Skip to main content

“ኢትዮጵያውያን፣ ኢትዮጵያ እያለች ሃገር የላቸውም”


“በዓለም አንደኛ ነው፤” በሚል በገዛ ጓደኞቼ ተጠቁሜ፣ ሲኒማ ኢትዮጵያ ገብቼ ያየሁት “ዘመቻ ድንግልን ፍለጋ” የተሰኘ ፊልም አንደኝነቱን ለደረጃ አጣሪ ኮሚቴ ሰጥቼና እምባዬን ወደሰማይ ረጭቼ ከውስጡ ያገኘሁትን ዓረፍተ ነገር ለወጌ ርዕስነት መርጬዋለሁ፡፡ ዓረፍተ ነገሩ “7ተኛው ሰው” የተባለ ሌላ “በዓለም አንደኛ” ፊልም አስታወሰኝ፡፡ ሰባተኛው ሰው ወደአሜሪካ ለዎርክሾፕ ከሄዱት ሰባት ሰዎች መካከል ወደሃገሩ ተመልሶ የመጣው እና በፊልሙ ዓለም ውስጥ በነበሩ ምሁራን፣ ተቃዋሚ እና ገዢ ፖለቲከኞች ብሎም በቤተሰቦቹ ሳይቀር የመገለል ዕጣ የደረሰበት ነበር፡፡ ለምን ተመለስክ በሚል፡፡

እዚህ ፊልም ላይ የታየው ታሪክ እንዳልተጋነነ ለማወቅ ከፈለጋችሁ አንድ የእውነተኛ ታሪክ ልጨምርላችሁ፡፡ ፋንታሁን ሸዋንቆጨኝ በብሔራዊ ቲያትር አንጋፋ ድምፃዊ ነበር፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በባለሙያዎች የተወደሰ አልበም አውጥቶ ብዙም አድማጭ አላገኘም ነበር፡፡ በርግጥ ዜማዎቹ ለአሸሸ ገዳሜ የማይመቹ ስለሆኑ፣ የዘመኑን መስፈርት አያሟሉም ነበር፡፡ ብዙዎቻችሁ ከጂጂ ጋር በማሲንቆ ያዜማቸውን እና ከሸገር ሬዲዮ በቀር በሌላ ሬዲዮ ጣቢያ እምብዛም በማይደመጡት ዜማዎቹ ታውቁታላችሁ፡፡ ስለርሱ ነው የምነግራችሁ፡፡

አርቲስት ፋንታሁን ከጥቂት ዓመታት በፊት ሙሉ የኪነት ቡድን በመሪነት ይዞ አውሮፓና አሜሪካ ደርሶ ሲመለስ፣ ልክ ሰባተኛው ሰው ላይ እንደነበረው ሰባተኛ ሰው ብቻውን ነበር የተመለሰው፡፡ ታዲያ እሱም ወይ ቆጭቶታል፣ ወይ መገለል ደርሶበታል፣ አሊያም ደግሞ በቢፒአር ጦስ ከደረጃው ዝቅ በመደረጉ ተበሳጭቷል ለድጋሚ ዙር ወደአሜሪካ እንደወጣ በዚያው ቀርቷል፡፡

በኢትዮጵያ ሕዝብ ገንዘብም ይሁን በለጋሽ ሃገራት ድጎማ፣ በቡድንም ሆነ በተናጠል፣ ለትምህርትም ሆነ ለሴሚናር የሚላኩ ኢትዮጵያውያን በወጡበት መቅረት ከጀመሩ ቆዩ፡፡ ጉዳዩ እየጨመረ መጣ እንጂ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የዛሬ ሰባት ዓመት ገደማ አንድ 30 ዓመት ያልሞላው፣ መቀሌ ዩንቨርስቲ ውስጥ የኢንፎርሜሽን ሲስተምስ አስተማሪ ለሦስት ወራት ስልጠና ወደአሜሪካ መሄድ ነበረበት፡፡ የወቅቱ አለቃው አሜሪካዊ ስለነበር ቪዛ ለማግኘት አልተቸገረም ነበር ነገር ግን የአሜሪካ ኤምባሲዋ ቪዛ ኃላፊ ‹‹ቪዛውን የምሰጠው እንደሚቀር እያወቅኩ ነው›› አለችው ለአሜሪካዊው አለቃው፡፡ አለቅዬውም ‹‹አይቀርም›› ብሎ ተወራረዳት፡፡ ሁለቱ ግለሰቦች በወር ደሞዛቸው አስያዙ፡፡ ይህንን ጉዳይ ወጣቱ አልሰማም፡፡

በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ሦስት ወር አለቀና ወጣቱ ከጀመርመን ሁኖ ደወለ - ለአለቃው፡፡ ‹‹በሉፍታንዛ እየበረርኩ ነው፡፡ አሁን ጀርመን ላይ ለትራንዚት አርፌያለሁ፤ ነገ አዲስ አበባ ነኝ›› አለው፡፡ የቪዛ ጉዳይ ኃላፊዋ ተሸነፈች፡፡ ታሪኩን በዝርዝር ሲሰሙት በጣም ያስደስታል፡፡ ይሄ ታሪክ ግን አሁን አልፎበታል፡፡ አለቅዬውም አምኖ አይወራረድም፡፡

አንዲት እኔ በቅርብ የማውቃት ሴት ለአጭር ጊዜ ስልጠና አሜሪካ ከገባች በኋላ በሳምንቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጂ20 ስብሰባ ላይ መገኘታቸውን ለመቃወም በተጠራ የኢትዮጵያውያን ስደተኞች ተቃውሞ ሰልፍ ላይ ፊት ለፊት መፈክር ይዛ ቆማ ዩቱዩብ ላይ አየኋት፡፡ ልጅቱ እዚህ እያለች አንድም የተቃውሞ ድምጽ ስታሰማ አላስታውስም ነበር፤ የኋላ ኋላ ግን ፖለቲካዊ ጥገኝነት እንደጠየቀች ሰማሁ፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጥገኝነት የሚባል ነገር ቢኖር ኖሮ አሪፍ ነበር፡፡ ምክንያቱም እሷን መሰሎቹ ጥገኝነት ጠያቂዎች የእውነት ፖለቲካዊ ስጋት ተጋርጦባቸው ለሚሰደዱትን ዜጎች መጠጊያ የሚያሳጣ ጥርጣሬ እንዲያጋጥማቸው መንስኤ ሆነዋል፡፡

አንዲት የቅርብ ጓደኛዬ ከዕድሜዋ በእጥፍ ሲደመር አንድ ዓመት የሚበልጣትን አሜሪካዊ አገባች፡፡ በርግጥ እንደነገረችኝ ከሆነ ግንኙነታቸው “ፍቅር አለበት፤ በዚያ ላይ ከሐበሻ ወጣት አሜሪካዊ ጎልማሳ የተሻለ ሮማንቲክ” እንደሆነ በተለያዩ አጋጣሚዎች ነግራኛለች፡፡ እኔ ግን ከሰውዬው ባልተናነሰ መልኩ ከአሜሪካጋ ፍቅር እንደያዛት ይሰማኛል፡፡ ጉዳዩ ‘በምንም ምክንያት ይሁን በየትም በኩል ከኢትዮጵያ ውጣ፤ አለበለዚያ ያልፍብሃል’ ነው ጨዋታው፡፡

ከምንወዳት ሃገራችን ለመውጣት ሕይወታቸውን የሚከፍሉ ሰዎች ቁጥርም ቀላል አይደለም፡፡ በኤርትራ ባሕር ወደየመን እና የሞያሌ ወደብን አሳብሮ ወደሱዳን ለማቋረጥ በሚደረጉ ተጋድሎዎች የሚያልፉትን ሕይወቶችና ባክነው የሚቀሩ ዜጎቻችንን ታሪክ ማንበብ ነዋሪ ምሳሌ ነው፡፡ በቅርቡ ሞዛምቢክ ውስጥ ወደደቡብ አፍሪካ ለማቋረጥ የተሸሸጉ ኢትዮጵያውያንን ማጋለጥ ያሸልማል መባሉ አንገት የሚያስደፋ የአደባባይ ገመና ነው፡፡

እዚህም ‹‹እዬዬ!›› እዚያም ‹‹እዬዬ!››
በሚገርም ሁኔታ አብረውኝ ያደጉ እና የኑሮ ዱብዱብ በተለያየ አጋጣሚ ያገናኙን በርካታ ሰዎች አሁን በፌስቡክ የጓደኞቼ ዝርዝር ውስጥ ተገጥግጠዋል፡፡ ባሕር ማዶ ያሉት ጥቂት የማይባሉ ናቸው፡፡ እናም አንዳንዴ በቻት መስኮት ስናወጋ የሚነግሩኝ ነገር እዚህ እያሉ ከሚያማርሩት የተሻለ ዕድል እንዳልገጠማቸው የሚያሳብቅ ነው፡፡
አንዱ፤ “ኢትዮጵያን በእንብርክኬ ይቅርታ ልጠይቃት እፈልጋለሁ” አለኝ፡፡ ይህ ሰው እዚህ እያለ መኖር አቁሞ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ እዚህ አገር ሰርቶ ሰው መሆን እንደማይችል በቁርጠኝነት፣ በየአደባባዩ ይመሰክር ነበር፡፡ እዚያስ?
ሌላው፤ “የአሜሪካ ሕንፃ ለኔ ምኔ ነው፤ የዕለት ጉርስ ይሆነኛል?” ጠየቀኝ፡፡ “አየዋለሁ እንጂ አልገባበትም” እኔ መልስ እንደሌለኝ ጠፍቶት አይደለም፡፡ ብሶቱን እያራገፈ እንጂ! እንደርሱ አገላለጽ “አሜሪካ ተበልቶባታል፡፡” አሁን “እንዳህያ ሰርተው እንደ ጉማሬ ማውጣት ብቻ ነው የቀረው” ካለ በኋላ “እኔ እንደውም በድብርት ራሴን እንዳላጠፋ ነው የምፈራው” ብሎኛል፡፡
ሌላዋ፤ “ውጪ አገር መሄድ፤ የሃገር ፍቅርህን ይጨምረዋል እንጂ ጠብ የሚያደርገው ነገር የለም፤” ብላኛለች፡፡

እዚህ ነገሩ የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ለምሳሌ ከላይ የጠቀስኩት አንደኛው ሚስት እዚህ፣ ከባሏ በሚላኩላት ጥቂት ዶላሮች የሚታይ ለውጥ እያመጣች በመሆኑ ለብዙ ተመልካቾቿ የስደት ናፍቆትን አጠናክራለች፡፡ እዚያ ምንም ተሁኖ ቢሰራ፣ እዚህ መጠነኛ ፋይዳ ያለው ለውጥ ማስመዝገቡ ሁሉንም ሰው ወደማያውቁት ገዳም እንዲመንኑ አስመኝቷቸዋል፡፡

በሌላ በኩል እዚያ ሁነው የሚያማርሩት “ለምን ወደሃገራችሁ መጥታችሁ አትኖሩም?” ሲባሉ አለመስማማታቸውን፣ እዚህ ያሉቱ በጥርጣሬ እንዲመለከቱት እያደረጋቸው ነው፡፡ እነርሱ የደረሱበት ደረጃ ሌሎች እንዳይደርሱ የሚያደርጉት የምቀኝነት ንግግር እስከሚመስል ድረስ፡፡ እውነታው ግን ሌላ ነው፡፡ ብዙዎቹ ስደተኞቹ እዚህ የጀመሩትን ኑሮ አቋርጠው በሰው አገር አዲስ ኑሮ ጀምረዋል፤ አዲሱ ኑሮም አልሞላም፡፡ እዚህ መጥተው ሦስተኛ ኑሮ መጀመሩ ምን ያህል መስዋዕትነት እንደሚያስከፍላቸው ያውቃሉ፤ ስለዚህ ተመልሰው ይሄዳሉ፡፡ አንድ ቀን የሄዱበት ጉዳይ ከሞላላቸው ይመለሳሉ፤ ብዙዎቹ ግን ሳይሞላላቸው በፊት ለቀብራቸው ኢትዮጵያ ይመጣሉ - ኢትዮጵያ ውስጥ አልቅሶ የሚቀብራቸው ሰው አይጠፋም፡፡

Comments

Popular posts from this blog

The "Corridor Development" is a Façade of the Prosperity Party

Befekadu Hailu I have seen a news report claiming that 40% of central Addis Ababa will be demolished for the corridor development; I am not able to confirm the validity of the news but it sounds real to me given the size of massive operations in the demolition of old neighborhoods and construction of bike lanes, green areas, and glittering street lights. I like to see some beauty added to my city but cannot help mourning the slow death of it too. Addis Ababa was already in a huge crisis of housing and the demolition of houses is exacerbating it. Apparently, Prime Minister Abiy Ahmed is eager to showcase his vision of prosperity by demonstrating how fast his administration can do magic by beautifying the front sides of the streets with lights, new pavements, and painted fences ("to fake it until he makes it" in my friend's words). Therefore, he and his party do not care about the miserable human stories behind the scenes and they will harass you if you tell it (Azeb Woku...

የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ

በፍቃዱ ዘ . ኃይሉ “የአዲስ አበባ ብሔርተኝነት” ቢኖር ኖሮ መሪው ልጅ ሚካኤል ይሆን ነበር። አሁን አሁን እሱ ስለ አዲስ አበባ የዘፈናቸውን ዘፈኖች ቁጥር ራሱ በትክክል መቁጠር ይቸግረኛል። ለአዲስ አበባ ከተዘፈኑ ዘፈኖቹ ውጪም በየዘፈኑ ውስጥ የሚጨማምራቸው መልዕክቶች በራሳቸው መወድሰ አዲስ አበባ ናቸው። ለምሳሌ፣ በቅርቡ በለቀቀው ‘አዲስ አራዳ’ በተሰኘው አልበሙ ውስጥ ‘የድሬ ልጅ’ የሚል ዘፈን አለው። ዘፈኑ የተዘጋጀው ያው የአዲስ አበባ እህት ተደርጋ የምትቆጠረውን ድሬ ዳዋን ለማወደስ ነበር። ልጅ ሚካኤል ግን የአዲስ አበባ ፍቅሩ ያመልጠውና የሚከተለውን ያቀነቅናል፦ “መጣልሽ በሏት፣ ድሬ ድረስ፣  ከአዱ ገነት፣ ከሸገር፣ ከአዲስ ደረሰ፣... የሸገር ልጅ አራዳ ነው፣ ሰው አክባሪ፣ ሰው ወዳዱ፣ ቀላጅና ተረበኛ፣ ፍቅር ይዞ የሚተኛ፣ ‘አለው’ የለ፣ ‘የለው’ የለ፣ ከሁሉ ጋ፣ ግባ ጀባ...፤” ፤ ልጅ ሚካኤል በዚህ አልበሙ ብቻ አዲስ አበባን የሚያውድሰባቸው ሌሎችም ዘፈኖች አሉ፤ ‘ አዲስ አራዳ ’ የሚለው የአልበሙ መጠሪያ እና ‘ሸገር’ የሚሉት ዘፈኖቹ ዋነኞቹ ናቸው። ታዲያ እንዲህ በአዲስ አበባ ፍቅር የሚቃጠለው ልጅ ሚካኤል "ሊነግረን የሚፈልገው ምንድን ነው?" የሚለው ጥያቄ ደጋግሞ ይመጣብኛል። ይህ የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ ምንነትን ለመረዳት የሚጥር ፖለቲካዊ መጣጥፍ ነው። ‘አዲሱ አራዳ’ ማነው? በዚህ ዘፈኑ በብዙዎቻችን ዕድሜ የትዝታ ማኅደር ውስጥ የሚገኙ ነገር ግን በአዲስ አበባ ልማት ሥም የፈረሱ እና እየተረሱ ያሉ ሰፈሮችን ሥም ያነሳሳል። ዘፈኑ በግጥሙም በዜማውም፣ የሐዘን እንጉርጉሮ ያለበት ነው። ምሳሌ እንውሰድ፦ “ጨርሰሽ ስትወጪ ከቡፌ ዳ’ላጋ፣ ጠብቂኝ እንዳልል፣ ቆመሽ መሐሙድ’ጋ፣ አገር ...

መጽሐፍ የሚወጣው፣ የተዋነይ ዘ ጎንጅ 5 መሥመር ቅኔ

ጎንጅ ቅኔ ያጠናበት ደብር ሥም ነው። ደብረ ጥበብ ጎንጅ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም። ተዋነይ የባለቅኔው ሥም ነው። (የግዕዝ ትርጉሙ "ዋናተኛ" ማለት ነው።) ሊቁ ተዋነይ የልኅቀቱን ያክል እምብዛም አይወራለትም፤ ነገር ግን በዘመኑ ወደር የሌለው ልኂቅ ስለመሆኑ ሥራው ይናገራል። የሕይወት ተፈራ "Mine to Win" የተሰኘ ድርሰት መቼቱን በዐፄ ዮሓንስ ንግሥና ዘመን፣ በጎጃም/ጎንደር የቅኔ መማሪያ ደብሮች ያደረገ ልብወለድ ነው። ልቦለዱ የቅኔ ትምህርት ስርዓትን ያስተዋውቀናል፤ በበኩሌ የቅኔ ትምህርትን እና የቅኔ ሊቃውንት ታላቅነት ቀድሞ ከነበረኝ ግንዛቤ የበለጠ እንዲሆን አድርጎኛል። በተለይ የተዋነይ ዘ ጎንጅ (በውኑ ዓለም የነበረ ባለቅኔ) ተከታይዋ አምስት መሥመር ቅኔ መጽሐፍ የሚወጣት እንደሆነች ልቦለዱ አሳሰበኝ። ወይም በአጭሩ ብዙ ምዕራባውያን ስንት መጽሐፍ የጻፉለት ፍልስፍናን በአምስት መሥመር ይዟል። የቅኔው ትርጓሜ የመጽሐፍ ቅዱስን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ፈጣሪ ኅልውና ይሞግታል። “የአምን ወይገኒ ኵሉ ዓለም በዘፈጠረ ለሊሁ ብዙኃን እንዘ ይገንዩ ይስግዱ ቅድሜሁ ለነጽሮ ዝኒ ነገር እሥራኤል ከመይፍርሑ ሙሴ ፈጠረ ፈጣሪሁ ወ ፈጣሪ ፈጠረ ኪያሁ።” (ተዋነይ ዘ ጎንጅ። ምንጭ፣ሕይወት ታደሰ ወደአማርኛ የተረጎመችው የሕይወት ተፈራ መጽሐፍ) ትርጉሙን በኋላ እመለስበታለሁ። ስለተዋነይ መጀመሪያ የሰማሁት የበውቀቱ መጽሐፍ ላይ ነበር። እሱም በጨረፍታ - “የሌሊት ዜማዎች” የሚለው ግጥሙ ውስጥ። በውቀቱ ተዋነይን በግጥሙ ግርጌ ማስታወሻው አስተዋውቆን ያልፋል፣ “ተዋነይ በቅኔ ቤት አፈ ታሪክ ሞትን በግዝት ለሰባት ዓመታት ያቆመ ጀግና ነው"። ከዚያ በኋላ፣ አዲስ አድማስ ላይ የወጣ አንድ ጽሑፍ ተዋነይ የተላከበትን ...