Pages

Sunday, July 22, 2012

የእንቆቅልሹ እንቆቅልሾች


ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ምኒልክ ሲሞቱ፣ መኳንንቱ ለሕዝቡ የ‹እምዬ›ን ሞት ለማርዳት ፈርተው ዓመታት ቆይተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊስ ዳግማዊው ‹ዳግማዊ-ምኒልክ› ለመሆን በቅተው ይሆን እንዴ? ይህቺን ጽሁፍ እስካሰናዳሁባት ሰዓት ድረስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልካም ጤንነት ላይ ናቸው፣ በጠና ታመዋል እና ሞተዋል የሚሉ ‹‹ታማኝ ምንጮች›› ከየአቅጣጫው እየፈለቁ ነው፡፡ እውነታውን ምሎ የሚናገር ሕዝብ ወይም የሕዝብ አባል ግን የለንም፤ ጉዳዩ በእንቆቅልሽ የተሞላ ነው፡፡

አሁን፣ አሁን ገዢው ፓርቲ የራሱ ዋሾነት ሳያንሰው የአማራጭ መረጃ ምንጮችን ታማኝነት እስከወዲያኛው ለማድረቅ ሆነ ብሎ የሚጫወተው ‹ጌም› ያለ እየመሰለኝ መጥቷል፡፡ በ‹‹ታማኝ ምንጮች›› በኩል የሐሰት መረጃዎችን ማፍሰስ፣ በጣም እስኪናፈሱ መጠበቅ፣ ወሬዎቹን በከፊል የሚያረጋግጡ መግለጫዎችን መስጠት፣ መጨረሻ ላይ ግን ወሬዎቹ በሙሉ ‹‹ከአሉባልታ›› ያልበለጡ መሆናቸውን አረጋግጦ የዜና ምንጮቹን ተአማኒነት መግደል፡፡ ለኔ፣ መለስ ቢያንስ በቅርቡ ወደቢሯቸው መመለስ ከቻሉ ተናፋሽ ወሬዎችን ለማመን ይሄ የመጨረሻዬ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ከዚያ በፊት የዚህ እንቆቅልሽ እነቆቅልሾች ስለሆኑት ነገሮች ትንሽ ልበል፡፡

Tuesday, July 10, 2012

እውነቱ እና ፍርሃቱ


የፍራቻ ፖለቲካ እና የፖለቲካ ፍራቻ - ጥንድ በኢትዮጵያ መሪዎችና ሕዝቦች መሀል የተጋረጡ የጦር መሳሪያዎች ናቸው፡፡ ሕዝቡ ካልፈራ ፖለቲከኞቹ የፍራቻ ፖለቲካ ይጫወታሉ፣ ፖለቲከኞቹ የፍራቻ ፖለቲካ ካልተጫወቱ ሕዝቡ ፖለቲካን ይፈራል፡፡ የሁለቱም ውጤት አንድ ነው፤ ውጤቱም ሕዝቡ መሪዎቹን የሚያስከፋ ነገር መናገርም ሆነ መተግበር ይፈራል፡፡

የፍራቻ ፖለቲካ፤ በገዢው እና ተቃዋሚዎቹ
ጥንት፣ ወትሮም ንጉሥ የማይከሰስ በመሆኑ መንግስታት ሕዝቦቻቸውን ማስፈራራታቸው የደንብ ያህል ነበር፡፡ ‹‹የተማረ ይምራን›› መባል ከተጀመረበት እና ደርግ የንጉሡን መንበር ከተረከበበት ጊዜ ወዲህም ግን ‹‹ደንቡ›› አልቆመም፡፡ ደርግ ‹‹አብዮቱን›› ሊቀለብሱ የሚንቀሳቀሱትን በሙሉ እንደማይምራቸው በሕዝብ ፊት ምሎ ዘመተባቸው፡፡ አብዮቱን ከሚቀለብሱት እንዳንዱ ላለመሆን የፈራ በሙሉ የኢሠፓ አባል ሆኖ በወንድሙ ላይ ዘመተ፡፡ ቀሪው ‹‹መሀል መስፈር›› የፈለገውም፣ ከፍራቻው’ጋ እንደተሟገተ 17 ዓመታት ኖረ፡፡

ኢሕአዴግ ቀርቶ የፍራቻ ፖለቲካ የቀረ ከመሰለ በኋላ ግን መልኩን ቀይሮ መጣ፡፡ አብዮቱን መቀልበስ፣ ሕገመንግስቱን መቀልበስ በሚል ተተካ፡፡ መንግስት የተቃወመውን ሁሉ በሆነ ስም በመፈረጅ ስለሚወነጅል፣ ላለመፈረጅ የሚሰጋው ሁሉ ወደወጣበት ምሽግ ተመልሶ ገባ፡፡ ‹‹ፖለቲካ እና ኮረንቲ›› የሚለው አባባል የተፈጠረው ያኔ ነው፡፡

የፍራቻ ፖለቲካን፣ ኢሕአዴግ በሌላም አካሔድ ይጫወትበታል፡፡ እንደገዢው ፓርቲ ዲስኩር ከሆነ፣ ኢሕአዴግ ከወረደ ወይም ተቃዋሚዎች ወደስልጣን ከወጡ የብሔር ብሔረሰቦች ጥያቄ/ነፃነት ተዳፍኖ ይቀራል፣ የሃይማኖቶች እኩልነት አደጋ ላይ ይወድቃል፣ ልማቱ ይደናቀፋል… ወዘተ፣ ወዘተ፡፡

Wednesday, July 4, 2012

የባለፀጋዋን አገር ዜጋ፤ አቶ ድህነትን እናስተዋውቅዎ


ከዕለታት አንድ ቀን ከምሣ መልስ ቡና የምጠጣበት ካፌ ተሰይሜያለሁ፡፡ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የአዲስ አበባ መስተዳደር ፕሮግራም ይተላለፋል፡፡ ፕሮግራም አቅራቢያዋ በእኛ ቲቪ ያልተለመደ ዓይነት ፕሮግራም እያቀረበች ነው፡፡ አንዷ መምህርት ትናገራለች ‹‹ልጆቹ ራሳቸውን ይስታሉ›› አለች፡፡ ልጆቹ ያለቻቸው እሷ የምታስተምርበት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያሉ ተማሪዎችን ነው፡፡

‹‹እናነሳቸውና ካፌ ወስደን ውሃ አጠጥተን፣ ዳቦ አብልተን ስንለቃቸው ደህና ይሆናሉ፤›› አለች መምህርቷ፡፡ ‹‹በኋላ ላይ ሲደጋገምብን ጠይቀናቸው- ለካስ የሚወድቁት ምግብ ከበሉ ሁለት ሦስት ቀን እየሆናቸው ነው፡፡››

ያንን ፕሮግራም ተመልክተው ከእንባቸው ጋር ያልታገሉ ሰዎች አልነበሩም፡፡ ሕፃናቱ በተለያዩ ምክንያቶች ከወላጆቸቸው የተነጠሉ ሲሆኑ፣ ያልተነጠሉትም ቢሆኑ ቤተሰቦቻቸው በየቀኑ የመመገብ አቅም የሌላቸው ነበሩ፡፡ የኋላ ኋላ በደረሰኝ መረጃ ያንን ፕሮግራም ያቀረበችው ጋዜጠኛ ‹‹በመርዶ ነጋሪነት›› ከአለቆቿ ተግሳፅ ደርሶባታል፡፡