Pages

Saturday, December 19, 2015

“…ማን አለ እንዳንተ፣ ታማኝ?”



የሆነ ጊዜ የሰማኋት ቀልድ ትዝ አለችኝ፤ አንዳንድ የተቃዋሚ ተወካዮች ፓርላማ ውስጥ በነበሩበት በዚያ በደጉ ጊዜ ነው አሉ፡፡ አንድ ተወካይ የሻዕቢያ መንግሥት ላይ ሊደረግ ስለሚገባው እርምጃ ሲናገሩ እንዲህ አሉ፤ “አሁኑኑ ገብተን ድምጥማጣቸውን ማጥፋት አለብን፡፡ አለበለዚያ ካደሩ አይቆረጠሙም፤ እነዚያ ወያኔዎችም ያኔ ሲመሠረቱ ሳንጨፈልቃቸው ዝም ብለናቸው ነው ዛሬ አናታችን ላይ…” አሉና ያሉበት ቦታ ትዝ ሲላቸው ድንግጥ ብለው ወደአቶ መለስ መቀመጫ አማተሩ፡፡ አቶ መለስ በጥሞና ያዳምጣሉ፤ ተወካዩ እንደደነገጡ “…ልጨርሰው ወይስ ትጨርሰኛለህ?” አሉ ይባላል፡፡

የሕወሓት/ኢሕአዴግ ወታደሮች አዲስ አበባ ደርሰው “ሲቪል” መንግሥት ከመመሥረታቸው አስቀድሞ “እኩይ” ናቸው በሚል ሲቃወማቸው የነበረ እና እስካሁንም ስክነቱ ያልተለየው አክቲቪስት ታማኝ በየነ ነው፡፡ የታማኝ የአክቲቪስትነት ሪከርድ ከኮሜዲያንነቱ የሚመዘዝ ነው፡፡ በቀልዶቹ ቢጀምርም አሁን ግን በጣም ‹ሲሪዬስ› ነው፡፡ አሁን እነቪኦኤ፣ ዶቸ ቬሊ፣ ኢሳት በየቤቱ እንደሚደመጡት ከደርግ ማክተሚያ ቀደም ብሎ ብዙ ሰው በየቤቱ ‹ድምፂ ወያነ›ን በድብቅ ያደምጥ ነበር፡፡ የፕሮፓጋንዳ ሚዲያዎች አመል ነውና ያው ውሸታቸው አይጣል ነው፡፡ ታዲያ ታማኝ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ቀርቦ የምሩን ሲቀልድ ‹እዚህ ቦታ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር፣ እዚያ ቦታ ደግሞ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር ደመሰስን ይላሉ፡፡ ሲደመር ግን ይሄን ያክላል፡፡ ቆይ እኔ የምለው ወያኔዎቹ የሚደመስሱት ጦር ከጠቅላላ ጦሩ በለጠ እኮ፤ ከየት እያመጡ ነው የሚደመስሱት?› ዓይነት ቀልድ ተናግሮ አላገጠባቸው፡፡ ከዚያ በድምፂ ወያነ መልስ ተሰጠው፤ “ቁጥሩን አዲስ አበባ ስንደርስ እናወራርዳለን” የሚል፡፡ ዛቻ የሽፍትነት ዘመንም አመል ነበረች፡፡

ግንቦት 20/1983 - ኢሕአዴግ አዲስ አበባን ሲረግጥ፣ ሲ ኤን ኤን ካነጋገራቸው ሰዎች አንዱ ታማኝ በየነ ነበር፡፡ “በመሣሪያ ተከበናል፣ ምንም ሠላም የለም…” የሚል ነገር ለጋዜጠኛው ሲነግረው ይታያል፡፡ ታዲያ ታማኝ ሁኔታውን በቀልድ ሲያስታውስ “ጓደኞቼ ከውጪ ደውለው ‹ሲ ኤን ኤን› ላይ አየንህ ሲሉኝ፣ ወዲያውኑ እንግሊዝኛዬ እንዴት ነበር?” አልኳቸው ይላል፡፡

ታማኝ ከአዲሱ ስርዓት ጋር አብሮ መኖር በማይችልበት ሁኔታ የተቀያየመው፣ ካልተሳሳትኩ የወቅቱ ባለሥልጣናት፣ እነታምራት ላይኔ በተገኙበት ስታዲዬም ውስጥ በቀለደው ቀልድ ነው፡፡ እንደማስታውሰው ቀልዱ በማንነት ላይ የተመሠረተ እና ለኢሕአዴግ የማንነት ብያኔ የማይበገር ዓይነት ቀልድ ነው፡፡