፡ የፊልሙ ዋና ገፀ ባሕርይ (ጀስቲን ቲምበርሌክ ይተውነዋል) ጊዜን ከሃብታሞቹ እየዘረፈ ለድሆቹ ሲያከፋፍል ይታያል፡፡ ነገርዬው ሶሺያሊዝም ይመስላል፡፡ ዘመናችን ሶሺያሊዝምን እየናፈቀ ይሆን የሚል ጥያቄ መጣብኝ፡፡ ነፃ ገበያ ብሎ ነገር አበቃለት ይሆን?

Friday, November 4, 2011

ኢትዮጵያ ከኢሕአዴግ በኋላ፤ ሰጥቶ የመንጠቅ ዘመነ መንግስት

From Addis Ababa, Ethiopia
በርግጥ ይሄ የአገሪቱ ቅርጽም ኢሕአዴግ አመጣሽ ነው:: 
ስጦታ ወይስ ንፍገት የሚለውን ግን እናንተው ፍረዱ::
ኢሕአዴግ (ሕወሓት) ከአሸባሪነት ወደ አሸባሪ ሰያሚነት በተሸጋገረባቸው ሃያ ዓመታት ውስጥ ብዙ ተግባራትን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ ተግባራቱ፤ ገሚሱ ለፓርቲው ሕልውና፣ ጥቂቱ ለአገሪቱ ሕልውና (ፓርቲው ያለርሷ አይኖርምና)፣ ቀሪው ደግሞ እንዲሁ ማድረግ ደስ ሲለው ያደረጋቸው ነገሮች ናቸው፡፡ አሁን የምጽፈውም ለኢትዮጵያ የትኞቹ ፌሽታ፣ የትኞቹ መዐት ይዘው መጡ የሚለውን ለማስታወስ ያክል ብቻ ሳይሆን የኢሕአዴግ ስጦታ ውሃ በወንፊት መሆኑን የታዘብኩ ስለመሰለኝ ነው፡፡

ስጦታ
በ20 ዓመታት ውስጥ የመንግስት ኃላፊነትን (በጉልበቱም ቢሆን) ከወሰደ በኋላ አንዳንድ ለውጦችን አምጥቷል፡፡ ሆኖም የመጡትን ለውጦች ካየናቸው አብዛኛዎቹ የተፈፀሙት በመጀመሪያው አምስት ዓመታት ብቻ መሆኑ ያስገርመናል፡፡ ሆኖም እዚህ ስጦታ እያልኩ የምዘረዝራቸውን ነገሮች ሁሉ መልሶ እንዴት እንደሚወስዳቸው ወረድ ብለን፤ በሌላ ንዑስ ርዕስ እንመለከተዋለን፡፡

Friday, October 28, 2011

“ይህ - የታገልንለትን ጉዳይ አለማወቅ ነው”

From Addis Ababa, Ethiopia
ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያም በአንድ ወቅት በፈፀሙት ድርጊት ተፀፅተው ይቅርታ ይጠይቁ እንደሁ በገነት ‹ማስታወሻ› ላይ ሲጠየቁ ‹‹ማንን ነው ይቅርታ የምጠይቀው? ወያኔን? ወያኔ እኔን ይቅርታ ጠይቆኛል?...ይህ የታገልንለትን ጉዳይ አለማወቅ ነው›› በማለት ጥያቄውን በጥያቄ መልሰዋል፡፡ መንግስቱ በአስተዳደራቸው ማክተሚያ ሰሞንም፣ በመንግስት መገናኛ ብዙሐን እንዲህ ብለው ነበር፡፡ ‹‹ለአገሬና ለወገኔ ይበጃል ብዬ ባደረግኩትና በተሳተፍኩባቸው ተግባሮች ሁሉ በግሌ ሕሊናዬን የሚወቅሰኝ ነገር የለም›› ብለዋል፡፡

‹‹መ››ንግስቱ እና ‹‹መ››ለስ
መለስ በመንግስቱ ቆብ ውስጥ ገብተው ይሆን?

በመጀመሪያ የስልጣን ዘመናቸው ዲሞክራት  መስለውን ነበር::
እኛን ብቻ ሳይሆን ምዕራባውያንንም በዚህ ሸውደዋቸዋል::
ምዕራብውያን ታዛዥነታቸውን ስለሚወዱላቸው ብቻ ተቀብለዋቸዋል::
የመለስ ታዛዥነት ለውጭ ኃይሎች ብቻ እንጂ ለአገራቸው ሕዝብ
አይደለም::  መለስ በውጭ ዲፕሎማሲ ጎበዝ የሚመስሉዋችሁ ከሆነ -
አይደሉም:: ሊደራደሩበት የሄዱትን ጉዳይ አሳልፈው በመስጠት
መስማማትን ይመርጣሉ::  ውጪያዊ ተቃውሞ የማይደመጥባቸውም
ለዚያ ነው::

በዴሞክራሲ ጉዳይ "ሙጋቤ የሚለው አፍሪካውያን የምዕራባውያን
ዓይነት ዴሞክራሲ  አያስፈልጋቸውም::" ብሎ ነው ብለው መለስ
ከጋዜጠኛ ጋር ከተሟገቱ በኋላ የዴሞክራሲ  በኢትዮጵያ ተስፋው
ተመናምኗል:: ሙጋቤ  መንግስቱን አስጠልለዋል - አሁን ደግሞ
መለስም  የርሳቸውን የዴሞክራሲ ቲዎሪ እየዘመሩ ነው::
መንግስቱና መለስ እያደር የሚያመሳስላቸው ነገር ተበራክቷል፡፡ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ነጋሶ ጊዳዳ ‹‹የነጋሶ መንገድ›› በተሰኘው ግለታሪካቸው እንደነገሩን የሕወሓት ተገንጣይ ቡድን ተሸንፎ ሲወጣ የነመለስ ቡድን (በተለይ አቶ መለስ) ‹‹ጃኬታቸውን አስወልቀን ሸኘናቸው›› እያሉ ሲፎክሩ ነጋሶ መለስን ‹‹መንግስቱን፣ መንግስቱን መሰልከኝ›› ብለዋቸዋል፡፡ እውነት ነው፤ (መ)ንግስቱና (መ)ለስ (መ)ንትያ ናቸው፡፡ እስኪ በዝርዝር እንመልከተው…

Tuesday, October 25, 2011

“አሰብ የማን ናት?”ን በጨረፍታ

From Addis Ababa, Ethiopia

በ260 ገጾች ተቀንብቦ የተጻፈው የዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም ‹‹አሰብ የማን ናት?›› ዶ/ሩን የሚያስመሰግን፣ ኢትዮጵያውያንን የሚያነቃቃ ነው፡፡ መጽሃፉን እያነበብኩ እያለሁ ይሰማኝ የነበረው ስሜት በመዳን ላይ ያለ ቁስል ዳርዳሩን ሲያኩት የሚሰጠውን ዓይነት ስሜት ነበር፡፡ (የምታውቁት ካላችሁ)

የመጽሃፉ መግቢያ፣ የመጀመሪያው አንቀጽ ‹‹ኢትዮጵያውያን በተለያዩ የታሪክ ወቅቶች በአገር ውስጥ ብቅ ያሉ አምባገነን መሪዎች የጫኑባቸውን በደሎች ሰው ሰራሽም ሆኑ ተፈጥሮ የወለደቻቸውን ችግሮች በትዕግስት ያስተናገዱ ሲሆን፤ ኢትዮጵያውያን በትዕግሰት የማይመለከቱት ነገር ቢኖር የድንበር መደፈርን ነው ማለት ይቻላል፡፡›› ይላል፡፡

የመጽሃፉ ዓላማ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አሰብ የኢትዮጵያ መሆኗን አውቆ የባሕር በራችንን ማስመለስ ብሔራዊ ግዴታችን እንደሆነ ለማስታወስ መጣር መሆኑም በመግቢያው ላይ ተገልጧል፡፡

Thursday, October 20, 2011

“ደረሰኝ ሳይቀበሉ፥ ሒሳብ አይክፈሉ”

ሰሞኑን ጉምሩክ ከሚሰሩ ሰዎች የሰማሁት ዜና የተለመደ ዓይነት ቢሆንም፥ እንደተለመደው ከመገረም አልዳንኩም፡፡ ጉምሩክ የላካቸው አሥር ጥንዶች አሥር ስጋ ቤቶች ውስጥ ገብተው ቁርጥ እና ጥብሳቸውን ከበሉ በኋላ ከአሥሩ ስጋ ነጋዴዎች አንዱ ብቻ ደረሰኝ ሲያቀርብ ቀሪዎቹ ዘጠኙ ያለደረሰኝ ሒሳብ በመቀበል ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ስታትስቲክስ ውሸታም ነው ቢባልም፣ በዚህ ስሌት እኮ 90 በመቶ የሚሆኑት የሥጋ ነጋዴዎች ታክስ ያጭበረብራሉ ማለት ነው፡፡

ይህንን ዜና ስትሰሙ ለማን አዘናችሁ፣ ወይም በማን አዘናችሁ? ነጋዴዎቹ ምነው ቀድመው መረጃ ቢያገኙ ወይም ምን ዓይነት መንግስት ነው ያለው ብላችሁ ከተማረራችሁ፥ ለፍርድ የቸኮላችሁ ይመስለኛል፡፡ ነጋዴዎቹስ ቢሆኑ ለሕጉ ለምን አይገዙም?

በኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ያልተመለሱ ሕዝባዊና መንግስታዊ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ሁሉም በእኩል ደረጃ አሳሳቢዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ችግሮች ውስጥ አንዱ የሕግ የበላይነት ጉዳይ ነው፡፡ እኔ እንደማስበው በሕግ የበላይነት ጉዳይ ሁላችንም እንስማማለን፡፡ ልዩነታችን በአተገባበሩ ላይ ነው፡፡ ሌላው በዚሁ ማዕቀፍ ውስጥ ያለው ጥያቄ የሕግ የበላይነት ከማን የሚለው ነው - ከሕዝቡ፣ ከመንግስት ወይስ ከሁለቱም?

Tuesday, October 11, 2011

ኢትዮጵያውያን ለምን ዲቪ አይሞሉ?

From Addis Ababa, Ethiopia
ባለፈው ዓመት በዚህ ሰሞን ዲቪ ለኢትዮጵያውያን ስሞታ ይስ ስጦታ? የሚል መጣጥፍ ጽፌ ነበር፡፡ በዚያ ጽሁፍ ብዙ ወጣት ኢትዮጵያውያን ልባቸው ከሃገራቸው ውጪ ነው በማለት በማሕበረሰቡ የቁም ቅዠት፣ በአገሪቱ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁኔታ ፈርጄ ‹‹ኢትዮጵያውያንን እንደበረሃ አሸዋ ከተበተኑበት የሚሰበስባቸው ማን/ምን ይሆን?›› የሚል ጥያቄ አስፍሬ ነበር የደመደምኩት፡፡

የስደት እና የዲቪ ጉዳይ ዛሬም ስላላባራ (በቅርቡ የሚያቧራም ስለማይመስል) በዚህ ሐሳብ ዙሪያ አሁንም እንድጽፍ የሚጎተጉተኝ ስሜት አላጣሁም፡፡ በዚያኛው ጽሁፍ ኢትዮጵያውያን ለምን ይሰደዳሉ ብልም ከዓመት በኋላ ተገቢ ሁኖ ያገኘሁት ጥያቄ ግን ‘ለምን አይሰደዱ?’ የሚለውን ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን ለምን ይሰደዳሉ ለሚለው ጥያቄ በርካታ መልሶችን በቀላሉ ማግኘት ይቻላል፡፡ ዋና፣ ዋናዎቹ ምክንያቶች ኢኮኖሚያዊ ቀውስ፣ ፖለቲካዊ ነፃነት ማጣትና የተሻለ ትምህርት ፍለጋ ናቸው፡፡ ከተማሩ በኋላ መመለስ ልምድ ባይሆንም፡፡ (አወይ የዋህነት! ከተማሩ በኋላ መመለስ ቀርቶ፤ ለሴሚናር፣ ለዎርክሾፕ፣ ለዘገባ ወይም ለጉብኝት ሄዶ መመለስስ የታለና?!)

Friday, October 7, 2011

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና አንዳንድ አካላት

From አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

የዕድገትና የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ አንድ ዓመቱን ጨርሷል፡፡ ኢትዮጵያ እንደተጠበቀው በዓመት ከ11 እስከ 15 በመቶ የማደግ ሕልሟን አሳካች ወይስ ችግር አለ? በቅርቡ የምንሰማው ይሆናል፡፡ በርግጥ ‹‹ከዕቅዱ በታች ፈፅሞ የማያውቀው መንግስታችን›› ዘንድሮም የሁለት ዲጂት እንደሚያስመዘግብ መጠራጠር ከአሸባሪነት ያልተናነሰ ሃጢያት ነው የሚሆነው፡፡

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና UNECA
ስለትራንስፎርሜሽኑ የመጀመሪያ የስኬት ዓመት ከሰሞኑ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀብድ ቢጤ መስጠት ጀማምሯል፡፡ ሰሞኑን የምዕራባውያን ኢኮኖሚ እየፈረሰ ለቻይናዎች እጁን መስጠቱን የሚያትት ወሬ ካወሩልን በኋላ እንደ UNECA የአገሪቱ ዳይሬክተር ከሆነ ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት 10 በመቶ ታድጋለች፡፡ የUNECA ባለስልጣን እንዲህ ለማለት ከደፈሩ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንማ ኢትዮጵያን በሦስት ዲጂትም ሊያሳድጋት ይችላል የሚል ሐሳብ ያዘኝና ተውኩት፤ ምክንያቱም UNECA የሚጠቀምበት መረጃ ለካስ ከኢትዮጵያ መንግስት የተገኘ ነው፡፡

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና መለስ ዜናዊ

Friday, September 30, 2011

የአፋልጉኝ ማስታወቂያ ለተቃዋሚዎች


መጀመሪያ ጭብጨባ

አንድነት ፓርቲ በቅርቡ ተቃዋሚዎች/የተቃዋሚ ደጋፊዎች በቂ የመረጃ ምንጭ የላቸውም በማለት በየሣምንቱ ማክሰኞ፣ በ5 ብር ገበያ ላይ የምትውል ‹‹ፍኖተ ነፃነት›› የተሰኘች ጋዜጣ ማሳተም ጀምሯል፡፡ አንዱአለም አራጌ ሲናገር እንደሰማሁት ‹‹በጋዜጣዋ ላይ የኢሕአዴግ ደጋፊና አባላትም ቢሆኑ መጻፍ ይፈቀድላቸዋል፤ አንድነት እንደ ኢሕአዴግ የመናገር ነፃነትን የማፈን ፍላጎት የለውም፡፡››

ከዚህ በተጨማሪም ፓርቲው በየሣምንቱ እሁድ ማለዳ በተጋባዥ ምሁራን ጽሁፍ አቅራቢነትና በተሳታፊዎች መካከል የሚካሔድ የውይይት ፕሮግራም ጀምሮ ነበር፡፡ (የእነ አቶ አንዱአለም በ‹‹አሸባሪነት›› ተጠርጥሮ መታሰር ይህንን ጠቃሚ ልምድ እስከወዲያኛው ያስቀረው ይሆን?)

በሌላ በኩል (የኔ favorite ባይሆንም እንኳን) ኢዴፓ የዓለም ሊበራል ፓርቲዎችን ጉባኤ በ2004ዓ.ም. በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ሊያካሒድ ጎንበስ ቀና እያለ መሆኑ የሚያስመሰግን ነው፡፡ እንዲህ ሰበብ እየፈለግን የምናቆለጳጵሳቸው ተቃዋሚዎች ግን በደመስማሳው ስንመለከታቸው መንግስት አንድ ውሳኔ ባሳለፈ ቁጥር የፕሮፓጋንዳ መግለጫ ከመስጠት ባሻገር (ያውም ከሰጡ) ባለፈው ምርጫ ካየናቸው በኋላ የት እንደገቡ ጠፍተዋል፡፡

Thursday, September 22, 2011

ሞክሮ መሳሳት እና ከስህተት መማር


እስኪ የዛሬውን ወጋችንን ብዙ በተደመጠ ቀልድ እንጀምረው፡፡ አንዲት ተማሪ ለፈተና ተቀምጣለች፡፡ ጥያቄዎቹን አየቻቸው ‹እውነት› ወይም ‹ሐሰት› ነው መልሳቸው፡፡ ምንም ባለማጥናቷ የቱ እውነት፣ የቱ ሐሰት እንደሆነ አታውቅም፡፡ የመጣላት አማራጭ ሳንቲም ከኪሷ አውጥታ ‹አንበሳ› ሲሆን ‹እውነት›፣ ተቃራኒ ሲሆን ደግሞ ‹ሐሰት› እያለች መመለስ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ፈተናዋን ሰርታ ስትጨርስ በጣም ብዙ ጊዜ ተረፋት ስለዚህ የሰራችው ትክክል መሆን አለመሆኑን ለማረጋገጥ ፈለገች፡፡ ግን ደግሞ ማረጋገጫ መንገድ የላትም፤ ስለዚህ በጀመረችው መንገድ እንደገና ሳንቲም እየወረወረች አንበሳን ለእውነት፣ ጀርባውን ለሐሰት እየመደበች መልሷን ታረጋግጥ ጀመር፡፡

በእንዲህ ዓይነቱ ፈተና ውስጥ ሁለት መልስ ብቻ በመኖሩ፥ ያለሳንቲምም ቢሆን ሞክሮ መሳሳት፣ ሞክሮ ለመማር ነው፡፡ (በፈረንጅ አፍ Trial and Error Learning ይባላል፡፡ በአማርኛ ልተረጉመው ፈልጌ ነበር፤ ከበደኝ እንጂ! ‹ሞክሮ በመሳሳት መማር› ብለው ትክክል ነው እንዴ?) ግን ደግሞ በሕይወት ዓለም እልፍ መንገዶች አሉ፤ የትኛው መጨረሻው እንደሚያምር ለማወቅ ወይ በሁሉም መንገዶች ተራ፣ በተራ መሄድ አሊያም [ወደኋላ የምንመካከርበትን ጉዳይ ማድረግ] ያስፈልጋል፡፡ በሁሉም መንገዶች እየሄድን መጨረሻቸውን እንይ እንዳንል ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ ከችግሮቹ አንዱ፡- ለሙከራ የጀመርነው መንገድ መጨረሻው ባያምርስ? እሺ፡- መጨረሻው ሰላም ሆኖ መድረሻውን ስላልወደድነው ብቻ መመለስ ብንፈልግ የምንመለሰው እንዴት ነው? ከሁሉም የሚያሳዝነው ግን ሁሉንም መንገዶች ለመሞከሪያ በቂ ጊዜ የለንም፤ ሕይወት አጭር ናት፡፡

ዓላማቸው ግልጽ ባልሆነ የሐሳብ ድሪቶዎች ይህንን ያህል ካደከምኳችሁ ይበቃል፡፡ የዚህን ጽሁፍ ዓላማ ለማብራራት ግን አሁንም አንድ አንቀፅ ያስፈልገኛል፡፡ ከሰው ጋር ተግባብቶ ለመኖር እየሞከሩ፣ መሳሳት፤ እየተሳሳቱ፣ መማር ይቻል ይሆናል፡፡ በሰዎች ዕጣ ፈንታ ለመወሰን ግን እየሞከሩ መሳሳት፣ እየተሳሳቱ መታረም አይቻልም፡፡ ዕጣ ፈንታ መዳረሻ በመሆኑ ማጣፊያ (undo) የለውም፡፡ በሃገራችን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚወጡ መመሪያዎች እና ውጤታቸው ግራ ቢያጋቡኝ ይህንን መጻፍ ጀመርኩ፡፡

Thursday, September 15, 2011

መንግስት ያልቻለውን እኛ ብንሞክረውስ?


ጎበዝ! ወሩ የአዲስ ዓመት መጀመሪያ ነው፡፡ የኑሮ ውድነቱን ጉዳይ ካምናው የተሻለ የሚያሰኘው ነገር የለም፡፡ እንዲያውም ከሰሞኑ ሮይተርስ የኢትዮጵያ ስታትስተክስ ኤጀንሲን ጠቅሶ ያስነበበን ዜና እንደሚነግረን ከሆነ የገንዘብ ውድቀቱ ከአምናው ነሐሴ ጋር ሲነፃፀር ባለፈው ወር 40.6 በመቶ አሻቅቧል፡፡ ማለትም የዘንድሮ መቶ ብር መግዛት የሚችለው የአምናው 60 ብር መግዛት የሚችለውን ያክል ብቻ ነው፡፡ ገንዘብን ባንክ በማጠራቀም 40በመቶ ማትረፍ አይቻልም፤ በመነገድም ይህን ያህል ትርፍ ማግኘት ይቻል እንደሆነ እጠራጠራለሁ፡፡ ስለዚህ በደሞዝ ጭማሪ መርካት አይቻልም፤ ጊዜው ራስን የማዳን ነው፡፡ መንግስት ያተመውን ገንዘብ በቦንድ ግዢም አለ በሌላ ሰብስቦ ሊጨርሰው ስላልቻለ የኑሮ ውድነቱ በቅርቡ ላያባራ ይችላል፡፡

ስለሆነም ለኑሮ ዘይቤ ለውጥ ጊዜው ዛሬ ነው፡፡ የኑሮ ውድነትን ማሸነፍ የሚቻለው በኑሮ ዘይቤ ነው፡፡ (5/11 ወይም ቁምሳ ምናምን የተሰኙ የኑሮ ዘይቤዎች እዚህ ቦታ የላቸውም፡፡ ለጸሎት ካልሆነ በቀር እየጾምን ሳይሆን ሳንጾም መኖር መጀመር አለብን)

ዐቢይ ለውጥ

Saturday, September 3, 2011

የሁለት እምነቶች ጦርነት… [ወግ አጥባቂዎች እንዲያነቡት የማይመከር - ክፍል ሦስት]

ጦርነቱ እንደቀጠለ ነው፡፡ ጦር ሜዳው ሕሊና፣ ጦረኞቹ አማኞች እና ኢ-አማኒዎች ናቸው፡፡ በኔ ጦማር ኢ-አማኒዎች ምክንያተኞች እንደሆኑ ይታመናል፡፡ ለዚህም ነው፣ ስለ ኢ-አማኒዎች በተናገርኩ ቁጥር ከአማኒዎች ጋር ማወዳደር የሚቀናኝ፡፡ እንግዲህ በክፍል ሁለት ጽሁፌ ለማመልከት እንደታገልኩት አማኒዎች ከኢ-አማኒዎች አንፃር (ወይም አንግል) ሲታዩ ፈሪዎች፣ ጠባቦችና አምላካችን ብለው በሚጠሩት አካል ላይ ጨካኞች መሆናቸውን ገልጬ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ‹‹ሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም ይላል›› (መዝ. 14፥1) የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱሰ ጥቅስ ተንተርሼ ሙግቴን እቀጥላለሁ፡፡ ~ ‹ጎበዝ በይፋ ፈጣሪ የለም ይላል› ወደማለቱ ነኝ፡፡

ኢ-አማኒዎች (atheists) ሞራል የሌላቸውና ማስተዋል የተሳናቸው ተደርገው በአማኒዎች ይሳላሉ፡፡ ኢ-አማኒዎች ከአማኒዎች ይልቅ የሞራል (የሕሊና) ጥያቄን ከግምት ውስጥ ማስገባት የሚችሉና ዓለምን ለመቀየር የሚያስችል አስተውሎት ያላቸው ስለመሆናቸው ጥናቶች ሳይቀሩ ያረጋግጣሉ፡፡

Thursday, August 18, 2011

የሁለት እምነቶች ጦርነት… [ወግ አጥባቂዎች እንዲያነቡት የማይመከር - ክፍል ሁለት]

በክፍል አንድ ጽሁፌ የፈጣሪ ሕልውናን በተመለከተ መከራከር እና የግል አቋም መያዝ እንጂ መደምደሚያ ላይ መድረስ እንደማይቻልና በሳይንሳዊ ሙግት የፈጣሪን ሕልውና (የቅዱሳን መጽሃፍትን ፍፅምና) ማረጋገጥ እንደማይቻል በጥቂት ነጥቦች መግለፄ ይታወሳል፡፡ ዛሬ ደግሞ ቃል በገባሁት መሰረት ጥቂት ስለዝግመተ ለውጥ እና ኢ-አማኒነት ለመነጋገር የሚያስችሉንን ነጥቦች ይዤ ቀርቤያለሁ፡፡

ጥቂት ስለዝግመተ ለውጥ
በዝግመተ ለውጥ (evolution) እሳቤ ላይ ብዙ ተሳልቆዎች ተነግረዋል፡፡ አብዛኛዎቹ ስላቆች የተነገሩት ባላዋቂነት መሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ ከቀልዶቹ መካከል አንዱን አንስተን ጥቂት እንነጋገርበት፡፡ አባትና ልጅ እያወሩ ነው፡፡
ልጅ፡- አባዬ፤ ሰው ከየት ነው የመጣው?
አባት፡- እኛማ የአምላክ ፍጡሮች ነን፤
ልጅ፡- አስተማሪያችን ግን ሰው ከዝንጀሮ ነው የመጣው ብሎ ነገረን፤
አባት፡- እንግዲህ እሱ አባቱ ዝንጀሮ ይሆናል፤ እኔና አንተ ግን የአምላክ ፍጡሮች ነን፡፡

ቀልዱ ሊያስቅ ይችል ይሆናል እንጂ መሰረታዊ ችግር አለበት፡፡ ምክንያቱም የዝግመተ ለውጥ እሳቤ ሰው ከዝንጀሮ መጣ አይልም፡፡ የዘንድሮ ሰው እና የዘንድሮ ዝንጀሮ አንድ ዓይነት የዘርግንድ ነበራቸው የሚል መላምታዊ ድምዳሜ ግን ያስቀምጣል፡፡ ይሄ እንዴት ሊሆን ይችላል - ወደ መልሱ የሚያመራን ጥያቄ ነው፡፡

Monday, August 15, 2011

የሁለት እምነቶች ጦርነት… [ወግ አጥባቂዎች እንዲያነቡት የማይመከር]

ዓለማውያን በምክንያት ሲሟገቱ ኢትዮጵያውያን ግን ገና ‹‹የዘራፍ›› ዘመን ላይ ነን፡፡ ይህንን ለመናገር ያደፋፈረኝ በሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ ትችት መሰንዘር - በሃገራችን - ቡጢ የሚያስቀምስ ሃጢያት መሆኑን ስለማውቅ ነው፡፡ እኔ ኢ-አማኒ (atheist) ነኝ፡፡ በርግጥ እንደ ብዙሐኑ ሁሉ እኔም ቤተሰቦቼ በውልደት ያወረሱኝ አምልኮታዊ አስተሳሰብ ነበረኝ፡፡ ልዩነቱ ለአቅመ መጠየቅ ስደርስ የተነገረኝን መቀበል ስላልተቻለኝ የሆንኩትን ሆኛለሁ፡፡

ዛሬ በዚህ ጽሁፍ ላይ ትልቁ አጀንዳ የኔ ጉዳይ አይደለም፡፡ በርግጥ እኔ ኢ-አማኒ መሆኔን መግለፅ ያስፈለገኝ - ኢ-አማኒነት ከአማኒነት የተሻለ ምክንያታዊ ነው ብዬ ስለምከራከር ነው፡፡ ማንም አንባቢ ጽሁፌ ላይ የሚመለከተውን ሐሳባዊ ወይም አመክንዮአዊ ግድፈት በአስተያየቱ ሊጠቁመኝ ወይም በትችት ሊያር’ቀኝ (ር ይጠብቃል) የመሞከር መብቱ የተጠበቀ ነው፡፡

ፈጣሪ አለ ወይስ የለም?

Saturday, August 6, 2011

ለመደገፍ መደገፍ፤ ለመቃወም መቃወም

ቲፎዞነት የጋርዮሽ ስርዓትን ይመስለኛል፡፡ ሰዎች በቡድን ሆነው አንድን ነገር ብቻ በፍጹም ልቦና ለመደገፍ የመቁርባቸው ነገር - ካሰቡት ያስቃል፡፡ ሰዉ ሁሉ በየፊናው የሚደግፈው የእግር ኳስ ቡድን፣ የፖለቲካ ቡድን፣ የሃይማኖት ቡድን፣ የፆታ ቡድን ራሱ ሳይቀር ያበጃል፡፡
ማንቸስተር ዩናይትድ (ብልጫ አወዛጋቢ ቢሆንም) በጨዋታ ብልጫ አርሴናልን ቢረታ እንኳን የአርሴናል ደጋፊዎች ‹‹በጨዋታ በልጠናል›› ብለው መሟገታቸው፣ ወይም ደግሞ የቡና ደጋፊዎች ‹‹ጊዮርጊስ ከፍሏል›› ማለታቸውን አያቆሙም፡፡

የኢሕአዴግ ደጋፊዎች ኢሕአዴግ የፈለገውን ያክል የሚያስቀይም አዋጅ ቢያወጣና ርምጃ ቢወስድ ‹‹ትክክል ነው›› ብለው ሽንጣቸውን ገትረው ከመሟገት አይመለሱም፡፡ የተቃዋሚዎቹም ቡድን እንዲያው ነው፡፡ በእያንዳንዷ የገዢው ፓርቲ ርምጃ ላይ የትችት እና ተቃውሞ በትራቸውን ከማሳረፍ አይመለሱም፡፡ (እሺ - አንመለሰም ካላልኩኝ ራሴን ማፅደቄ ነው፡፡) ከቡድኖቹ ቁማር ጀርባ ያለችውን ሃገር ማሰብም ያስፈልጋል::

Monday, July 25, 2011

በዻሳ ወይስ badhaasaa?

የብሔር ፖለቲካ በጣም ስስ (sensitive) ነው፡፡ በቀላሉ ተቆስቁሶ ብዙ ሊጓዝ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ በኢሕአዴግ ዘመን፣ በብሔር ፌዴራሊዝም ከተከፋፈለች ወዲህ እንኳን የብሔር ፍላጎቶችና ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ አላገኙም፡፡ የኦሮሞ ብሔረሰብ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ ከ34 በመቶ በላይ ድርሻ አለው፡፡ (2007 National Census) ሆኖም የኦሮሞ ሕዝብ ለዘመናት የሚገባውን ትኩረት የመነፈጉ ጉዳይ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ለሚሆን ጊዜ ሲያነታርክ ቆይቷል፡፡

የብሔር (በተለይም የኦሮሞ ተወላጆች) ፖለቲካ ጉዳይ የታገሉለትን ያሕል ብዙ መሻሽል ባያስመዘግብም፣ በርካታ አማራጮችን ለፖለቲካው የሚመግቡ ኢትዮጵያውያንን አፍርቷል፤ እነ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ እነ ቡልቻ ደመቅሳ እና እነ ዶ/ር መረራ ጉዲና የዚህ ትሩፋቶች ናቸው፡፡

ለነገሩ የዚህ ወጌ ቁምነገር የብሔር ፖለቲካ በጥቅሉ አይደለም፤ ነገር ግን ከብሔር ፖለቲካ ዘውግ ውስጥ አንዱን መዝዤ መሟገት ቃጥቶኛል፡፡ ጉዳዩ የተቀበረ ቢመስልም ለኔ ግን ገና አልሞተም፤ ልክ በኤርትራ መገንጠል ጉዳይ ላይ መቁረጥ እንዳልቻልኩት ሁሉ - በዚህም ገና አልቆረጥኩም፡፡

በነገራችን ላይ ኢሕአዴግ ‹‹በመቃብሩ ላይ›› ካልሆነ በቀር የማይቀይራቸው በርካታ ጉዳዮች መካከል ይመደባል የዛሬ ጉዳዬ፡፡ ለዚያ ነው ብዙዎቹ ኢትዮጵያዊ ምኞቶቼ እውን እንዲሆኑ ቶሎ የኢሕአዴግ መቃብር እንዲማስ ሌት ተቀን የምመኘው፡፡

አላግባብ ልብ ማንጠልጠሌን ልተወውና

Friday, July 8, 2011

እንኳን ኢሕአዴግ ደርግም ወድቋል

ደርግ አንቀጥቅጦ በመግዛት አቻ የለውም፡፡ የሰራዊቱ ግዝፈት እንኳን ተራ ሽፍቶች የተደራጀ ጦር እንኳን የሚደመስሰው አይመስልም ነበር፡፡ የሰራዊት ግዝፈት ለአንድ ስርዓት ዋስትና ሊሆን እንደማይችል የተረጋገጠው በደርግ ውድቀት ነው፡፡

ለደርግ መውደቅ የራሱ የሰራዊቱ አስተዋፅዖ ቢኖርበትም እምነት አጉዳዩ የደህንነት ቢሮ ትልቅ ሚና ተጫውቷል፡፡ በወታደራዊ ስልት እዚህ ግባ የማይባል ዕውቀት የሌላቸውብሶት የወለዳቸውሽምቅ ተዋጊዎች ዘመናዊ አደረጃጀት ያለውን ግዙፉን ወታደራዊ መንግስት የገረሰሱት በዚህ ምክንያት ነው፡፡

Saturday, July 2, 2011

የመለስ ፖለቲካ እና የኢትዮጵያ አበሳ ባሳለፍነው 20 ዓመት

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያ መንግስት፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምናምን ማለት እየደበረኝ ነው፡፡ ምክንያቱም ለ20 ዓመታት ሲገዙ የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ የሁሉም ነገር ፈጣሪና ፈላጭ ቆራጭ ናቸው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ ከተባለ እኛንም ስለሚወክል፤ የመለስ ማለትን መርጫለሁ፡፡ “Power corrupts; absolute power corrupts absolutely” (ስልጣን ያበላሻል፤ ፍፁም ስልጣን ደግሞ ፈፅሞ ያበላሻል) እንዲሉ የአቶ መለስ ስልጣን እንዳበላሻቸው ከመናገር አልቆጠብም፡፡ አቶ መለስ ግን ተበላሽተው አልቀሩም ያበላሹት ብዙ ጉዳይም አለ፡፡ ለምሳሌ የሚከተሉት፡-

Tuesday, May 31, 2011

የአምባገነን መንግስታት ባሕርያት እና የመለስ እውነታዎች

አምባገነን መንግስታት ከአንድ ባሕር ይቀዳሉ፤ በርካታ የሚመሳሰሉባቸው ባሕርያት አሉዋቸው፡፡ በዚህች መዳፍ በምታክል ገጽ እና በእኔ ቁንፅል እውቀት ሁሉንም ዘርዝሮ መጨረስ ይከብዳል፡፡ ለነገሩ የአምባገነን መሪዎችን የጋራ ባሕርያት እነሱ ራሳቸው በቅጡ አያውቁትም፡፡ ነገር ግን በተለይ ጎልተው የሚለዩባቸውን ባሕርያቶች አንድ፣ ሁለት እያልን እስከአምስት መቁጠር እንችላለን፡፡ እነሆ፡-

Monday, May 30, 2011

ከአሜን ወዲህና ከአሜን ወዲያ ማዶ

በአገራችን ሰው ተመርቆ ሲያበቃ ዝም ማለት የለበትም - ‹‹ከአሜን ይቀራል!›› ይባላል፡፡ አሜን በፀጋ መቀበል፣ ይሁንልኝ፣ ይደረግልኝ እንደማለት ነው፡፡ ይሄ የዓለማችን ዕውቅ ደራሲዎች ‹አዎንታዊ አስተሳሰብ› ወይም ‹ተስፈኝነት› (optimism) የሚሉት ዓይነት እሳቤ ነው፡፡ ሰሞኑን ‹ተኣምራዊው ኃይል› በሚል የተተረጎመውን የርሆንዳ ባይርኔን መጽሃፍ እያነበብኩ ነበር፡፡ የአዎንታዊ አስተሳሰብ አቀንቃኝ ነች፡፡ እኔም የአዎንታዊ አስተሳሰብ አቀንቃኝ ነኝ ባይ ነኝ፤ ሰዎች ግን ብዙ ብሶት ሳወራ ስለሚሰሙ ከአሉታዊዎች ተርታ ያሰልፉኛል፡፡ ለዚያ ነው ዛሬ የ‹አሉታዊ አስተሳሰብ› ወይመ ‹ጨለምተኝነት› (pessimism) አቀንቃኝ ሁኜ ልሟገት የተነሳሁት፡፡

Pessimism ስሙ አያምርም፤ ጨለምተኝነት ነው፡፡ ነገር ግን የስሙን ያህል ክፉ ነው ወይ? ዓለማችንንስ ያቀኗት እውን አዎንታዊ አሳቢዎች (optimists) ብቻ ናቸው? የሁላችንም ጥያቄ ነው፡፡ አዎንታዊ አሳቢዎች(optimists) ስለ አሉታዊ አሳቢዎች (pessimists) ያላቸው አመለካከት ራሱ ጨለምተኛ (pessimist) ነው፡፡ የአሉታዊ አሳቢዎች ድርሻ በአዎንታዊ አሳቢዎች እይታ አፈር ድሜውን በልቷል፤ እየበላ ነው፡፡

በአንድ አስቂኝ አባባል እንጀምር፡-

Thursday, May 12, 2011

"ድር ቢያብር" ለአምባገነኖች ምናቸው ነው?


Gene Sharp የአረቡን ዓለም አብዮት አቀጣጥሏል የሚባልለትን From DICTATORSHIP to DEMOCRACY: a Conceptual Framework for Liberation የተሰኘ ጥናት ጸሃፊ ናቸው፡፡ ጥናቱ የአምባገነኖችን ዓይነት ሲዘረዝር ሚሊቴሪ አምባነገን፣ ከአባት ወደልጅ የሚተላለፍ የንግስና ሥርዓት፣ አሃዳዊ የፖለቲካ ፓርቲ የሚመራው እና የውጭ ወራሪዎች ብሎ ይመድባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን በየትውልዱ አራቱንም ዓይነት አምባገነኖች ለመሸከም ተዳርገናል፡፡ ይኸው አሁንም በአሃዳዊ የፖለቲካ ፓርቲ የሚመራው አምባገነናዊ አስተዳደር ላይ እንገኛለን፡፡

የመለስ ዜናዊን እና ፓርቲያቸውን አምባገነንነት የሚጠራጠር ኢትዮጵያዊ ካለ (ምንም እንኳን የአባይን መገደብ የማይደግፍ ‹‹ኢትዮጵያዊነቱን በገዛ ፈቃዱ ሰርዞታል›› እንደተባለው፣ ኢትዮጵያዊነቱ ይሰረዝ ለማለት ባልደፍርም፤) የአምባገነን ትርጉሙን ሊነግረን ይገባል፡፡

መለስ ዜናዊና ፓርቲያቸው ተለሳልሰው ቦታ፣ ቦታቸውን ከያዙ በኋላ የሚነቀንቃቸው ጠፍቷል፡፡ መጀመሪያ ላይ ብዙው ሕዝብ በጨዋታቸው ተሸውዶ ነበር፤ የምርጫ 97 ድራማ እስኪያጋልጣቸው ድረስ፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ለወንበራቸው ምን ያህል ቀናኢ እንደሆኑ በግልፅ አስመስክረዋል፡፡ በመሰረቱ እነመለስ በአናሳ ቡድን አመራራቸው ትልቅ ‹ኢምፓየር› መስርተዋል፡፡ ከስልጣናቸው በምርጫ ከወረዱ ከተጠያቂነት የማያስተርፋቸው ነገር አይጠፋም ስለዚህ በምርጫ ይወርዳሉ ብሎ መመኘት ልጅነት ወይም ጅልነት ነው፡፡

Gene Sharp ቀደም ሲል በጠቀስነው ጥናታቸው ሊዩ ጂ የተባለ ቻይናዊ ጸሃፊ በ14ኛው ክፍለዘመን ከጻፈው ታሪክ ውስጥ የሚከተለውን ያስነብቡናል፡፡

Monday, May 9, 2011

የአባይ ግድብ፣ የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ፣ የባሕር በር እና የወር ደሞዝ


አንዳንድ ደፋሮች ‹‹ኢትዮጵያውያን ምቀኞች ናቸው›› ይሉና አንድ ተረት ይተርታሉ፡፡ እግዚአብሄር አንዱን ኢትዮጵያዊ ‹‹የፈለግከውን ጠይቀኝ እና አደርግልሃለሁ፤ ነገር ግን ላንተ የማደርገውን ነገር በእጥፉ ለጎረቤትህ አደርግለታለሁ›› ብሎ ሲለው ፣ ሰውየው በብርሃን ፍጥነት ‹‹እንግዲያውስ አንድ ዓይኔን አጥፋልኝ›› አለው ይባላል፡፡

የአባይ ግድብ እና የኢትዮጵያውያን ስሜታዊ መንዘርዘር - - -
ኢሕአዴግ የአዋሽ ወንዝን ገድቤ 5000 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል አመነጫለሁ ቢል ኖሮ በአባይ ጉዳይ እንደተወዘወዝነው በደስታ የምንፈነድቅ አይመስለኝም፡፡ ለምን? እውን የመንግስት ሚዲያው እንሚለፍፈው ‹‹ቁጭቱ›› ብቻ ነው? ‹‹አይመስለኝም›› እንዲያውም ያቺ እላይ የጠቀስናት ድብቅ የጋራ ባሕሪያችን አፈንግጣ ወጥታ ነው፡፡ አባይን መገደብ ግብፅን ዋጋዋን መስጠት ስለሚመስለን ነው፡፡ ‹‹የታባቷ›› ዓይነት ነገር!!!

የአባይ ግድብ እና የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ - - -
እኔ የምለው? የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ አባይን መገደብ ብቻ ነው እንዴ? ምክንያቱም አሁን የምንሰማው መፈክር እኮ ‹‹ቦንድ በመግዛት እና የወር ደሞዛችንን በመለገስ አባይን ገድበን የትራንስፎርሜሽኑን ዕቅድ እናሳካ›› የሚል ነው፡፡ ቀድሞ ነገር የአባይ ግድብ በትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ መቼ ተካተተና፡፡ ተጨማሪ ነገር አይደል እንዴ? ሕዝባዊ አመፅ ባለማስነሳታችን - ምርቃት!!!

የአባይ ግድብ እና የወር ደሞዝ - - -
ሰሞኑን አዲስ አድማስ ላይ ካነበብኩት ወገኛ አባባል አንዱ ‹‹አባይ ድሮ ግንድ ይዞ ይዞር ነበር፤ አሁን ደግሞ ደሞዛችንን ይዞ ይዞራል›› ነው፡፡ በኢትዮጵያ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ እምብዛም ያልተዋጣለት በአብላጫ ድምፅ የመወሰን ጉዳይ ዘንድሮ ለደሞዝም ውሏል፡፡ በየመስራቤቱ አዳራሽ ቀድሞ የተወሰነው የደሞዝ ስጦታ አጀንዳ ይነሳና፣ የይስሙላ ውይይት ከተደረገበት በኋላ በአብላጫ ድምፅ የያንዳንዱ ሰው ደሞዝ ይወሰዳል፡፡ እኔ የምለው ‹‹የራስን ዕድል በራስ መወሰን›› የምትለዋ የሕገ መንግስታችን አወዛጋቢ ሐረግ ለወር ደሞዝ ሲሆን አትሰራም እንዴ?!

የአባይ ግድብ እና የባሕር በር - - -
የኢሕአዴግ መንግስት አባይን በመገደብ ብቻ ደርሶ አርበኛ ለመመስል ከመሞከሩ በፊት መመለስ ያለበት ጥያቄ ያለ አይመስላችሁም፡፡ ለኢትዮጵያ ከአባይ ግድብ እና ከባሕር በር የትኛው ያስፈልጋት ነበር? እውነቱን ለመናገር ከኤርትራ ጋር አብሮ የሸኘውን ወደባችንን በምንም ሊክስልን አይችልም፤ መቶ ብር ቀምቶ አንድ ብር የሰጠ ቸር አይሰኝም!!!

Wednesday, May 4, 2011

የሚከፈላቸውና የማይከፈላቸው ‹አዳሪዎች›


‹አዳሪ› የሚለውን ቃል የተዋስኩት ከአበባው መላኩ ጣፋጭ የግጥም ስብስብ ውስጥ ነው፡፡ ከግጥሞቹ ስንኞች ጥቂት ቆንጥሬ ጀባ ልበላችሁና ወደጽሁፌ ልንደርደር፡፡

‹‹… ሴትነቴን ወደው፣ እኔነቴን ንቀው፣
በፍቅሬ ተማርከው ገላዬ ስር ወድቀው፣
‹እን’ደር› ይሉኛል በስሜት ታውረው፣
እነሱ ቀድመውኝ በወንድነት አድረው፡፡…››

ጽሁፉ ወንደኛና ሴተኛ አዳሪዎችን ይመለከታል፡፡ በዚህ ወግ ውስጥ እስከዘለቅን ድረስ ‹አዳሪ› ማለት በሴሰኝነት የተጠመዱ ወንዶችና ሴቶችን እንጂ ከተቃራኒ ፆታ ጓደኛቸው ጋር ያደሩ እና የሚያድሩ ሰዎችን አይመለከትም፡፡

በመጀመሪያ ፍቅር ስለመስራት

Tuesday, May 3, 2011

ፅድቅና ኩነኔ


ኢትዮጵያ ሃይማኖቶችርስ በርስ ተከባብረው ተሳስበው የሚኖሩባት ሃገር ነች፡፡ የትዮጵያውያንን ማሕበራዊ ጋርዮሽ የሃይማኖት ልዩነታቸው ላወከውም፡፡ በዚህ ስሌት የሚከተለው ምነትም Aክባሪ ንደማያጣ ተስፋደርጋለሁ፡፡ ምነትና በሃይማኖት መካከል የተሰመረ መስመር መኖሩን ርግጠኝነት መናገርልችልም፡፡

ሃይማኖት ያለምነት ምንም ነውና፡፡ ስለዚህ ንድ ሰው ሃይማኖተኛ ለመሆን ምነት/ማመን ያስፈልገዋል ማለት ነው፡፡ ምላኩን ማመን፣ ቅዱሳት መፃሕፍት የሚናገሩትን ማመን፣ ወይም ጣፈንታው ቀድሞ መፃፍ ማመን፡፡