Pages

Saturday, April 30, 2011

ከሠራተኛ፣ ለማኝና ቀማኛ ማነው በላተኛ?


እንዲያው ለመንደርደር ያህል ‹‹ከለማኝና ከቀማኛ የቱ ይሻላል?›› ተብላችሁ ብትጠየቁ መልሳችሁ ምን ይሆናል? ነገሩ ከሁለት መጥፎ ነገሮች የተሻለ መጥፎ መምረጥ ነው፡፡ (የተሻለ መጥፎ ስንል ጉዳቱ ያልከፋ እንደማለት ነው፡፡) ስገምት፥ ብዙዎቻችሁ ለማኝ የምትመርጡ ይመስለኛል፤ ግን ለማኝ ከቀማኛ በምን ይሻላል? ሁለቱም የሰው ገንዘብ ፈላጊዎች አይደሉም?

ጨዋታን ጨዋታ ያነሳዋል እንዲሉ፣ አንዴ የታዘብኩትን ላውጋችሁ፡፡ ከእለታት አንድ ቀን፣ ከአንድ ካፍሬተሪያ በረንዳ ላይ ቁጭ ብዬ ማኪያቶ እየጠጣሁ እቆዝም ነበር፡፡ ከፊት ለፊቴ ታክሲ ተራ አለ፡፡ ታክሲው ተራ አካባቢ፥ ከባለታክሲዎቹ ውጪ የዕለት እንጀራቸውን ለማግኘት የሚራወጡ ሦስት ተዋናዮች ነበሩ - ተራ አስከባሪው፣ ለማኝ እና ማስቲካ ቸርቻሪ፡፡

Friday, April 29, 2011

ኢትዮጵያ የኢስላምም የክርስቲያንም ደሴት ናት


የእስልምና እምነት ተከታይ አይደለሁም፤ ለነገሩ የክርስትና እምነት ተከታይም አይደለሁም፡፡ ነገር ግን ዛሬ ሙስሊም ሆኜ ሳስበው ‹‹ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ናት›› የሚለው ቃል ሳስበው ከፋኝ፡፡ ኢስላም እና ክርስቲያን ተጣጥመው በአንድ ጣሪያ ስር የሚያድሩባት እየተባለች የምትሞገሰው ኢትዮጵያ ውስጥ ‹‹ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ነች›› የሚል ቲሸርት ለብሶ መሄድ የፀብ አጫሪነት ጠባይ ነው፡፡ ይሄ ብቻም አይደለ፤ አሁን አሁን የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችን ትኩረት በሚስብ መልኩ በምዕራብ ኦሮሚያ ቤተክርስቲያናት እየተቃጠሉ፣ ክርስቲያኖች እየተሰደዱ ነው - ይህንንም ክርስቲያን ሁኜ ሳስበው ያስከፋል፡፡

Tuesday, April 12, 2011

አማርኛ ሃይማኖቱ ምንድን ነው?

አማርኛ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቋንቋ የሚል ማዕረግ ባይኖረውም፣ የፌዴራል መንግስት የስራ ቋንቋ ነው፡፡ ልክ ከ፹ በላይ እንደሆኑት ቋንቋዎቻችን ሁሉ
ኢትዮጵዊነት በአማርኛ፣ አማርኛም በኢትዮጵያዊነት ይገለፃሉ፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ በሃይማኖት መቻቻል አንቱ የተሰኘች ሃገር ናት - ‘ተብሏል፣ ብለናል፣ አስብለናል፡፡’ ታዲያ አማርኛስ ምን ያህል የሃይማኖታዊ መቻቻል ‘ሙድ’ ገብቶታል? ‘እንጠይቃለን፣ እንመልሳለን፡፡’
1 - ሠላምታ
‘ጤና ይስጥልኝ’ በሚለው የኢ-አማኒ ጓዶች ተመራጭ አማርኛ እንኳን ብንጀምር በውስጡ ሰጪ አለ፡፡ ስለዚህ አማርኛ ሃይማኖት ባይኖረው እንኳን እምነት እንዳለው ከአጀማመራችን እንረዳለን፡፡ ስንቀጥል፡- ‘እንደምን አደርክ፣ ዋልክ?’ ለሚለው ምላሹ ‘እግዚአብሔር ይመስገን’ ይሆናል፡፡ አሁን አማርኛ ክርስቲያን ነው ለማለት የሚያስችል ፍንጭ መረጃ አገኛችሁ ማለት አይደለም? ክርስቲያን ያልሆኑ አማርኛ ተናጋሪዎች የአምላካቸውን ስም ተክተው ሊናገሩ ይችላሉ ግን አማርኛ አይመስልም፡፡ ‘ደህና’ የሚል ምላሽ ብቻ ብትሰጡ ደግሞ ባዶ ይመስላል፡፡ እኔ ለሰላምታ ‘ደህና’ የሚል ምላሽ አዳብሬያለሁ፡፡ ሰዎች ግን ‘ደህና’ የሚለውን ቃል በጥርጣሬ ነው የሚያዩት - ‘ደህና አይደለህም እንዴ?’ ደህንነት በአማርኛ በ‘እግዚአብሔር ይመስገን’ ብቻ ነው የሚረጋገጠው፡፡ ስለዚህ የታከተኝ ጊዜ ‘ኧረ ደህና ነኝ! እግዚአብሔር ይመስገን’ ብዬ እገላለገላለሁ፡፡

2 - መልካም ምኞት መግለጫ
ኢ-አማኒ የአማርኛ ተናጋሪ የመልካም ምኞት መግለጫ እጥረት አይቸግረውም፡፡ ከ‘እንኳን ደስ አለሽ/አለህ’ በስተቀር ሌላ ሃይማኖት ቀመስ ያልሆነ ቃል/ሐረግ የለም፡፡ ‘እንኳን ደስ አለሽ/አለህ’ ደግሞ ለተሳካ ጉዳይ ብቻ ነው፡፡ በርግጥ ‘ይቅናህ’ የሚል ቁጥብ አማርኛም አለ፡፡ ቁጥብ ያልኩት እሱም ቢሆን በውስጡ ‘እንዲሳካልህ ያድርግልህ’ የሚል አገባብ ስላለው ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ግን ‘እንኳን አደረሰሽ/አደረሰህ’ - አድራሽ ኃይል ያለበት መተኪያ የሌለው አማርኛ ነው፡፡ መልሱ ደግሞ ‘እንኳን አብሮ አደረሰን’ ነው - ለማያምኑ ሰዎች ግን ‘ማን ነው ያደረሰኝ?’ ዓይነት ጥያቄ ማጫሩ አይቀርም፡፡

ከመልካም ምኞት መግለጫ ጋር በተያያዘ አማርኛ አንዳንዴ ከክርስትናም መርጦ ኦርቶዶክስ የሚሆንበት አጋጣሚም አለ፡፡ ለምሳሌ ‘እንኳን ማርያም ማረችሽ! - ማርያም በሽልም ታውጣሽ፡፡’ አራስ መጠየቂያና መሰናበቻ አማርኛ ነው፡፡ ‘ማርያም ታኑርሽ/ታኑርህ’ ደግሞ የአራሷ መልስ፡፡

3 - ማፅናኛ
ሃይማኖተኛ ያልሆነ የአማርኛ የማፅናኛ ቃል ማግኘት የምንግዜም ፈተና ነው፡፡ ሰው አንድ ችግር ገጥሞት ወይም ታምሞ መጠየቅ ካለባችሁ፣ የምትጠቀሙት አማርኛ ‘እግዚአብሔር ይርዳህ፣ እንኳን እግዚአብሔር አተረፈህ፣ እግዚአብሔር ይማርህ፣እግዚአብሔር ያውቃል’ እና የመሳሰሉት ሐረጎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ቃላቶች ለአማኙ ሰው ተስፋ ሰጪ ናቸው፤ ምንም መፍትሄ ሳትሰጡ እንደመፍትሔ ሰጪ ያስቆጥሯችኋል፡፡ እነዚህን ቃላት አለመጠቀም ደግሞ ከችግሩ ተካፋይነት ይልቅ በችግሩ አካልነት ሊያስፈርጃችሁ ይችላል፡፡ በተለይ ኢ-አማኒ ለሆነ ሰው ቃላቱ የሽንገላ ያህል ለሚወዱት ሰው መናገር ለአፍ ይከብዳል፡፡ እኔ በበኩሌ አማኝ ባልሆንም ቅሉ አንዳንዴ፣ ቢያንስ አማኙ ስለሚያምንበት ቃላቱን ተናግሬ ‘ሸነገልኩት’ ብዬ መፀፀትን እመርጣለሁ፡፡

ሌላም፣ ሌላም፡- ምስጋናው ‘እግዚአብሔር ይስጥልኝ’፣ ምርቃቱ ‘እግዚአብሔር ይማርህ’፡፡ በጥቅሉ ቋንቋው ከሃይማኖታዊ አስተሳሰብ ጋር ያለውን ቁርኝት በማየት ብቻ ጥሩ ወይም መጥፎ ብሎ መፈረጅ አይቻልም፡፡ ሆኖም የግል እምነትን ወይም ፍልስፍናን የሚደግፍ ነው ለማለትም ይከብዳል፡፡ ይህ መሆኑ ግን አማርኛን ጎዶሎ ያደርገዋል ማለት አይደለም፤ አማርኛ እንደማንኛውም ቋንቋ ሙሉ ነው - ሃሳብን ከመግለፅ አንፃር፡፡

አሁን እያወራን ያለነው ስለአማርኛ ቋንቋ ብቻ ባይሆን ኖሮ ሩቅ ሳንሄድ የእንግሊዝኛዋን ‘Oh my God’ ብንመለከት እንኳን መተኪያ የሌላት ምርጥ ሐረግ እንደሆነች በማሰብ ችግሩ የአማርኛ ቋንቋ ብቻ አለመሆኑን ማስታወሳችን አይቀርም ነበር፡፡ አንዳንዴ በስምምነት ሃይማኖታዊ ይዘት ያላቸውን ቃላት ከመንፈሳዊ ይዘታቸው አንፃር ሳይሆን ስሜታችንን ከማስተላለፍ አቅማቸው አንፃር ብቻ ብንጠቀምባቸው ምንም ችግር የለውም - ልክ ታላቁ የፊልም ሰው ሉዊስ ባኑኤል እንዲህ እንዳለው ‘Thank God I’m an Athiest’፤ ችግሩ ሃይማኖተኛ ያልሆንን ሰዎች ቋንቋችን ውስጥ ሃይማኖት ሲገባ ይከፋናል፡፡

ይሄ በሰፊ ጥናት ሳይሆን በቅፅበታዊ የሐሳብ ምልልሶሽ ላይ የተመሰረተ መደዴ ድምዳሜ ነው፡፡ ጠለቅ እያላችሁ ብትሄዱ ግን ሌላም፣ ሌላም ሃይማኖተኛ አማርኛዎችን ከየንግግራችሁ መሃል ትለቅማላችሁ፡፡ ለምሳሌ ‘Nature’ የሚለውን የእንግሊዘኛ ቃል የሚተካ አማርኛ ቃል አፋልጉኝ፡፡ የለም፡፡ የግድ መተርጎም ሲኖርብን እንኳን ‘ተፈጥሮ’ ብለን ነው የምንተረጉመው፡፡ የተፈጠረ (ፈጣሪ ያለው ነገር) ብለን::

በአንድ ወቅት አንድ አሜሪካዊ ምሁር ባደረጉት ጥናት አማርኛ ቋንቋ የመቻቻል ፖለቲካን የሚያበረታቱ ቃላት እጥረት እንዳለበት በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡ በእዚችኛዋ የእኔ ፅሁፍ ደግሞ አማርኛ የፓለቲካ ብቻ ሳይሆን የሃይማኖታዊ መቻቻልን የሚያበረታታ ቃላት እጥረት አለበት ይሆን? እያልኩ እጠይቃለሁ፡፡ “A language can tell us what is important in a particular culture.” (ቋንቋ በአንድ ባሕል ውስጥ ተፈላጊነት ያለውን ነገር ይነግረናል) ይለናል አንትሮፖሎጂስቱ ማካን ጃ - ሶሻል አንትሮፖሎጂ በተሰኘው መፅሃፉ ስለቋንቋና የማሕበረሰብ አስተሳሰብ ቁርኝት ሲያወራ፡፡


እኔም እንደኔ በመጨረሻ አማርኛ ክርስቲያን ነው፤ ያውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ በማለት አራት ነጥቤን አስከትላለሁ፡፡

አማርኛ፣ ኣማርኛ፣ ዐማርኛ ወይስ ዓማርኛ?

በበፍቃዱ ኃይሉ -
“እዚህ ግቢ የሚሸጥ ዕንጀራ አለ” የሚል ፅሁፍ አንድ ግቢ በር ላይ ተፅፎ ባላይ ኖሮ ይህንን ፅሁፍ ለመፃፍ አልነሳሳም ነበር፡፡ ማስታወቂያውን አንብቤ ስጨርስ የሆነ ነገር እንደጎደለው ተሰምቶኝ ደግሜ አስተዋልኩት፡፡ እርግጥ ነው ዕንጀራ የሚለው ቃል ውስጥ ያለችው ዕ” ለቃሉ ተስማሚ ትክክለኛዋ ሆሄ አልነበረችም፡፡ ለቃሉ ሌላ ትርጉም ባትሰጠውም ቅሉ እኔን ለማደናገር ያክል ግን በቅታለች፡፡

አማርኛ ቋንቋ የ“ግዕዝ” ፊደላትን መጠቀሙ ያጎናፀፈው ፀጋ ለእያንዳንዱ ድምፅ አንድ ሆሄ ማስቀመጡ ብቻ አይደለም፡፡ አንዳንድ ድምፆች እንዲያውም ትርፍ ሆሄያት አሉዋቸው፡፡ እነዚህ ሆሄያት ከልምድ ብዛት ከቃላቱ ጋር ይዋሃዱ እና በአእምሮአችን ይታተማሉ፡፡ ከላይ እንደገለፅኩት፤ ምናልባት መንትያቸው ተተክቶባቸው ያነበብናቸው ግዜ ልክ የቃላቱ ትርጉም የተለወጠ ያህል ግር ይለናል፡፡ ይሄ ግን ዛሬ፣ ዛሬ በብዙ ወጣቶች ላይ የሚስተዋል ነገር አይደለም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ወጣቶቹ በአማርኛ አፃፃፍ ክህሎታቸው ስለበፀለጉ አይደለም፡፡ ብዙዎቹ እንኳንስ ለሆሄያት ግድፈት ሊጨነቁ ይቅርና ዓረፍተ ነገሮቹን ለዛ ባላቸው መንገድ ገጣጥመው ለመፃፍም እየተቸገሩ ይገኛሉ፡፡ ለምን?

እንዳለመታደል ሁኖ ከላይ ላነሳሁት ጥያቄ ፈጣን ምላሽ የሚሰጠኝ የምርምር ፅሁፍ አጠገቤ አላገኘሁም፡፡ ይሁን እንጂ እኔ በጥያቄው ላይ የራሴን መደዴ መላምት ማስቀመጤ አልቀረም፡፡ ከነዚህም ውስጥ፡-
  • ለአማርኛ ትምህርት የተሰጠው ትኩረት አናሳነት፣
  • የግዕዝ ሆሄያት መብዛት እና
  • የፊደሎች ድግግሞሽና የድግግሞሹ ፋይዳ ማጣትን እንደዓቢይ ምክንያቶች ወስጃቸዋለሁ፡፡

፩ኛ - አማርኛ ለምኔ?
በአገራችን አማርኛ ቋንቋ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የሥራ ቋንቋ እንደሆነ በአዋጅ ቢቀመጥም በአፍቃሬ እንግሊዘኛ ትውልድ ቅኝ ግዛት ስር መውደቁን ለመረዳት ብዙ ማሰብ አያስፈልግም፡፡ በጉራማይሌ ከሚደጎመው ንግግር እስከተደበላለቀው የታናሽ እህት ወንድሞቻችን የአማርኛ ፅሁፍ ዋቢ መጥቀስ እንችላለን፡፡ ትምህርት ቤቶች ቢያንስ “በእንግሊዘኛ ተነጋገሩ” ማለት ሲቻል “በአማርኛ አትነጋገሩ” ብለው የግቢያቸው ማስታወቂያ ሠሌዳዎች ላይ እስከመለጠፍ ደርሰዋል፣ እንግሊዘኛ ተናጋሪዎች እንደሁሉን ቻይ እየተቆጠሩ ነው፣ በጥቅሉ ትውልዱ ለአማርኛ የሚሰጠው ዋጋ ወርዷል ብዬ አምናለሁ፡፡

ለዚህ እንደዋነኛ መንስኤነት የምኮንነው ለአማርኛ ቋንቋ ትምህርት የተሰጠውን አናሳ ትኩረት ነው፡፡ ምንም እንኳን አማርኛ የብዙዎቻችን አፍ መፍቻ ቋንቋ ቢሆንም በምርምር (በትምህርት) ብቻ የሚስተዋሉ የራሱ የሆኑ ሕግጋት እና አላባውያን ያሉት መሆኑ እየታወቀ የመንግስትም ሆነ የግል ትምህርት ቤቶች ወጣቶች ከቋንቋው ጋር በፍቅር እንዲወድቁ ትኩረት ሰጥተው አለመስራታቸው፣ ተማሪዎችን በቋንቋ አጠቃቀማቸው እና በፊደል አጣጣላቸው ጫን ያለ አስተያየት አለመስጠታቸው አማርኛ ለምኔ ትውልድ ሊያፈራ በቅቷል፡፡

ቋንቋ ሁሉ ሙሉ ነው ከሚለው ኀልዮት በተፃራሪ አማርኛ ቋንቋ የመግለፅ አቅም እንደሚያጥረው የሚከራከሩ ሰዎችም እየተበራከቱ ናቸው፡፡ ለዚህ እንደምክንያት የሚጠቅሱት በከፍተኛ ፍጥነት እየበለፀገች ያለችው ዓለማችን በየጊዜው አዳዲስ ቴክኖሎጂ አፈራሽ ምርቶችን ታስተዋውቀናለች፡፡ ለነዚህ ፈጠራዎች ከስያሜ አንስቶ አሰራራቸውን ለመግለፅ የሚያስችል እድገት ግን በቋንቋው ላይ አለመስተዋሉን ነው፡፡ ቋንቋውን ከኋላ ቀርነት ጋር ተጣብቆ የቀረ አድርገው እንዲያስቡትም የሚያደርጋቸው ይኸው ነው፡፡ በዚህ ረገድ የሚመለከተው አካል የሚታይ ስራ የሚሰራ የትርጉም ተቋም ሊኖረው ይገባል፡፡

ቋንቋን መውደድ ባሕልን ብሎም አገርን መውደድ ነው፡፡

፪ኛ - ተዘግኖ የማያልቅ የሆሄያት ገበታ
በአማርኛ ቋንቋ ያሉት የሆሄያት ብዛት አጠያያቂ አይደለም - ብዙ ናቸው፡፡ ከአማርኛ ይልቅ ለግዕዝና ትግሪኛ የበለጠ የሚያገለግሉትንም ከቆጠርን የፊደል ገበታው ከሦስት መቶ የሚበልጡ ሆሄያትን ይዟል፡፡ ለዚህም ይመስላል ከ‘ሀ’ እስከ ‘ፐ’ ያሉትን በቅደም ተከተል አስታውሶ መጥራት ለብዙዎቻችን ፈተና የሚሆንብን፡፡ ይሁን እንጂ አሁንም በየቦታው እየተስተዋሉ ያሉት ተግዳሮቶች ፊደላቱን የመቁጠር አይደለም፡፡ የቋንቋውን ሆሄያት የማምታታት እና የማሳሳት ፈተናዎች ናቸው፡፡ ከሁሉም አሳፋሪ የሚሆነው ደግሞ ግድፈቶቹ እየታዩ ያሉት ወጣቶችን በሚቀርፁ የሕትመት ስራዎች እና ሚዲያዎች ላይ ሳይቀር መሆኑ ነው፡፡

‘ፓ’ን በ‘ፖ’ ማቀያየር የተለመደ ከመሆኑ የተነሳ በተለያዩ ጋዜጦችና በኢትዮጵያ ቴሌቭዥንም ጭምር “ስፖርት” ተብሎ ሊፃፍ የሚገባው “ስፓርት” እየተባለ ሲፃፍ በተደጋጋሚ ታዝበናል፡፡ ይህ እንግዲህ የቋንቋው ሆሄያት በራሳቸው የፈጠሩት ተግዳሮት ነው፡፡ እነዚህ ፊደላት በማሽን በተለቀመ ፅሁፍ ውስጥ በቀላሉ የሚለዩ ቢሆኑም በእጅ ጽህፈት ላይ ረቂቅ የስዕል ችሎታ እንዲኖረን አስገዳጅ ዓይነት ነው፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ በተለይ በነዚህ ሁለት ፊደላት (‘ፓ’ እና ‘ፖ’) እና መሰሎቹ (‘ጸ’ እና ‘ደ’፣ ‘ኘ’ እና ‘ፕ’) መካከል ያለውን ልዩነት ከሰው ሰው በሚለያይ የእጅ ፅሁፍ ውስጥ በአግባቡ እንዲታይ መጠበቅ የዋህነት ነው፡፡ እስከዛሬም ቢሆን ፊደላቶቹን የምንረዳቸው በአገባባቸው ነው፡፡ ይህ ግን በሕትመት ስራዎች ላይ የሚጠበቅ አይሆንም - በስነፅሁፍ ስራዎች ላይ ሲከሰት ደግሞ አሳፋሪ ይሆናል፡፡

አንዳንድ ጊዜ ግን የማይምታቱትን የማምታታት አባዜም የሚደጋገሙባቸው አጋጣሚዎች አሉ፡፡ አንዳንዶች በሻ እና ሾ፣ በባ እና ቦ፣ በካ እና ኮ እና በሌሎችም መካከል ያለውን ልዩነት መረዳት የእድሜ ልክ ዳገት ይሆንባቸዋል፡፡ የእነዚህን ፊደላት ቅርፅ ለመለየት ምንም ጥበብ አያስፈልገውም፡፡ መሰረት የሚጥል የአስተምሕሮ አካሔድ በመዋዕለ ሕፃናት ደረጃ ማስቀመጥ በቂ ይመስለኛል፡፡
፫ኛ - ድምጾች፣ ፊደላቸውና ድግግሞሹ
የአማርኛ የፊደል ሆሄያትን ድግግሞሽ የተመለከቱ ጉዳዮችን ሳነሳ አንዳንድ የእንግሊዘኛ ተናጋሪዎች የአናባቢ ፊደላት አላግባብ መብዛትን በመቃወም የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አስታውሳለሁ፡፡ እነዚህ ሰዎች አላግባብ የተደነቀሩ አናባቢዎች አስፈላጊ አይደሉም ጊዜም ይፈጃሉ ስለዚህ ተወግደው ቃላቱ ነፃ መውጣት አለባቸው ባይ ናቸው፡፡ ለእንቅስቃሴያቸውም እንደ መሪ ቃል የሚጠቀሙበት “Enough is enuf!” የሚል መፈክር ነው - ችግሩን ከነመፍትሄው በአጭሩ የሚያሳይ መፈክር፡፡

የአማርኛ ቋንቋ ፅሁፍ ምንም እንኳን ከአናባቢዎች ተለጣፊነት የተላቀቀ ቢሆንም የራሱ የሆኑ ድክመቶች አብረውት ይኖራሉ፡፡ ቋንቋ ይወለዳል፣ ያድጋል፣ ይሞታልም ከተባለ ሆሄያቱም የቋንቋው አካላት እንደመሆናቸው አብረው መወለድ፣ ማደግና መሞት ይገባቸዋል፡፡ ይህ ግን በፊደሎቻችን ላይ አይስተዋልም፡፡ ለዚህ እንደምሳሌ የተደረጉ ጥናቶችን ባላገላብጥም ከራሴ ጋር ስጠያየቅ ያስተዋልኩትን የአማርኛ ፊደል ገበታ አንድ ችግር ልጥቀስ፡፡ እንደምናውቀው ሆሄያቱ በድምጽ ላይ (ከግዕዝ እስከ ሳብዕ ባሉ ድምጾች) ተመስርተው ነው የተደረደሩት፤ ይሁን እንጂ አንዳንድ አፈንጋጮችም ይገኙበታል፡፡ እነዚህ አፈንጋጭ ሆሄያት የ‘ሀ’ እና ‘አ’ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ በ‘ሀ’ እና ‘ሃ’ ወይም በ‘አ’ እና ‘ኣ’ መካከል ያለውን የድምጽ ልዩነት መናገር የሚችል ማንም የለም፡፡ ምክንያቱም ሁለቱም የራብዕ ድምጽ አላቸው፡፡ ታዲያ የነዚህ ድምጾች ቤተሰብ የሆኑት የግዕዝ ድምጾች የት ገቡ?

መልሱ ቀላል ነው፡፡ ይህንን ክፍተት ለመጣፍ ሲባል ብቻ የተፈጠሩ በሚመስሉ ሌሎች የድምጽ ቤተሰቦች ውስጥ ተሰድረው እናገኛቸዋለን፡፡ እነዚህ ምትኮች ‘ኸ’ እና ‘ኧ’ ናቸው፡፡ አባቶቻችን የፊደላቱ መብዛት ናላቸውን አዙሮዋቸው ሳያስተውሉ ያለፏቸው ግድፈቶች የሆኑ እንደሆን እኛ ‹በቃን!› እንዳንልና እንዳናርማቸው የሚያስገድደን ምንድን ነው፡፡ እስኪ ከዚህ በታች ‘አ’ን ‘ኧ’ ብለን ለማንበብ እንዲመቸን ከታች እናስቀምጠውና የድምጽ ጉርብጣቱ እንዴት እንደሚጠፋ እናስተውል፡፡
ኘ  ኙ  ኚ  ኛ  ኜ  ኝ  ኞ
 ኡ  ኢ  ኣ  ኤ  እ  ኦ
ከ  ኩ  ኪ  ካ  ኬ  ክ   ኮ
 ሁ  ሂ  ሃ  ሄ  ህ  ሆ
አባባሌ በ‘አ’ ቦታ ‘ኧ’ ወይም በ‘ሀ’ ቦታ ‘ኸ’ ይቀመጥ ሳይሆን ‘ሀ’ እና ‘አ’ በትክክለኛው የግዕዝ ድምጻቸው እንደ ‘ኸ’ እና ‘ኧ’ ነው መነበብ ያለባቸው ነው፡፡

ሌላው ጉዳይ ምንም እንኳን የአማርኛ ሆሄያት የቱንም ያህል የበዙ ቢሆንም ቅሉ ፊደል ያልተፈጠረላቸው ድምጾች በርካታ መሆናቸው እሙን ነው፡፡ እዚህ ሳልጠቅሰው ማለፍ የማልፈልገው ነገር ግን ላልተውና ጠብቀው ሲነበቡ የተለያየ ትርጉም የሚሰጡ ቃላትን ነው፡፡

የፊደል ገበታችን ብዙ ድምጾችን የተደጋገሙ ሆሄያት ባለቤት አድርጓቸዋል፡፡ ከነዚህም ውስጥ ‹ሀ፣ሐ፣ኀ›፣ ‹ሠ፣ሰ›፣ ‹አ፣ዐ› እና ‹ጸ፣ፀ› ሳይጠቀሱ አይታለፉም፡፡ ይሁን እንጂ ከነዚህ ተመሳሳይ ድምጽ የሚሰጡ ሆሄያት መካከል አንዳቸውም ጠብቀውና ላልተው ሲነበቡ የተለያዩ ትርጉም የሚሰጡ ቃላት መፃፍ የሚቻልበት ሁናቴ አስቤ ሊመጣልኝ አልቻለም፡፡ ወይም አቀያይረን ብንጠቀምባቸው የተለያዩ ትርጉም የሚሰጡበትን አጋጣሚ ሕግጋቱ የፈጠሩልን መስሎ አልተሰማኝም፡፡ ለምሳሌ “መሳሳት” የሚለው ቃል ሲጠብቅና ሲላላ ሁለት ትርጉም ይሰጣል፡፡ ነገር ግን ይህንኑ ቃል “መሣሣት” ብዬ ብፅፈው ከሁለት አንዱን ትርጉም አይዝልኝም፡፡ ይህ ካልሆነ ድግግሞሻቸው በልምድ ውስጣችን ከታተሙ ቅርፆች የጎላ ትርጉም የላቸውም፡፡ እንዲያ ከሆነ ደግሞ የመደጋገማቸው ፋይዳም ለመከራከር የሚያበቃ አይደለም፡፡ (ከአማርኛ ይልቅ በግዕዝ ቋንቋ ውስጥ አንድ ድምጽን የሚወክሉ ሆሄያት ድግግሞሽ ይበልጥ ትርጉም እንዳላቸው ሊቃውንቱ አበክረው ይናገራሉ፡፡)

በተመሳሳይ ርዕስ በከፍተኛ ሁኔታ የሚመሰርቷቸው ቃላት በመጥበቅና በመላላት ሁለት ትርጉም የሚሰጡባቸው ‘ለ’ እና ‘ነ’ን የመሳሰሉት የድምጽ ቤተሰቦች ግን አማራጭ መተኪያ የላቸውም፡፡ እንደምሳሌ ‹አለ› እና ‹ዋና› የሚሉት ቃላት እንኳን ብንወስድ በቃላቱ ውስጥ ‘ለ’ እና ‘ና’ አቻ ሆሄ ቢኖራቸው ኖሮ ምናልባት የድምጹን መጥበቅ ወይም መላላት እናመላክትባቸው ነበር፡፡ ስለሆነም የአማርኛ የሆሄ ገበታ በራሱ የቋንቋውን ሕልውና በማይጎዳ መልኩ ቢሆንም ማነቆ ነው ማለት ይቻላል - መደገማቸው ፋይዳ የሌለው ድምጾች በተለያየ ቅርፆች ተደጋግመዋል፤ ቢደጋገሙ እንዲህ እናደርግባቸው ነበር የምንላቸው ደግሞ አቻ የላቸውም፡፡ እንደኔ፣ እንደኔ አባቶቻችን የተዉልንን የፊደል ገበታ ብንከልሰው ተፅዕኖው እስከምን ድረስ እንደሆነ ብጠይቅ ድፍረት አይመስለኝም፡፡ ይህንን ስል ግን ጉዳዩ ትውልድ የማሰልጠን ያህል ከባድ እንደሆነ ተስቶኝ አይደለም፡፡

እንደማጠቃለያ
ይህንን ፅሁፍ የፃፍኩት በጥንቃቄ እና በብዙ የሐሳብ ውጣ ውረድ ነው፡፡ ነገር ግን በቀላሉ አይገኝምና፣ ቀድሞ በተሰራ ጥናት ላይ ተመስርቼ፣ መረጃ አገላብጬ እንዳለመሆኑ ድክመቶች ሊገኙበት ይችላል፡፡ እንደአማርኛ ቋንቋ አፍቃሪነቴ ግን ለአማርኛ አጠቃቀምና ዕድገት ይበጃል ያልኳቸውን ሁሉ መጠቆሜ ባለሞያዎችን ለጥናት ያነሳሳ ይሆናል ብዬ ገምቼ ነው፡፡ ማንም በፅሁፌ ላይ አስተያየት መስጠት የሚፈልግ ሰው በምርምር የተደገፈም ሆነ የግል አተያዩን አደባባይ ቢያወጣው ለማድመጥ በጣም እጓጓለሁ፡፡

አማርኛ ቋንቋችን ነው፡፡ ብቸኛው የራሱ ፊደል ያለው የአፍሪካ ቋንቋም ነው፡፡ እኛ ካልተጠቀምንበት፣ ካላጌጥንበት እንኳንስ መለያችን ሊሆን ቀስ በቀስ እንቆቅልሽ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ አማርኛን በወጉ መማር፣ በአማርኛ መቀኘት ይለምልም፡፡ አሜን!

Sunday, April 3, 2011

5 Myths of Ethiopia


All you heard about Ethiopia is not true
ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ CBC News የተሰኘው የካናዳ መገናኛ ብዙሐን በድረ ዓምባው ‹‹ለጋሽ ሃገራት በኢትዮጵያ ላይ ጫና እንዲያደርጉ›› Human Rights Watch የተሰኘው የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች መጠየቁን የሚያመለክት ዜና ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡ በዘገባው ላይ ካናዳ ለምስራቅ አፍሪቃ 4ኛ ለጋሽ ሃገር መሆኗን ገልጧል፡፡ ከዜናው ቀጥሎ በርካታ ካናዳውያን አስተያየታቸውን አስፍረው ነበር፡፡ እነዚያን አስተያየቶች ማንበብ ‹‹ኩራት እራቴ› ለሚለው የኢትዮጵያ ሕዝብ አሸማቃቂ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከተመፅዋችነትም በላይ በባዕድ ሃገራት ዜጎች የተሰለቹ ስደተኞች ማፍራቷን ከአስተያየቶቹ መረዳት ይቻላል፡፡

ሁሌም በኢትዮጵያ ጉዳዮች እንደማደርገው ዛሬም ተብሰከሰኩ፡፡ ኢትዮጵያ ‹ቀደምት› የሚለውን ስሟን ብቻ ይዛ ዛሬ ላይ በኋላ ቀርነት ለመፈረጅ ያበቃት ነገር እንደው ምን ይሆን? ለዚህ ዓይነቱ ጥያቄ በየጊዜው የተለያየ መልስ አገኛለሁ፡፡ ዛሬም እንደዛው፣ ልዩነቱ የዛሬውን መልሴን በሌላ አማራጭ ከመቀየሬ በፊት ለናንተ ማስነበቤ ነው፡፡