Pages

Saturday, November 26, 2011

“ኢትዮጵያውያን፣ ኢትዮጵያ እያለች ሃገር የላቸውም”


“በዓለም አንደኛ ነው፤” በሚል በገዛ ጓደኞቼ ተጠቁሜ፣ ሲኒማ ኢትዮጵያ ገብቼ ያየሁት “ዘመቻ ድንግልን ፍለጋ” የተሰኘ ፊልም አንደኝነቱን ለደረጃ አጣሪ ኮሚቴ ሰጥቼና እምባዬን ወደሰማይ ረጭቼ ከውስጡ ያገኘሁትን ዓረፍተ ነገር ለወጌ ርዕስነት መርጬዋለሁ፡፡ ዓረፍተ ነገሩ “7ተኛው ሰው” የተባለ ሌላ “በዓለም አንደኛ” ፊልም አስታወሰኝ፡፡ ሰባተኛው ሰው ወደአሜሪካ ለዎርክሾፕ ከሄዱት ሰባት ሰዎች መካከል ወደሃገሩ ተመልሶ የመጣው እና በፊልሙ ዓለም ውስጥ በነበሩ ምሁራን፣ ተቃዋሚ እና ገዢ ፖለቲከኞች ብሎም በቤተሰቦቹ ሳይቀር የመገለል ዕጣ የደረሰበት ነበር፡፡ ለምን ተመለስክ በሚል፡፡

እዚህ ፊልም ላይ የታየው ታሪክ እንዳልተጋነነ ለማወቅ ከፈለጋችሁ አንድ የእውነተኛ ታሪክ ልጨምርላችሁ፡፡ ፋንታሁን ሸዋንቆጨኝ በብሔራዊ ቲያትር አንጋፋ ድምፃዊ ነበር፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በባለሙያዎች የተወደሰ አልበም አውጥቶ ብዙም አድማጭ አላገኘም ነበር፡፡ በርግጥ ዜማዎቹ ለአሸሸ ገዳሜ የማይመቹ ስለሆኑ፣ የዘመኑን መስፈርት አያሟሉም ነበር፡፡ ብዙዎቻችሁ ከጂጂ ጋር በማሲንቆ ያዜማቸውን እና ከሸገር ሬዲዮ በቀር በሌላ ሬዲዮ ጣቢያ እምብዛም በማይደመጡት ዜማዎቹ ታውቁታላችሁ፡፡ ስለርሱ ነው የምነግራችሁ፡፡

Tuesday, November 22, 2011

የኢሕአዴግ ‹‹ትርፍ›› እና ኪሳራ


ኢሕአዴግን ፀሃዩ መንግስት እያለ በሽሙጥ የሚያንቆለጳጵሰው አበበ ቶላ በካድሬዎች ሽንቆጣ ብዛት ኮበለለ፣ የአውራምባ ታይምስ ማኔጂንግ ኤዲተርና የ2010 CPJ ፕሬስ ነፃነት ተሸላሚው ዳዊት ከበደም እያሻቀበ በመጣበት ትንኮሳና (እንደራሱ ገለፃ ‹‹ማክሰኞ፤ ሕዳር 12፤ 2004›› ሊታሰር ስለነበር) ወደ ሃገረ አሜሪካ እግሬ አውጪኝ አለ፡፡ የምንወዳቸው፣ ጽሁፎቻቸውን የምንናፍቅላቸው ጋዜጠኞች በሙሉ ከፊሎቹ ተሰደዱ፣ ከፊሎቹ አቋማቸውን አለዘቡ፣ ከፊሎቹ ብዕራቸውን ሰቀሉ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ታሰሩ፡፡ ‹‹ሂስ ቀረበብን ብለው ሃገር ጥለው ፈረጠጡ›› በሚል በጠቅላይ ሚኒስቴሩ የተተቹት እነ ዐቢይ ተክለማርያም እና መስፍን ነጋሽ በአሸባሪነት በሌሉበት በተከሰሱበት በዚህ ቀውጢ ሰዓት የሃገራችን የፕሬስ ነጻነት በአስተማማኝ ሁኔታ ላይ እንዳለ አቶ በረከት ስምዖንን፣ ሚሚ ስብሃቱን፣ ሳምሶን ማሞን ወይም የኢቴቪ ሚዲያ ዳሰሳ አዘጋጆችን ጠይቆ መረዳት ይቻላል፡፡

በተቃራኒው WorldPress Freedom Index 2010 የኢትዮጵያን የፕሬስ ነፃነት ‹‹አስቸጋሪ ሁኔታ›› (ለመጨረሻ ሩብ ጉዳይ) ላይ እንዳለ ይነግረናል፡፡ የ2011 ውጤት ሲታወቅ ደግሞ ‹‹በጣም አሳሳቢ ደረጃ ላይ›› (የመጨረሻ ደረጃ ላይ) ነው ብሎ እንደሚፈርጀው መገመት አይከብድም፡፡ በFreedom of the Press Global Status ላይ ደግሞ ኢትዮጵያ ‹‹ነፃ ያልሆነች›› ተብላለች፡፡ ጋዜጠኞችንም በማሰር ቢሆን ኢትዮጵያን ከኤርትራ በቀር የሚበልጣት እንደሌለ chartsbin.com በዝርዝር ያስነብበናል፡፡ እኛ ማንን እንመን? በመንግስት ቲፎዞነታቸው የምናውቃቸውን እኒያን ግለሰቦች ወይስ በጥናት ላይ ተመርኩዘው የሚነግሩንን እኒህ ኃላፊነት የሚሰማቸውን ድርጅቶች? ግዴለም የምናየውን እንመን፤ የታሰሩትንና እየተሰደዱ ያሉትን ጋዜጠኞች አይተን እንፍረድ፡፡

Thursday, November 10, 2011

“Every nation deserves its government” - ኦቶ ቮን ቢስማርክ

ሠላም ሰፍኗል፡፡ ሠላም የሚያሰፍን ግን አንዳችም ነገር የለም፡፡ የኑሮ ዋጋ ከሕይወት ዋጋ በልጧል፣ በቂ ቀርቶ ግማሽ ነፃነት የለም፤ ሕዝቡ ግን አይበሳጭም ወይም ብስጭቱን አፍኖ ተቀምጧል፡፡ ‹‹የባሰ አታምጣ›› እያለ የምድራዊውን ገዢ በደል ‹‹በሰማያዊው›› ላይ ያሳብባል (‹‹የቄሳርን ለቄሳር›› መባሉ ተዘንግቷል!) - የኢትዮጵያ ሕዝብ የኢሕአዴግን መንግስት እንደሚጠላው እና እንደተማረረበት ቢታወቅም - ‹በቃኸኝ› ሊለው ግን አልፈለገም ወይም አልደፈረም፡፡

ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ ኢትዮጵያውያን ለአብዮት የሚያበቃ ብስጭት ላይ ደርሰዋል? ባሉት ጽሁፋቸው ላይ ‹‹ሕዝባዊ አመጽ በኢትዮጵያ የመነሳት ዕድሉ በብዙሐኑ ስነልቦናዊ ዝግጅት ላይ የተመረኮዘ ነው›› በማለት የስነልቡናው ዝግጅት አናሳ በመሆኑ በኢትዮጵያ ሕዝባዊ አመጽ፣ በቅርቡ ይቀሰቀሳል ብሎ መጠበቅ እንደማያዋጣ አመልክተዋል፡፡

ሕዝባዊ አመጽ ያስጠላል፡፡ ሁሉም ሰው በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት ይወዳል፡፡ ነገር ግን ከጊዜያዊ ሰላም ይልቅ ዘላቂ ለውጥ ይበልጥ አስፈላጊ ነው፡፡ የማንበላ መብላት፣ የታረዝን መልበስ፣ የታሰርን መፈታት ያምረናል፡፡ እንዳምና ካቻምናው ሁሉ ከመሰረታዊ ፍላጎቶቻችን ጋር ተጣብቀነ በምግብ ራስን ስለመቻል እና የነፃነት አየር ስለመተንፈስ ማውራት ያሰለቻል፤ እንደሌሎች ሃገራት ስለዓለም ዓቀፍ ገበያ፣ ስለኅዋ ሳይንስ እና ስለሁለተኛ ፍላጎቶቻችን የማውራት ወግ ያምረናል፡፡ አምሮታችንን ለመወጣት ደግሞ እንቅፋት ከፊት ለፊታችን ተደቅኖ ይታየናል - ለውጡ ባይመጣስ ብለን እንፈራለን ወይም ደግሞ የለውጥ ሒደቱን ከወዲሁ ስናስበው ይደክመናል፡፡

Monday, November 7, 2011

In T1me - ጊዜ ገንዘብ (ገንዘብ ጊዜ) ቢሆን ኖሮ!

From Addis Ababa, Ethiopia
“Occupy Wall Street” በሚል መፈክር አንድ በመቶ የሚሆኑ ባለፀጎች የሚመሩትን የኢኮኖሚ ፖለቲካ 99 በመቶዎቹ ሊንዱት እየተፍጨረጨሩ ባለበት በዚህ ቀውጢ ሰዓት፣ In Time የተሰኘ ፊልም ወጥቷል፡፡ ፊልሙ ጊዜን መገበያያ ገንዘብ አድርጎ አምጥቶታል፡፡ መገበያያ ብቻ ግን አይደለም፤ ሕይወትም ጭምር ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ያለው ሰው ሃብታም፣ ትንሽ ጊዜ ያለው ሰው ደግሞ ድሃ ነው፡፡ ድሃው ቶሎ ይሞታል፣ ሃብታሙ ግን ዘላለም የመኖርም ዕድል አለው - በስህተት ካልሞተ፡፡

የፊልሙ ዓለም ውስጥ ያሉ ሰዎች ሃብታቸውና ሕይወታቸው (ጊዜ) እጃቸው ላይ ታትሞ/በተፈጥሮ መሆኑ ነው/ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ማኪያቶ ለመጠጣት 5 ደቂቃ ሲከፍሉ፣ መኪና ለመግዛት ደግሞ ዓመታትን ያወጣሉ፡፡ ስጦታ ይሰጣጣሉ፣ ይሰራረቃሉ፣ ያተርፋሉ ይከስራሉ፡፡ ብዙዎቹ ድሆች ከሰዓታት የበለጠ ስለሌላቸው ሕይወታቸውን ለማሳደር ሲሉ ይዋከባሉ፡፡ ሃብታሞቹ ደግሞ ከእጃቸው ተርፎ ማዕከላዊ ቁጥጥር ሲስተም ውስጥ የሚያጠራቅሙት ዓመታት አላቸው፡፡

በፊልሙ ውስጥ ፖሊስ - ጊዜ ጠባቂ፣ ድንበር - የጊዜ ዞን፣ ባንክ - የጊዜ ማበደሪያ በመባል ይታወቃል፡፡

In Time ሊያስተላልፍ የሞከረው ነገር ሃብታሞች ብዙ ገንዘብ ባካበቱ ቁጥር የሚያካብቱት ከድሃው የተቆነጣጠረ መሆኑን ነው፡፡ ገንዘብ ዕድሜን ቢቀጥል ኖሮ (በርግጥም ይቀጥላል) እነርሱ እየኖሩ ድሃው ይሞታል እንደማለትም ነው፡፡ የፊልሙ ዋና ገፀ ባሕርይ (ጀስቲን ቲምበርሌክ ይተውነዋል) ጊዜን ከሃብታሞቹ እየዘረፈ ለድሆቹ ሲያከፋፍል ይታያል፡፡ ነገርዬው ሶሺያሊዝም ይመስላል፡፡ ዘመናችን ሶሺያሊዝምን እየናፈቀ ይሆን የሚል ጥያቄ መጣብኝ፡፡ ነፃ ገበያ ብሎ ነገር አበቃለት ይሆን?

Friday, November 4, 2011

ኢትዮጵያ ከኢሕአዴግ በኋላ፤ ሰጥቶ የመንጠቅ ዘመነ መንግስት

From Addis Ababa, Ethiopia
በርግጥ ይሄ የአገሪቱ ቅርጽም ኢሕአዴግ አመጣሽ ነው:: 
ስጦታ ወይስ ንፍገት የሚለውን ግን እናንተው ፍረዱ::
ኢሕአዴግ (ሕወሓት) ከአሸባሪነት ወደ አሸባሪ ሰያሚነት በተሸጋገረባቸው ሃያ ዓመታት ውስጥ ብዙ ተግባራትን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ ተግባራቱ፤ ገሚሱ ለፓርቲው ሕልውና፣ ጥቂቱ ለአገሪቱ ሕልውና (ፓርቲው ያለርሷ አይኖርምና)፣ ቀሪው ደግሞ እንዲሁ ማድረግ ደስ ሲለው ያደረጋቸው ነገሮች ናቸው፡፡ አሁን የምጽፈውም ለኢትዮጵያ የትኞቹ ፌሽታ፣ የትኞቹ መዐት ይዘው መጡ የሚለውን ለማስታወስ ያክል ብቻ ሳይሆን የኢሕአዴግ ስጦታ ውሃ በወንፊት መሆኑን የታዘብኩ ስለመሰለኝ ነው፡፡

ስጦታ
በ20 ዓመታት ውስጥ የመንግስት ኃላፊነትን (በጉልበቱም ቢሆን) ከወሰደ በኋላ አንዳንድ ለውጦችን አምጥቷል፡፡ ሆኖም የመጡትን ለውጦች ካየናቸው አብዛኛዎቹ የተፈፀሙት በመጀመሪያው አምስት ዓመታት ብቻ መሆኑ ያስገርመናል፡፡ ሆኖም እዚህ ስጦታ እያልኩ የምዘረዝራቸውን ነገሮች ሁሉ መልሶ እንዴት እንደሚወስዳቸው ወረድ ብለን፤ በሌላ ንዑስ ርዕስ እንመለከተዋለን፡፡