Pages

Monday, June 25, 2018

የማንነት ብያኔ አፈና…

ከእኛ አገር የማያልቁ ችግሮች መካከል አንዱ የማንነት አረዳድ እና አበያየን ጉዳይ ነው። ማንነት እና ምንነት የፖለቲካ ጫወታችን አስኳል ሆኖ ሳለ፣ የማንነት አበያየናችን ግን ግለሰቦች የራሳቸውን ማንነት የሚበይኑበት ነጻ ዕድል የማይሰጥ ነው። 

የኦነጉ በያን አሶባ ባንድ ወቅት ከኢሳት ቴሌቪዥን "ኦሮሞ ማነው?" የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር። "ኦሮሞ ነኝ ያለ" የሚል ምርጥ መልስ ሰጥተዋል። ነገር ግን ብዙዎች ማንነትን በዘር የሚወረስ እንጂ በማኅበራዊ-ሥሪት (social construction) የሚመጣ ነገር አድርገው አይመለከቱትም። እውነት መሆኑን ከራሷ ማረጋገጥ አልቻልኩም እንጂ ድምፃዊ ሴና ሰለሞን ከአማራ ተወላጆች የተወለደች ኦሮሞ ነች፤ "ኦሮሞ ነኝ" ስላለች። ራሷን የምትገልጸው እንደ ኦሮሞ ሲሆን፣ በዘፈኖቿ የታገለችውም ለኦሮሞ ሕዝብ ነጻነት ነው። የወላጆቿ የማንነት ታሪክ የሐሰት ወሬ ቢሆን እንኳ ነባራዊ ምሳሌ እናጣለን እንጂ፣ ምሳሌው ማንነትን የመምረጥ ግለሰባዊ ነጻነቱን የተሳሳተ አያደርገውም። 

'ኢትዮጵያዊ ማንነት አለ፣ የለም? ጎጃሜ ማንነት አለ፣ የለም? አዲሳበቤ ማንነት አለ፣ የለም?' የሚሉት ጉንጭ አልፋ ክርክሮች ምንጫቸው የግለሰቦች ማንነት እኛ ራሳችንን እንዲሁም ሌሎችን ከምንረዳበት መንገድ ውጪ መወሰን የለበትም ከሚል አስተሳሰብ የመነጨ ነው። በቀላል ቋንቋ ለመግለጽ አባባሉ "እኔ ናችሁ ከምላችሁ ውጪ መሆን አትችሉም" ነው። 

በበኩሌ ሰዎች የራሳቸውን ማንነት ብለው የሚጠሩት ወይ 'የሚኮሩበትን' አሊያም 'የተበደለባቸውን' [ወይም የተበደለባቸው የሚመስላቸውን] ማንነታቸውን ነው ብዬ ነው የማምነው። ይሁን እንጂ ሁሉም ሰዎች ማኅበራዊ ሥሪታቸው ከብዙ ድርብ፣ ድርብርብ ማንነቶች የተገነባ ነው። ጥቁር ሕዝብ መሐል ላደጉ ኢትዮጵያውያን ጥቁርነት የማንነታቸው መገለጫ መሆኑ ትዝ ብሏቸው አያውቅም። ነገር ግን ከኢትዮጵያዊ ወላጆች ተወልደው ነጮች አገር ያደጉ ኢትዮጵያውያን "ምንድን ነህ/ምንድን ነሽ?" የሚል ጥያቄ ቢቀርብላቸው፣ ጥቁርነታቸው ቀድሞ የሚመጣባቸው መልስ ሊሆን ይችላል? "ምንድን ነህ/ነሽ?" የሚለው ጥያቄ የማንነት ወይም የምንነት ጥያቄ መሆኑ አያጠራጥርም። መልሱ ግን ወጥ አይደለም። እንደ ሁኔታው እና ቦታው ይለያያል። አንዱ "አካውንታንት ነኝ" ብሎ ሙያውን እንደማንነቱ መገለጫ ሊጠቅስ ይችላል፣ ሌላዋ "ሙስሊም ነኝ" ልትል ትችላለች። በሁኔታው፣ በወቅቱ እና በቦታው ሰዎች ስለማንነታቸው የሚሰማቸው ስሜት የተለያየ ሊሆን ይችላል። ይህም የማንነትን ወጥ አለመሆንና ድርብርብነት ያረጋግጣል።

እኔ በማንነቴ ቀረፃ ውስጥ "የድሀ ልጅ" መሆኔን ያክል ተፅዕኖ የፈጠረብኝ ነገር አለ ብዬ አላምንም። የድሀ ልጅ ሆኖ ማደግ ያለንን ነገር 'ላጣው እችላለሁ' በሚል ፍርሐት እና የሌለንን ነገር 'ላገኘው አልችልም' በሚል ስጋት ውስጥ መኖር ማለት ነው። ይህ ማንነት ነው። በድህነት ውስጥ ላደገ ሰው፣ ዓለም ማለት የመግዛት አቅም ባላቸው እና በሌላቸው ሰዎች የተሞላች ናት። የአዲስ አበባ ድሀ፣ ከብራዚል ድሀ ጋር በሥነ ልቦና የሚያግባባ ማንነት አለው። ነገር ግን "የድሀ ልጅ" የሚባል ማንነት በኛ የፖለቲካ መዝገበ ቃላት የለም። ስለዚህ ከዚህ ውጪ ብዙ ማንነቶች አሉኝ። ለምሳሌ ጦማሪነት። ከዚህ በፊት ስታሰር ስፈታ የነበርኩት ተቺ ጦማሪ ስለሆንኩ ነው። ስለዚህ ምንድን ነህ ስባል 'ብሎገር ነኝ' የምልባቸው ግዜያት ብዙ ናቸው። ለምሳሌ እስር ቤት በማንነቴ ነው የታሰርኩት የሚሉ ነበሩ። እነሱ "ኦሮሞ በመሆኔ"፣ "አማራ በመሆኔ" ሲሉ እኔ ደግሞ "ብሎገር በመሆኔ" እል ነበር። ይህም ማንነት ነው። ይህንን ብነፈግ እንኳ በትምህርት ያፈራሁት፣ በተወለድኩበት አካባቢ ያፈራሁት፣ በእምነቴ ወይም ባለማመኔ ያፈራሁት ብዙ ማንነቶች አለኝ። 

ነገር ግን በኢትዮጵያ ፖለቲካ ብያኔ መሠረት እነዚህ ሁሉ ማንነቶቼ ዋጋ የላቸውም። "ምንድን ነህ?" ስባል የወላጆቼን የዘውግ ማንነት እንድናገር ይጠበቅብኛል። ወላጆቼ ቅይጥ ቢሆኑ እንኳን የአባቴን [ይህ ካልሆነ ደግሞ የእናቴን] የዘውግ ቡድን ማንነቴ ብዬ እንድናገር ይጠበቅብኛል። እኔ እኔን ይገልጸኛል የምለው ማንነት እንዲኖረኝ ነጻነቱ የለኝም። በዚህ አካሔድ "ኦሮሞ ነኝ" ማለት፣ ወይም "አማራ ነኝ" ማለት፣ ወይም "አዲሳበቤ ነኝ" ማለት ምንም ዋጋ/ጥቅም የለውም። ምክንያቱም በኔ ማንነት ላይ እኔ የመወሰን ነጻነቱ የለኝም። 

Wednesday, June 20, 2018

የተዘነጋው የኮንሶ እስረኞች ጉዳይ ("እኛስ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ወይ?")

ፎቶው ላይ ከግራ ወደቀኝ የሚታዩት፤ የኮንሶ መሪ ካላ ገዛኸኝ እና ወንድማቸው

በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ሕዝባዊ አመፆች በተቀጣጠሉበት ወቅት፣ በሕዝብ ብዛት ትንሿ ኮንሶም ከዐሥር ወራት ላላነሰ ጊዜ ሕዝባዊ ተቃውሞ ታደርግ ነበር። በወቅቱ የመብት ተሟጋቾች አመፁ አገር ዐቀፍ እንደሆነ ለማስረዳት እንደምሳሌ የኮንሶን ጉዳይ ደጋግመው ይጠቅሱት ነበር። በወቅቱ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሠላማዊ ተቃውሞዎችን በኃይል በመበተን፣ ብዙዎችን ወደ እስር ቤት አጉረዋል። ከነዚህ እስረኞች ውስጥ የኮንሶ የጎሳ መሪ የሆኑት ካላ ገዛኸኝ ወልደዳዊት ካዮቴ ይገኙበታል። ('ካላ' በጎሳ መሪነት የሚገኝ የጎሳ ሐረግ ማዕረግ ነው።)

ካላ ገዛኸኝ ከመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ በሲቪል ምሕንድስና ተመርቀዋል። የጎሳ መሪነቱን ከአባታቸው የወረሱት በጥቅምት 2006 በባሕላዊው ወግ መሠረት ከአባታቸው ነበር። የጎሳ መሪው በኮንሶ ማኅበረሰብ ልማድ መሠረት ልማዳዊ ዳኝነት፣ ግልግል እና ሌሎችም ማኅበራዊ አስተዳደር ይሰጣል። ይሁን እንጂ የአሁኑ የጎሳ መሪ ካላ ገዛኸኝ ሠላማዊ ሕዝባዊ ጥያቄ በማንሳታቸው ምክንያት ከሌሎች የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት ጋር ለእስር ከተዳረጉ እና ከማኅበራዊ ኃላፊነታቸው ከተገለሉ አንድ ዓመት ከ10 ወራት አለፏቸው። ካላ ገዛኸኝ በተከሰሱበት መዝገብ ብቻ 43 ሰዎች ተከስሰዋል። ያነጋገርኳቸው የአካባቢው ነዋሪዎች እንደነገሩኝ ግን የጠቅላላ እስረኞቹ ቁጥር 467 ነው። እነዚህ ሕዝባዊ ጥያቄ ያነሱ የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት በጊዶሌ ማረሚያ ቤት፣ ኮንሶ ፖሊስ ጣቢያ እና አርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ታስረው ይገኛሉ። ካላ ገዛኸኝ እና ሌሎችም 180 ገደማ ሰዎች የታሰሩት በአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ነው። 

ከእስር ውጪ ከመንግሥት የሥራ ገበታቸው ተባርረው (እና ከግንቦት 2008 ጀምሮ) ቤተሰባቸው የኅልውና አደጋ ላይ የወደቀባቸው ከ250 በላይ የኮንሶ ብሔረሰብ አባላት እንዳሉ ዝርዝሩን እና አቤቱታ ያቀረቡበትን ደብዳቤ ተመልክቻለሁ። 

የኮንሶ ጥያቄ ምንድን ነው?

የአካባቢው ነዋሪዎች እንደነገሩኝ ኮንሶ ተጠሪነቷ ለደቡብ ክልላዊ መንግሥት የነበረች ልዩ ወረዳ ነበረች። ይሁን እንጂ ከመጋቢት 2003 ጀምሮ ልዩ ወረዳነቷ ቀርቶ፣ ተጠሪነቷም ለዞን ሆኗል። ነዋሪዎቹ በአሁኑ ወቅት 'በሰገን አካባቢ ሕዝቦች' አስተዳደር ሥር 'እንደተጨፈለቁ' የነገሩኝ ሲሆን፣ ይህም የራስን በራስ የማስተዳደር ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ከመጣሱም በላይ ከተለያዩ የመንግሥት አገልግሎቶች የመገለል ጦስ እንዳመጣባቸው አጫውተውኛል። ይህንንም በመቃወም በ2008፣ የ81ሺሕ ሰዎች ፊርማ በማሰባሰብ 12 አባላት ያሉት ኮሚቴ በመወከል ጥያቄያቸውን ለክልሉ ምክር ቤት እንዲሁም ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አቅርበዋል። ሆኖም ያገኙት መልስ የለም። ይልቁንም የፀጥታ ኃይሎች 12ቱን የኮሚቴ አባላት ሊያስሯቸው ሲሞክሩ ሕዝቡ ሆ ብሎ ወጥቶ በማስቆም፣ የኮሚቴ አባላቱ እንዳይታሰሩ በሚል ውክልናቸውን አንስቷል። 

ኮሚቴዎቹ ቢነሱም ተቃውሞዎቹ ግን የቀጠሉ በመሆኑ በወቅቱ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር የነበሩት አሰፋ አብዩ ተወካዮቻችሁን ላናግር በማለታቸው 23 ሰዎች ተወክለው አነጋግረዋቸዋል። ወትሮም ጥያቄያቸውን ማስተናገድ የነበረበት ሌላ አካል በመሆኑ የፌደራል ፖሊስ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ካላ ገዛኸኝን ጨምሮ ሁሉንም ለቃቅሞ ለእስር ዳርጓቸዋል። በእስሩ ወቅት የጎሳ መሪውን እና ልማዱን በሚያዋርድ መልኩ ካልሞተ በቀር ከክንዱ የማይወልቀውን ከዝሆን ጥርስ እና ከአውራሪስ ቀንድ የተሠራ የቃልኪዳን አምባር ፖሊሶች መሰባበራቸውን በምሬት ነግረውኛል።

ክሱ ምን ይላል?

የታሰሩት ሰዎች ከ400 በላይ ቢሆኑም ፍርድ ቤት እየቀረቡ ያሉት ግን የተወሰኑት ብቻ እንደሆኑ ተነግሮኛል። ፍርድ ቤት ከሚቀርቡት ታሳሪዎች መካከል የነካላ ገዛኸኝ መዝገብ (እዚህ ሙሉውን ማየት ይቻላል) ላይ እንደሚነበበው ከሆነ ክሱ የፖለቲካ ነው። "የወረዳው ሕዝብ በመንግሥት ላይ በአመፅና በአድማ ካልተሰለፈ ይህ ጥያቄ በሠላማዊ መንገድ ምላሽ አያገኝም" በማለት ቅስቀሳ አድርገዋል በሚል ታስረው እስካሁን ፍርድ አላገኙም። እንደሌሎች ፖለቲካ እስረኞችም ክሳቸው አልተቋረጠላቸውም። አሁን ቀጣዩ ቀጠሯቸው በመጪው ሰኞ ሰኔ 18/2010 ነው። 

ለምን አልተፈቱም?

የኮንሶ እስረኞች ከኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች በተቃውሟቸው ምክንያት ተለቃቅመው እንደታሰሩት ዜጎች ሁሉ የፖለቲካ እስረኞች ናቸው። ይሁን እንጂ ከኮንሶ እስረኞች መካከል እስካሁን አንድም ሰው አልተፈታም። በዚህም "እኛ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ወይ?" የሚል ቁጭት ተሰምቷቸዋል። ከ350 ሺሕ በላይ ነዋሪ ባላቸው 42 የኮንሶ ቀበሌዎች የተውጣጡ ሽማግሌዎች ይህንን አቤት ለማለት ተሰብስበው አኔቱታዎቻቸውን ለክልሉ መንግሥትም፣ ለፌዴራሉ መንግሥትም አቅርበው ነበር። ይሁን እንጂ ማንም መልስ አልሰጣቸውም። ይልቁንም አሁንም በክልሉ የፀጥታ ኃይሎች እየተዋከቡ ነው። ከሽማግሌዎቹ መካከል አንድ ሰው ባለፈው ሳምንት ሲታሰር ሌሎችም ማስፈራሪያ እየደረሰባቸው ነው። 

አሁን ዜጎች የፀጥታ ኃይሎች ማዋከብ በመቅረቱ መፍራት ባቆሙበት ሰዐት፣ የኮንሶ ሰዎች ግን አሁንም ከእስር ስጋት ጋር ተፋጥጠዋል። ይህንን እጅግ በጣም አሳጥሬ የጻፍኩትን መረጃ የሰጡኝ ሰዎች ሥማቸውን መጥቀስ ይፈቅዱልኝ እንደሆነ ስጠይቃቸው፣ "እኛ አካባቢ ያለው ሁኔታ እንደ አዲስ አበባ አይደለም። ለኛ ጥሩ አይደለም" ብለውኛል። 

ለኮንሶ ብሔረሰብ ዜጎቻችን የሚደርስላቸው ማን ይሆን? [እባካችሁ ይህንን መረጃ እንዲሰራጭ በማገዝ የሚመለከተው አካል በአስቸኳይ የኮንሶ ዜጎቻችንን ከእስር እንዲፈታ የበኩሎን አስተዋፅዖ ያድርጉ።]

Monday, June 4, 2018

በማንነት ማፈናቀልን እንዴት መቀነስ ይቻላል? (የግል ጥቆማ)

(ከታች ያስቀመጥኳቸው ጥቆማዎች በጥናት ላይ የተመሠረቱ የመፍትሔ ሐሳቦች ሳይሆኑ በግል ትዝብት የተጠቆሙ ናቸው። በምስሉ ላይ የሚታየው (ፎቶ: ቴዎድሮስ አያሌው) በ1977 ድርቅ ወቅት ደርግ ቄለም ወለጋ አስፍሯቸው የነበሩ እና አሁን ተፈናቅለው አላማጣ የሚገኙ ናቸው። በምስሉ እንደሚታየው አብዛኛዎቹ የተወለዱት እዚያው አካባቢ ሲሆን፣ ወላጆቻቸው እና አያቶቻቸው ናቸው ከአላማጣ ነበር ቄለም ወለጋ እንዲሰፍሩ የተደረጉት።)

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ 'የማንነት' እና 'የብሔር' ፖለቲካ ወይም ጥያቄ ተምታተዋል። ብዙ ግዜ ሁሉም ነገር 'የብሔር ጥያቄ' ነው፤ መልሱም የሚገኘው 'በብሔርተኝነት' ነው የሚባለው ጉዳይ ከማንነት ጋር የተያያዘውን ጥያቄ ያድበሰብሰዋል። እንዲያውም አንዳንዴ ብሔርተኝነት ችግሩን ሊያባብሰው ይችላል። የማንነት ወይም የብሔር ትርጉሙም እንዲሁ የተምታታ ነው። ምክንያቱም ማንነትም ይሁን ብሔር በተለምዶ የሚበየነው በቋንቋ ላይ ተመሥርቶ ነው። ስለዚህም በተምታታ ትርጉም ላይ የተመሠረተ ብሔርተኝነትም ለተሳሳተ ጥያቄ የተሳሳተ መልስ ለመስጠት ይዳርጋል። ማንነት በቋንቋ ሊመሠረት ይችላል፤ ነገር ግን አንድ ቋንቋ እየተናገሩ የተለያየ ማንነት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ሕዝቦች አሉ። ማንነት በፆታ ብቻ ሊወሰን ይችላል። ወይም ደግሞ በፆታዊ ግንኙነት ምርጫ ሊወሰን ይችላል። በመልክ ወይም በቆዳ ቀለም። ወዘተ… ለምሳሌ ያክል ቱትሲዎች እና ሁቱዎች አንድ ቋንቋ ተናጋሪ ሆነው፣ ልዩነታቸው የመልክ (እና የታሪክ ድርሻ) ነው። 

ፌዴራሊዝሞች የአወቃቀር ስርዓታቸው ምንም ቢመስል፣ ዋነኛ ዓላማቸው በብሔርተኝነቶች መካከል ውጥረቶችን ሥልጣን በማከፋፈል እና በማጋራት ማርገብ ነው። የእኛው ግን ውጥረቱን ምናልባትም አባብሶታል አልያም ገሀድ አውጥቶታል። በሕገ መንግሥቱ ባይሰፍርም "የእንትን ክልል፣ ለእነ 'እንቶኔ'" የሚል ያልተጻፈ ሕግ አለ። 'እንቶኔነት' ከወላጆች በደም የሚወረስ መሆኑም እንዲሁ ያልተጻፈ ሕግ ነው። ስለዚህ በእንትን ክልል ያሉ ከእነ እንቶኔ ውጪ ያሉ ነዋሪዎች በሙሉ የመገለል፣ የመጠቃት፣ የመሰደድ ዕድላቸው ሰፊ ነው። በእርግጥ በዚህ መሰሉ ጥቃት እና ስደት በተደጋጋሚ የሚጠቁት ሰዎች በተለይ በብዙ ክልሎች የተበተኑት ብሔረሰብ አባላት ናቸው። ነገር ግን ይሔ ዕጣ ያልገጠመው አለ ለማለት ይከብዳል። ባለፈው ዓመት ከሶማሌ የተፈናቀሉት 600 ሺሕ የኦሮሞ ተወላጆች ጉዳይ ሪከርድ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ የአማራ ተወላጆች የመፈናቀል ዜናን መስማትም ለጆሮ እንግዳ አይደለም። የሆነ ሆኖ ዛሬ በኢትዮጵያ ያሉ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች ቁጥር 1 ሚሊዮን ተኩል ገደማ ነው። በየዘውጉ ተጎራባቾች አንዱ አንዱን በውኃ እና ግጦሽ/እርሻ መሬት ማጥቃት እና ማፈናቀል የነበረ፣ እና የበለጠ ፖለቲካዊ እየሆነ የመጣ ነገር ነው። ማንነትን መሠረት ያደረጉ መፈናቀሎች በተከሰቱ ቁጥር የዘውጉን ቡድን እየቆጠሩ የአንድ ወገን ጉዳይ ብቻ ማስመሰሉ ለብሔተኝነት ፖለቲካ ይበጅ ይሆናል እንጂ ችግሩን ለመቅረፍ እምብዛም አይበጅም። ልብ በሉ፣ የተፈናቀሉት ሰዎች በማንነታቸው እስከሆነ ድረስ የተፈናቃዮቹን ማንነትም ይሁን የአፈናቃዮቹን ማንነት መጥቀሱ ላይ ችግር የለውም። ነገር ግን ለብሔርተኝነት ትርፍ ሲባል ብቻ ነገሩ በሁለት ሕዝቦች መካከል የተደረገ ፍጥጫ ማስመሰል እሳቱ ላይ ነዳጅ ማርከፍከፍ ነው። ከዚያም በላይ ሰዎች ችግሩን በገለልተኛ ዓይን አይተው እንዳይከላከሉት ወይም ጥብቅና እንዳይቆሙለት ይገፋል።

ለምሳሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝ ክልል አንድ ቀበሌ ውስጥ የተፈናቀሉ የአማርኛ ተናጋሪዎች ጉዳይ "የቤንሻንጉል-ጉሙዝ ሕዝብ የአማራን ሕዝብ አፈናቀለ" ብሎ መዘገብ የተሳሳተ ምስል ከመስጠቱም በተጨማሪ በሁለቱ ሕዝቦች መካከል መቃቃር ይፈጥርና በክልሉ ሌሎች ቀበሌዎች ነዋሪዎች የሆኑ አማርኛ ተናጋሪዎችንም ለበለጠ ጥቃት ሊዳርግ ይችላል። አንዳንዴ መፈናቀሎቹ የሚከሰቱት በቀበሌዎቹ አስተዳደሮች ሆኖ ሳለ፣ የሕዝቡ ሥራ አስመስሎ ማቅረቡም ነዋሪዎቹን ከጎረቤቶቻቸው ጋር ማቀያየም ነው።

ችግሩ እንዴት ይቀረፍ?

በመጀመሪያ ደረጃ የችግሩን ምንጭ በአግባቡ መፈተሽ አስፈላጊ ነው። ዋነኛው ችግር የሚመስለኝ የአስተሳሰብ ነው። 

1ኛ፣ ክልሎች የየትኛውም ክልል ተወላጅ በክልላቸው የመኖር መብት እንዳለው መቀበልና መብቱን ማረጋገጥ አለባቸው።

የትኛውም ክልል የየትኛውም ብሔረሰብ ተወላጅ የግል ንብረት አይደለም። የትኛውም ብሔረሰብ ተወላጆች በየትኛውም ክልል ውስጥ ከየትኛውም ብሔረሰብ ተወላጅ የበለጠ ወይም ያነሰ መብት የላቸውም። የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 32/1 "ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወይም በሕጋዊ መንገድ ሀገሪቷ ውስጥ የሚገኝ የውጭ አገር ዜጋ በመረጠው የአገሪቱ አካባቢ የመዘዋወርና የመኖሪያ ቦታ የመመሥረት፣" መብት አለው ይላል። ይህ ደግነቱ ሕገ መንግሥቱ አክብሮታል አንጂ ባያከብረውም የማይሻር የተፈጥሮ ሕግ ነው። በክልሎች ቀርቶ በአገራት ድንበሮች ይህንን መገደብ ከተፈጥሮ ሕግ ያፈነገጠ፣ ነገር ግን ለስርዓት (order) ሲባል የምንታገሰው ሕግ ነው። ይህንን ከልብ መቀበል ያስፈልጋል። በሕግ እና ደንቦች የሚተገበርበት መንገድ ይመቻቻል እንጂ በልዩነት የሚታደልበት/የሚነፈግበት መንገድ ሊኖር አይገባም። 

ፌደራሊዝሙ ያልተማከለ አስተዳደር ፈጥሯል። (በፌዴራሊዝሙ አወዛጋቢው ጉዳይ አከላለሉ ዘውግ-ተኮር መሆኑ ላይ ነው። ይሔ ጽሑፍ መዋቅሩ ሳይለወጥ ችግሩን መቅረፍ ላይ ያተኮረ ስለሆነ ወደዛ ውዝግብ አንገባም።) እነዚህ አስተዳደሮች በእየርከኑ ባሉ የአስተዳደር ክፍሎች ውስጥ የነዋሪዎችን ቁጥር ከግምት ውስጥ ያስገባ የብዙኃን አመራር እና የድሀጣንን መብት የማክበር ግዴታ አለባቸው። ብዙኃኑ የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ከሆነ ቋንቋው የክልሉ የሥራ ቋንቋ ባይሆን እንኳ የአስተዳደር ክፍሉ የሥራ ቋንቋ መሆን ይኖርበታል። ይህ ግን ለአስተዳደር ቅልጥፍና እንጂ መብትን ለማከፋፈል አይደለም። ድሀጣኑ ከብዙኃኑ ዕኩል መብቶች እና ዕድሎች ሊኖሯቸው የግድ ነው። በሕጋዊ መንገድ መኖሪያ ቦታ የማግኘት እና የመሥራት መብታቸው ያለቁጥራቸው ወይም ያለማንነታቸው ገደብ ሊከበርላቸው ይገባል። የአካባቢ አስተዳደሮች ይህ አረዳድ እንዲሰርፃቸው ያልተቋረጠ የብዙኃን መገናኛዎች ዘመቻ እና የግንዛቤ ማስበጫ ሥልጠናዎች ሊሰጧቸው ይገባል። (በነገራችን ላይ በብዙ ክልላዊ አስተዳደሮች ውስጥ በርካታ አማርኛ ተናጋሪ ነዋሪዎች ያሉ ቢሆንም፣ ከአማርኛ ተናጋሪዎቹ ቁጥር ያነሰ ተናጋሪ ያላቸው ቋንቋዎች የሥራ ቋንቋ ሳይሆኑ ሌሎቹ የሆኑበት ብዙ ምሳሌ አለ። የአማርኛ ተናጋሪዎቹ ቁጥር እና አሰፋፈር እስከፈቀደ ድረስ ልዩ የአስተዳደር ዞን፣ ወይም ተደራቢ የሥራ ቋንቋ መሆን የማይችልበት ሕጋዊ አግባብ የለም።)

2ኛ፣ ከትውልድ ክልላቸው ውጪ የሚኖሩ ግለሰቦች የሚኖሩበትን ክልል ሕግ እና ደንቦች (ፍትሓዊ ወይም በሁሉም ላይ የተጣሉ እስከሆኑ ድረስ) ማክበር አለባቸው። 

አንዳንድ ከትውልድ ቀዬአቸው ውጪ የሚኖሩ ዜጎች፣ ማኅበረሰቤ ብለው የሚጠሩት የተወለዱበትን እንጂ የሚኖሩበትን ቀዬ አይደለም። ይባስ ብሎ የተወለዱበት፣ ያደጉበትን ቀዬ ሳይሆን የወላጆቻቸውን ደም እና የትውልድ ቀዬ ቆጥረው ቀዬዬ ብለው የሚጠቅሱ አሉ። "የኔ" የሚሉትን ማኅበረሰብ መምረጥ የግል ድርሻቸው ቢሆንም የሚያስከፋው ነገር የሚኖሩበትን ማኅበረሰብ የሚንቁ ሰዎች መኖራቸው ነው። እነዚህኞቹ፣ በሚኖሩበት አካባቢ የአስተዳደር ችግር ሲደርስባቸው 'አቤት' የሚሉት ለሚኖሩበት ክልል አስተዳደር የላይኛው ክፍል ሳይሆን፣ ለመጡበት ክልል አስተዳደር ነው። ይህ ያልተማከለ አስተዳደር የሥልጣን ክፍፍልን የሚጋፋ እና በክልሎች መካከል ውጥረት የሚያነግሥ አካሔድ ነው። በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል አንድ ቀበሌ ውስጥ አስተዳደራዊ በደል የደረሰባቸው ዜጎች፣ ከዚያ በላይ ላለው አስተዳደር ወይም ፌዴራል መንግሥቱ ያመለክታሉ እንጂ ለመጡበት/ለሚወለዱበት ክፍል ማመልከት የለባቸውም። 

ዜጎቻችን አገር ለቀው ሲወጡ፣ የሚቀበላቸውን አገር ባሕልና ስርዓት አክብረው እንደሚኖሩ ሁሉ፣ በአገር ውስጥ ከአንዱ ቀዬ ወደሌላው ሲሔዱ፣ አዲስ ለሚኖሩበት አካባቢ ልማድ እና አሠራር (መሠረታዊ መብቶቻቸውን እስካልገፈፉ ድረስ) ተገዢ መሆን ይኖርባቸዋል። የአካባቢውን ደንብና ስርዓት አለማክበር የግጭት እንዲሁም የመፈናቀል መንስዔ ስለሆነ በዚህ መንገድ መከላከልም ይቻላል።

3ኛ፣ ብሔርተኞች ብሔርተኝነት በዘውግ ሳይሆን በክልል ላይ አስተሳሰቡን እንዲወስን ማድረግ አለባቸው። 

ይህ የዘውግ ብሔርተኝነት (ethno-nationalism) ከክልሎቹ ሥያሜ ይጀምራል። አማራ፣ ሶማሊ፣ አፋር፣ ሐራሪ፣ ቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልሎች ለምሳሌ በክልሎቹ በሚኖረው አብዛኛው ሰው ዘውግ ሥያሜ ነው ክልሎቹ የሚጠሩት። ከዚህ በተሻለ ኦሮሚያ፣ ትግራይ፣ ጋምቤላ እና ደቡብ ሕዝቦች ዐቃፊ አገላለጽ አላቸው። ይሁን እንጂ እነርሱም ብሔርተኝነታቸው ክልላዊ (territorial-nationalism) አይደለም። ለምሳሌ በኦሮሚያ ገዢው ፓርቲ ኦሕዴድ (የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት) እንጂ "የኦሮሚያ ሕዝቦች" አልተባለም። በኦሮሚያ የሚኖሩት ግን የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች ብቻ ባለመሆናቸው ዐቃፊነት ይጎድለዋል። በዚያው ክልል ተቃዋሚው ኦፌኮ (የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ) ነው። የኦሮሚያ አለመሆኑ ብሔርተኝነቱ በክልሉ ያሉትን ሌሎች ዘውጎች እንዳያቅፍ ከሥሙ ጀምሮ እንቅፋት ይሆናል። የሌላ ዘውግ አባላት ለመብቶቻቸው ለመታገል እነዚህን ድርጅቶች መቀላለቀል አይችሉም ማለት ነው። በብአዴንም ተመሳሳይ ችግር ነው የምንመለከተው። በትግራይ አረና ምንም እንኳን በተግባር ባይሳካለትም በአስተሳሰብ ደረጃ ክልላዊ ፓርቲ ነው። የክልሉ ነዋሪ እስከሆኑ ድረስ ትግራዋይ ያልሆኑ ሰዎችም አረናን መቀላቀል ይችላሉ። 

ብሔርተኝነትን ክልላዊ ማድረግ በክልሉ ውስጥ ከብዙኃኑ ዘውግ ያልተወለዱ ሰዎች በክልሉ ውስጥ ውክልና እንዲኖራቸው ያደርጋል። ብዙዎቹ መፈናቀሎች የሚከሰቱት ሰዎቹን የሌላ ክልል ሰው ናቸው ብሎ ከሚያስብ በመነጨ አስተሳሰብ ነው። ነገር ግን ሰዎች አንድን አካባቢ መርጠው በሕግ አግባብ ነዋሪ እስከሆኑ ድረስ መወከል የሚኖርባቸው በሚኖሩበት አካባቢ እንጂ ጥለውት በመጡት አካባቢ መሆን የለበትም። ብሔርተኝነት ክልላዊ ሲሆን በነዋሪዎቹ መካከል ያለውን የዘውግ ውጥረት ይቀንሳል። ለምሳሌ ያክል በኦሮምያ ክልል ላሉ አማራዎች የአማራ ክልል ብሔርተኝነት ነው ጥብቅና የኦሮሚያ ብሔርተኝነት እንዲሆን ያደርጋል። 

4ኛ፣ የፌዴራል መንግሥቱ ከቀዬ ለመሰደድ እና የአገር ውስጥ ፍልሰት ፖሊሲ መቅረፅ አለበት። 

አዲስ አድማስ ጋዜጣ የጠየቃቸው አንድ ተፈናቃይ ወደትውልድ መንደራቸው ለምን እንደማይሔዱ ሲናገሩ ከትውልድ ቀያቸው የተሰደዱት የእርሻ መሬት አጥተው እንደሆነ ተናግረዋል። በርግጥም የአገር ውስጥ ፍልሰት ዋነኛው መንስዔ የእርሻ መሬት ለልጅ ልጆች ሲተላለፍ እየጠበበ ቤተሰብ ማስተዳደር ባለመቻሉ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ብዙ ግዜ በመታረሱ መሬቱ እየነጠፈ ራሳቸውን ለማስተዳደር ሌላ ቦታ ሔደው ማረስ ስለሚገደዱ ነው። እነዚህ ከቀያቸው በችግር የፈለሱ ዜጎች ሌሎች መንደሮች እየሔዱ ጫካዎችን በመመንጠር፣ የግጦሽ መሬቶችን በመውረር እና በሌሎችም ሕጋዊ በሆኑና ባልሆኑ መንገዶች የሚቀይሱት መንደር ከሔዱበት አካባቢ ሰዎች ጋር ግጭት ውስጥ እየከተታቸው ነው። ስለሆነም ይህ ችግር እየተባባሰ ይሔድ እንደሆነ እንጂ እየቀነሰ የሚሔድ አይመስልም። ሆኖም የፌዴራል መንግሥቱ ይህንን ጉዳይ አቅጣጫ ለማስያዝ የሚያስችል ፖሊሲ የለውም። ችግሩ አንድም ከሕዝብ ብዛት ጋር የሚያያዝ ነው። ይሁን እንጂ ያለፉት ሁለት የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዶች የሕዝብ ብዛትን በተመለከተም ይሁን የአገር ውስጥ ፍልሰትን በተመለከተ ያስቀመጡት አቅጣጫ የለም። ይህ ለቀውሱ መባባስ ብቻ ሳይሆን አፋጣኝ የእርምት እርምጃ መውሰድ እንኳን እንዳይቻል አድርጓል። 

5ኛ፣ መጠባበቂያ ፈንድ መመደብ።

ምንም እንኳን ዋናው ሥራ መፈናቀልን መከላከል ቢሆንም ከሆነ በኋላም ሰብአዊ እርዳታ ለተፈናቃዮቹ በአስቸኳይ ሊደርስላቸው ይገባል። በበጀት ረገድ ምን እየተሠራ እንደሆነ አላውቅም። የሆነ ሆኖ የዘንድሮን ያክል የከፋ ባይሆንም መፈናቀል በእየዓመቱ እየተከሰተ ነው። በአሁኑ ወቅት ብዙዎቹ ተፈናቃዮች በጊዜያዊ መጠለያዎች ውስጥ ናቸው። ግዜያዊ መጠለያዎቹ መሠረታዊ ፍላጎቶቻቸውን ለሟሟላት እንኳ አይችሉም። የንፅህና መጠበቂያ እና መፀዳጃ ሥፍራዎች አልተመቻቹላቸውም። ከምግብና መጠጥ እጥረቱ በተጨማሪ መሠረታዊ የሕክምና አገልግሎት ማግኘት የማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ናቸው። በዚያ ላይ ጊዜያዊ መጠለያዎቹ ውስጥ ሳይገቡ በአካባቢው ሰዎች ተጠግተው የሚኖሩም አሉ። ከችግሩ አሳሳቢነት አንፃር መንግሥት መጠባባቂያ በጀት በዚህ ሥም ማዘጋጀት እና የሰብአዊ እርዳታ ማድረግ እንዲሁም መልሶ ማቋቋም ይኖርበታል። 

Friday, June 1, 2018

የተቃውሞው ጎራ ለምን ደነገጠ? (What to do next?)

ኦሕዴድ እና ብአዴን በሕወሓት የበላይነት ይመራ የነበረውን የኢሕአዴግ ፖለቲካ ከውስጥ መነቅነቅ ሲጀምሩ ተቃዋሚዎች ተደስተው ነበር። ኦሕዴድ በክልሉ አንፃራዊ የተቃውሞ-ነጻነት ሲፈቅድም እንዲሁ ተደስተዋል። ነገር ግን የዐብይ ጠቅላይ ሚኒስትርነት እና የተቃዋሚውን ቋንቋ መነጋገራቸው ድንጋጤ ፈጥሯል። ባጭሩ ተቃዋሚዎች ከኢሕአዴግ ጋር "መደራደር ይገባናል" ሲሏቸው የነበሩት ጉዳዮች - የፖለቲካ እስረኛ ማስፈታት እና አንዳንድ አዋጆችን ማሻሻል፣ በጥቅሉ የፖለቲካ ምኅዳሩን የማስፋት ጥያቄ እና ተቋማትን ከፖለቲካ ጥገኝነት ማላቀቅ - የመሳሰሉትን ነገሮች በራሳቸው በኢሕአዲጉ ሊቀ መንበር ሲቀነቀን፣ ተቃዋሚዎች አጀንዳ አጥተዋል። የድንጋጤያቸው ምንጭም ይኸው ይመስላል። በርግጥ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ሲያልፉበት ከነበረው ፈታኝ ሁኔታ አንፃር በመዳከማቸው የፖለቲካ ለውጦችን እያዩ ከወቅቱ ጋር የሚሔድ ፖለቲካ መጫወት ቢያቅታቸው የሚገርም አይደለም። 

የፖለቲካ ድርጅቶቹ "የአኩራፊዎች እና የጡረተኞች መሰብሰበቢያ" እየተባሉ ሲተቹ ከርመዋል። ምንም እንኳን ከላይ ያሉ ቢመስልም ውስጣቸው በብዛት ባዶ ነው። ለኢትዮጵያ (100 ሚሊዮን ሕዝብ) የሚመጥን የመምራት አቅም ያላቸው ሰዎች ስብስብ የላቸውም። በመገናኛ ብዙኃን በሚራገቡ አጀንዳዎች ላይ የመንግሥትን አቋም ካወቁ በኋላ ተቃራኒውን ይዘው ከመሟገት በላይ ርዕዮተ ዓለማዊ አቅጣጫ የሌላቸው ድርጅቶች ቀላል አይደሉም። አንዳንዶቹ ከላይ ያሉትን ታዋቂ ሊቀ መንበሮቻቸውን የሚተኩ አባላት እንኳን አላፈለቁም። ኢትዮጵያን መምራት የሚችሉ በርካቶች ድግሞ ወይ የፖለቲካውን ትኩሳት እየፈሩ አንገታቸውን ደፍተው 'ዝምተኛ-ብዙኃን' መሐል ተቀብረዋል፤ አልያም ተሰድደዋል። በዚህም ምክንያት ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶቹ የኢሕአዴግ የፖለቲካ አጨዋወት ሲቀየር፣ የራሳቸውን አጨዋወት በመቀየር ፈንታ ድንጋጤ ውስጥ መግባታቸውን የሚያሳብቁ ነገሮች ናቸው አሁን የሚታዩት። "እስረኛ የፈቱት ወደው ሳይሆን ተገደው ነው"፣ "ሰውዬው ኢሕአዴግ ናቸው፣ ኢሕአዴግ ከሚቀየር ግመል በመርፌ ቀዳዳ…"፣ "ጥቂት ሰዎች ተቀየሩ ማለት ነገሮች ተቀየሩ ማለት አይደለም"፣ "ይች ይቺ ተቃውሞ ለማስቆም የተፈጠረች የኢሕአዴግ ሴራ/ድራማ ናት"… እነዚህ ንግግሮች ለቀጣዩ የፖለቲካ ጫወታ ፋይዳቸው ምን እንደሆነ ሊገባኝ አይችልም። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በእያንዳንዱ ንግግራቸው እና ድርጊታቸው የብዙዎችን ቀልብ እየገዙ እና "አለቀለት" ለተባለው ኢሕአዴግም አዲስ ነፍስ እየዘሩበት ነው። ይህ የገባቸው ተቃዋሚዎች የማጥላላት እና የማጣጣል ትርክት ለመፍጠር እየተፍጨረጨሩ ነው። ይህ ፖለቲካዊ ኪሳራ ሊያስከትል ይችላል።  የሴራ ፖለቲካዊ ትንተና እና ጫወታም መሬት ላይ ጠብ የሚያደርገው እንደሌለ ከበቂ በላይ ታይቷል። የብሽሽቅ ፖለቲካም ጉንጭ ከማልፋት በላይ ትርፍ የለውም። ሕዝብን "ተታልላችኋል" እያሉ መውቀሱም አግባብ አይደለም። ምክንያቱም ሕዝቡ የሚያየውን መዳኘት ይችላል።

ይልቁንም (በፖለቲካ ምኅዳሩ መጥበብ ምክንያት የተከተለው እና ሁለተኛው ደረጃ) "የማማረር ፖለቲካ" ተላቅቆ፣ ወደ አንደኛው ደረጃ ፖለቲካ ማለትም አማራጭን የማሳየት እና ሕዝባዊ መሠረት የመጣል ፖለቲካ መጫወት ያስፈልጋል። የፖለቲካ ምኅዳሩ ለይቶለት ሳይዘጋ በፊት ለእስር እና ስደት የተዳረጉት ፖለቲከኞች ጥያቄ ምንድን ነበር? የሕዝቦች ጥያቄ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ደኅንነት እንዴት ነው የሚጠበቀው? ድንቁርና እና ድህነትን እንዲሁም ኢፍትሓዊነትን ለመቀነስ አገራችን ምን ዓይነት የፖለቲካ ስርዓት መከተል አለባት? አሁን ሰዐቱ ይህንን የመመለስ ነው። 

የፖለቲካ ድርጅቶች የሚሠሩት ሥራ በየአደባባዩ ሰልፍ ከመውጣት እና የተቃውሞ መግለጫዎችን ከማውጣት በላይ ነው። አብላጫ የምክር ቤት ወንበር አግኝተው መንግሥት ሲመሠርቱ ብቻ ሳይሆን፣ እንደ አማራጭ በመኖራቸው ብቻ የሚሠሯቸው ሥራዎችም ብዙ ናቸው። በዋነኝነት አማራጭ የአገር አመራር አቅጣጫ ማሥመር አለባቸው። አገሪቱ ወዴት ነው መሔድ ያለባት? እንዴት ነው ወደዚያ መሔድ የምትችለው? የሚሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚያስችሉ የማኅበረ–ኢኮኖሚያዊ ፍልስፍናቸውን ለሕዝብ ማስተዋወቅ አለባቸው። ለዚህ ደግሞ ብቁ የሆኑ አመራሮችን መሰብሰብ እንዲሁም እየኮተኮቱ ማሳደግ አለባቸው። አለበለዚያ እንደሥማቸው ተቃዋሚ ብቻ ሆነው ይቀራሉ። 

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ "ተፎካካሪ" የሚለውን መጠሪያ እንደአስታራቂ መርጠዋል። እኔ እስካሁን ያለውን ፖለቲካ የገዢ እና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፖለቲካ ብለው እመርጣለሁ። ምክንያቱም ገዢው ፓርቲ አገር ለመምራት ወይም ሕዝብ ለማገልገል ሳይሆን ፈላጭ ቆራጭ ገዢ ለመሆን ነው ሲተጋ የኖረው። ተቃዋሚዎች ደግሞ የገዢውን አገዛዝ ሲቃወሙ እዚህ ደርሰናል። ኢሕአዴግ መቀ:የር እፈልጋለሁ ብሎ ጭላንጭል ሲያሳይ፣ የነገውን ለነገ ትተው ተቃዋሚቹም መቀየር አለባቸው። እውነተኛ አማራጭነታቸውን ለማሳየት አጋጣሚውን መጠቀም ይኖርባቸዋል። አለበለዚያ ነገ ኢሕአዴግ ስህተት እስኪሠራ ጠብቆ "ይኸው ይሄንኑ ፈርተን ነበር" ማለት አያዋጣም፤ በሥሙ ብዙ ነገር ለሚፈፀመው ሕዝብም የሚያተርፍለት ነገር የለም። ምንም እንኳን ወደፊትም የመሔድ ወይም ወደ ኋላ የመመለስ ዕድሉ ዕኩል ቢሆንም አሁን (በዚህ ቅፅበት) ከሞላ ጎደል ሰፊ የፖለቲካ ምኅዳር አለ። የፖለቲካ ምኅዳሩ ስፋት ወደኋላ እንዳይመለስ ሕጋዊ እና ተቋማዊ መሠረት አፍርቶ ለዘለቄታው ዋስትና እንዲያገኝ ከመሥራት ጎን ለጎን አማራጭ የፖለቲካ መፍትሔን ለሕዝብ ማስተዋወቅ ያስፈልጋል። ሕዝብ ውስጥ የሰረፀ ፖለቲካዊ የመፍትሔ ሐሳብ ካለ፣ አመንጪዎቹ የፖለቲካ ድርጅቶች ባይኖሩም እንኳን የግዜ ጉዳይ ቢሆን ነው እንጂ ግቡን ይመታል።

አማራጭ የፖለቲካ ሐሳብ ያላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ካሉ እኛም "ገዢ" እና "ተቃዋሚ" እያልን ከመፈረጅ እንገላገላለን። "ተፎካካሪ" ከሚለው እና የሥልጣን ሽሚያን ብቻ ከሚጠቁመው ቃልም ይልቅ "አማራጭ" የፖለቲካ ድርጅቶች የሚለውን እንጠቀማለን። አማራጭ የፖለቲካ ድርጅቶች ካሉ፣ የድርጅቶቹን ሥም ስንሰማ የገዢውን ሐሳብ በመቃወማቸው ሳይሆን፣ በአማራጭ ሐሳባቸው እናስታውሳለቸዋለን። 'ምረጡን' ብለው ሲመጡም እንደተቃዋሚ "ተቃውሟቸውን" ወይም እንደ ተፎካካሪ "ፉክክራቸውን" ሳይሆን አማራጭ ሐሳባቸውን እንመርጣለን። 

Time to move on, and choose your place in the board.