Pages

Monday, August 27, 2012

ነውርን ማን ፈጠረው?

From አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

ሰሞኑን በሞት ስልጣናቸውን ስለለቀቁት ጠቅላይ ሚኒስትር  ያለኝን ትዝታ ‹የመለስ ሁለት መልክ› በሚል ጽፌው ነበር፡፡ ጽሑፉ ውስጥ የመለስ አስተዳደር በተለይ የተመቻቸው የብሔር አባላት እንዳሉ በስም በመጥቀሴ ‹‹ዘረኛ ነህ›› የሚል ብዙ አስተያየት ተሰንዝሮብኛል፡፡ እነሆ ይህ አስተያየትም ይህን ጽሑፍ ወልዷል፡፡ ነውርን ማን ፈጠረው? በመጀመሪያም፡-

ነፃነት እና ልቅነት

ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት ለድርድር የማይቀመጡለት አጀንዳ ነው፡፡ ሆኖም ሁሉም ሰው ሐሳቤን በነፃነት የመግለፅ መብቴ በሕግ ተደንግጓል ወይም ተፈጥሮ ያጎናፀፈኝ ነው በማለት እንዳሻው አይናገርም፡፡ በተለይም ሐሳቡ የሚቀርብበት ሚዲየም ሰፊ ሲሆንና ብዙ ተደራሲዎች ሲኖሩት ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፡፡ ይህ ጥንቃቄ የሚያስፈልግበት በርካታ ምክንያቶች አሉ፤ ከነዚህም ውስጥ የሕዝብን አቅጣጫ ላለማሳት፣ መረንነትን ወይም ልቅነትን ላለማስፋፋት እና አሁን ስለሆነው ሳይሆን ነገ እንዲሆን ስለምንፈልገው በመሳሳት (ሳ ላልቶ ይነበብ) ነው፡፡ ሁሉንም በሒደት ወደታች አብራራቸዋለሁ፡፡

‹የሕዝብን አቅጣጫ ላለማሳት› ያልኩት ሐሳባችንን የምንገልጽበት አገባብ (context) ተደራሲያኑ ጋር ሲደርስ ሌላ አንድምታ እንዳይኖረው የሚለውን ነው፡፡ ምናልባትም ያለፈው ጽሑፍ ውስጥ ‹ባለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት አዲስ አበባ ውስጥ ከተሰሩ ሕንፃዎች መካከል አብዛኛዎቹ የትግራይ ልጆች ንብረት ናቸው› ማለቴ በአንባቢው ዘንድ የትግራይ ልጆች ሁሉ በኢሕአዴግ ስርዓት ተጠቅሟል የሚል ትርጉም ከሰጠ አቅጣጫ አስቷል ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን እኔ በፃፍኩበት መንፈስ የትግራይ ተወላጆች ከኢትዮጵያ ሕዝብ አንፃር ካላቸው ድርሻ (proportion) ጋር ሲወዳደር በስልጣን እና በከተማ ሃብት ይዞታ ላይ ያላቸው ድርሻ ከፍ ያለ ነው የሚል ነው፡፡

ይሄንን እውነታ እንዳላነሳ የሚያስገድደኝ አካል ሊኖር አይችልም፤ የአገላለፁ አቀራረብ ላይ ውይይት ሊደረግ ግን እንደሚችል አልደራደርም፡፡ ይልቁንም ይህንን ጉዳይ የማይወራ ‹‹ነውር›› ነው የሚሉት (የሚያነውሩት) የስርዓቱ ፈጣሪዎች ወይም ተጠቃሚዎች ራሳቸው እንደሆኑም ይሰማኛል፡፡

Friday, August 24, 2012

የመለስ ሁለት መልክ

From አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሞት ‹‹ድንገተኝነት›› ብዙ ድራማዎችን አስከትሏል፡፡ መጀመሪያ ላይ ብዙዎች ተደሰቱ፣ ማታ ላይ ኢቴቪ ያነጋገራቸው ‹‹አንዳንድ ሰዎች›› የሰውየውን ታላቅ መሪነት ሲዘክሩ ያድናቂዎቻቸው ቁጥር ጨመረ፣ በጣም ማታ ላይ ወ/ሮ አዜብ ‹‹ተቀጣሁ፤ ምን አጥፍቼ ነው?›› በማለት ሙሾ ሲያወርዱ ‹‹የመለስ ታላቅነት›› የተገለፀላቸው ሰዎች ቁጥር በእጥፍ አደገ፡፡ ልብ በሉ በሞታቸው የመጀመሪያ ዕለት ብቻ ሁለት የተለያየ ገጽታ ለመያዝ የበቁት መለስ ዜናዊ ብቻ ናቸው፡፡ ነገርዬው ግን አብሯቸው የኖረ ነው፡፡

ዴሞክራሲያዊ-አምባገነን

መለስ ዴሞክራሲያዊ መንግስት የሚመስል ነገር መስርተዋል፡፡ ‹‹ዴሞክራሲ›› የሚለው ቃል በሚዲያ ተደጋግሞ እንዲነገርም ይፈልጋሉ፤ ያለ እንዲመስል፡፡ በምርጫ ማሸነፍ ያለበት የእርሳቸው ፓርቲ ብቻ እንደሆነ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የገዢው ፓርቲ ደጋፊ እንዲሆኑ፣ ጋዜጦችና ጋዜጠኞ ስኬታቸውን ብቻ እንዲያወሩ ይፈልጋሉ፡፡ ነገሩ የተገላቢጦሽ ሲሄድም የሚወስዱትን እርምጃ በ21 ዓመታት አመራራቸው አሳይተውናል፡፡

መለስ ሳያነቡት እንደማያመልጣቸው የነገሩን The Economist ከሞታቸው በኋላ በጻፈው ጽሑፍ ‹‹መለስ አምባገነንነት ተቀባይነት እንዲያገኝ ሰርተዋል›› በማለት አስታውሷቸዋል፡፡


ኢትዮ-ኤርትራዊነት

መለስ ኦነግ፣ ኦብነግንና ምንም ሪፖርት የተደረገ ጥፋት ሰርቶ የማያውቀውን ግንቦት ሰባትን በአሸባሪነት ሲፈርጁ ለስንት እልቂት ሰበብ የሆነውን ‹‹ሻዕቢያ››ን አሸባሪ ያላሉት በእርሳቸው መስፈርት ስላልሆነ ከመሰላችሁ አትሸወዱ፡፡ ቤተሰባቸው ስለሆነ ነው፡፡ መለስ ለኤርትራ እና ለኢሳይያስ ጥልቅ ፍቅር ነበራቸው፡፡ የ‹‹ትሮይ ፈረስ›› የሚለውን መጽሐፍ ካነበባችሁ ‹‹ኅወሓት››ን ማን ጠፍጥፎ እንደሰራው ይገባችኋል፡፡ በእናታቸው ኤርትራዊ የሆኑት መለስ ኅወሓት ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረ በኋላ ለኢሳይያስ ኤርትራን የመገንጠል እና የአሰብ ወደብን የመቀማት ሕልም ተባባሪ ሆነዋል፡፡ በትግል ወቅት የሚሰነዘሩ ሐሳቦችን ‹‹የኤርትራ ሕዝብ ትግል ባፍጢሙ አይደፋም›› የሚል መጽሐፍ በመጻፍ በጠብመንጃም በጽሑፍም ታግለዋል፡፡
አገር ወዳድ - የአገር ጠላት

መለስ - በተለይ በስልጣናቸው መጨረሻ ሰሞን አገር ወዳድ ለመምሰል ይጥሩ ነበር፡፡ በተቃራኒው ታሪካችንን በመቶ ዓመት ሲቀጩት፣ ባንዲራችንን ከተራ ጨርቅ በላይ ፋይዳ እንደሌለው ሲነግሩን ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ ‹‹አገር ማለት ሕዝቡ ነው›› ባሉበት አፋቸው ‹ለልማቱ (ለሕንፃና መንገዱ) ሲባል ሕዝቡ ይጎሳቆል› ብለውበታል፡፡ ልዩነቱ የሚጎሳቆለው ሕዝብ እና የሚጣሰው ሰብአዊነት የእርሳቸውን እና የቤተሰባቸውን በር አያንኳኳም፡፡ ኤርትራን ያህል ሃገር እና አሰብን የሚያህል ወደብ አሳልፈው ሰጥተው፣ መልሰው ደግሞ ባድሜን ለምታክል ቁራጭ መሬት 120 ሺ ሰው ይገብሩብናል፡፡

ኢኮኖሚያዊ ዕድገት እና ድህነት

የመለስ ኢትዮጵያ ባለፉት ስምንት ዓመታት ‹‹በሁለት ዲጂት›› አድጋለች፡፡ ሕዝቡ ግን ከመቼውም የበለጠ ድህነት ውስጥ ገብቷል፡፡ የገንዘብ ግዥበቱ ዕድገት በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ አይታወቅም፡፡ እርግጥ ነው በርካታ መንገዶች ተሰርተዋል፣ ብዙ ሕንፃዎች ቆመዋል ነገር ግን ኢሕአዴግ በገባ በ10 ዓመቱ በቀን ሦስቴ አበላዋለሁ ብለው ቃል ገብተውለት የነበረውን ሕዝብ በ20 ዓመታቸውም አላበሉትም፡፡

እውነቱን እየተነጋገርን ስለሆነ የተሰሩት ሕንፃዎች የማን ናቸው የሚለውን ጥያቄም መልሰን እንለፍ፡፡ በፊት በታታሪ ሰራተኝነታቸው የኢዲስ አበባን ግማሽ ሃብት ተቆጣጥረው የነበሩት ነጋዴዎችና ባለሃብቶች ጉራጌዎች ነበሩ፡፡ ዛሬስ? ኢሕአዴግ ከገባ ወዲህ የተሰሩትን ሕንፃዎች ብትቆጥሩ ከግማሽ በላይ ለሚሆኑት ባለቤት የትግራይ ልጆች ናቸው፡፡ በ20 ዓመት ይህን ሁሉ ሀብት ያፈሩት በምን ጥበብ ነው?

ንግግር አዋቂው ተሳዳቢ

ንግግር አዋቂ (አንደበተ ርቱዕ) ሰዎች አይሳደቡም፤ ምክንያቱም በንግግራቸው ማሳመን ይችላሉ፡፡ ስድብ በንግግር ማሳመን ያልቻለ ሰው ውጤት ነው፡፡ መለስ ዜናዊ ንግግር ሆነ እንዲሁም በጥቅሉ አዋቂነታቸው በሰፊው ይወራላቸዋል፡፡ ይህንን ግን በቅጡ ላጤነው የቱ’ጋ እንደሆነ ለማወቅ ይቸግራል፡፡ አንደበተ ርቱዕነት በንግግር ለዛ ማሳመን እንጂ ቃላትን በመሰንጠቅ፣ አዳዲስ የስያሜ ባጅ በመለጠፍና በማደናገር የሚፈጠር አይደለም፡፡ ስለፖሊሲያቸው ሲጠየቁ ‹ፊዚካል ፖሊሲ› የሚባል የለም ‹ፊስካል ፖሊሲ› ነው የሚባለው የሚል ዋና መስመሩን የሳተ ‹‹የፉጨት›› ሌክቸር መስጠት ያምራቸዋል፡፡ ከአንደበተ ርቱዕ ሰዎች በማይጠበቅ መልኩ ‹‹የገማ፣ የበከተ፣ የበሰበሰ፣ ደደብ…›› የሚሉ ስድቦችን በሕዝብ ፊት ደጋግመው ተሳድበዋል፡፡

አሁን መለስ ሞተዋል፡፡ ቀብራቸው በእልፍ ሺህ (እውነት እየተነጋገርን አይደል፤ ከነዚህ ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በትግራይ ተወላጆች፣ ወደሩብ  በሚጠጉ አባሎቻቸውና የስርዓቱ ተጠቃሚዎች እና ወደሩብ በሚጠጉ ግራ የገባቸው ሰዎች) አጀባ፣ በኢቴቪ እና ሬዲዮዎች ፕሮፓጋንዳ ይካሄዳል፡፡ የፕሮፓጋንዳው መዓት ‹‹ሳያዩ የሚያምኑትን›› ብዙሐን ኢትዮጵያውያንን ለኢሕአዴግ እንደሚመለምል አልጠራጠርም፡፡ ቢሆንም ግን መለስ ሲሞቱ (የመሪ ሳይሆን የስርዓት ለውጥ ነው በማለት) ንቄው የነበረውን የሕልፈታቸውን ብስራት ዛሬ አግኝቸዋለሁ፡፡

ከመቶ፣ ሁለት መቶ ዓመት በኋላ መለስ ሲታወሱ በሕንፃና ቀለበት መንገድ ሊታወሱ አይችሉም፣ ዘመኑ አይፈቅድላቸውም፡፡ የኤርትራ ጉዳይም ቢሆን አሉታዊ ነው፡፡ ሊታወሱ የሚችሉበት አንድ ብቸኛ አማራጫቸውን ተፈጥሮ ነጥቋቸዋል፡፡ መለስ ሦስት ዓመት ቢቆዩና እንዳሉትም ስልጣን ቢለቁ ኖሮ በኢትዮጵያ ታሪክ ስልጣኑን ‹‹በፈቃዱ›› የለቀቀ የመጀመሪያው መሪ ይሆኑ ነበር፤ አመለጣቸው፡፡

Monday, August 20, 2012

ፋጡማ ኖረች አልኖረች፣ ጳጳሱ ኖሩ አልኖሩ…?


አቡነ ጳውሎስን እጅግ በጣም አወዛጋቢ ከሆኑ ኢትዮጵያውያን ተፅዕኖ ፈጣሪዎች ተርታ እመድባቸዋለሁ፡፡ ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊት ለክብራቸው የቆመላቸው ሐውልት ሲገነባ አገር ምድሩ ሌላ አጀንዳ አጥቶ ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹ሰው በቁሙ ለምን ሐውልት ያሰራል?› የተሰኘ ጽሑፍ በአንባቢ ቁጥር ተወዳዳሪ የተገኘለት ባለፈው ሳምንት የታወጀው የሞታቸው ዜና ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ የተቀረጸበት የስነ ምግባር ወግ ሰው ከሞተ በኋላ ማክበር ላይ ስለተመሰረተ፣ ሙት ወቃሽነት ከነውሮች ሁሉ የከፋ ነውር ነው፡፡ ስለዚህ ሰሞኑን የማይወዷቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ምዕመናን ሳይቀሩ ‹‹ነፍስ ይማር›› መባባልን እንደትልቅ ቁምነገር፣ በተቃራኒው ደግሞ ‹‹ሞታቸውን እንደመልካም አጋጣሚ›› የሚቆጥሩትን እንደ አጥፊ በመታዘብ ላይ ናቸው፡፡ እኔም በበኩሌ ስለአቡኑ አወዛጋቢ ዐበይት የታሪክ ትውስታዎች ከአወራሁ በኋላ፣ ሃይማኖተኛ ባልሆንም ስለ‹በሰላም ይረፉ ማለት ማንን ገደለ?› ለሚለው ጥያቄ የራሴን እምቢታ ለመስጠት በዚህ ጽሑፍ መጥቻለሁ፡፡

ማዕረጋቸው አንድ አንቀጽ የሚደርስላቸው አቡነ ጳውሎስ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ እምነት ውጪ ላሉት ሁሉ የተመቹ ነበሩ፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ አማኞች ዘንድ ግን መልካም ስም የላቸውም፡፡ የስማቸው መበላሸት የሚጀምረው ደግሞ ወደ መንበረ ጵጵስናው የመጡበት መንገድ ላይ ይጀምራል፡፡

ጳጳሱ እንደአብዛኛዎቹ የፖለቲካ መሪዎቻችን ሁሉ፣ ከትግራይ ክልል ያውም ከአድዋ ነው የፈለቁት፡፡ ኢሕአዴግ አዲስ አበባን በተቆጣጠረ በዓመቱ፣ አቡነ መርቆርዮስ ተሰድደው እርሳቸው ጳጳስ ለመሆን በቁ፡፡ ከዚያ በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን ከየትኛውም ቤተ ሃይማኖት የበለጠ መስዋእትነት ስትከፍል ነበር፡፡ Haustein & Østebø የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ቁጥር በኢትዮጵያ ከ54 በመቶ ወደ 43.5 በመቶ የወረደው በኢሕአዴግ ወይም በአቡነ ጳውሎስ ዘመን እንደሆነ ይነግሩናል፡፡

Friday, August 10, 2012

ጫወታ ስለ ‘የኦሎምፒክ ጫወታዎች’


እንደመታደል ሆኖ ከ200 በላይ አገሮች ጋር ተፎካክረን እስከ 20ኛ የሚደርስ ደረጃ የምናገኝበት ብቸኛው መድረክ የኦሎምፒክ ጫወታዎች ነው፡፡ (ማን ነበር ‹የምንወዳደረውም ሆነ የምናሸነፈው በአትሌቲክስ ብቻ፣ ከአትሌቲክስም በሩጫ ብቻ፣ ከሩጫም በረዥም ርቀት ብቻ› ብሎ ከዓመታት በፊት ‹ጭብጨባ አታብዙ› ያለን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ? እርግጥ ነው፣ ዘንድሮስ አልተሳካም እንጂ አጭር ርቀትም፣ ዋናም ሞካክረናል በሉልኝ!!!)

ጫወታ አንድ፤ የኦሎምፒክ ፉክክር ፖለቲካ

የዓለምአቀፍ ኦሎምፒክ ኮሚቴው በኦሎምፒክ ቻርተሩ ምዕራፍ አንድ ክፍል ስድስት ላይ ‹‹የኦሎምፒክ ጫወታ ፉክክሮች በግለሰቦች ወይም በቡድኖች ብቻ እንጂ በአገራት መካከል አይደለም…›› ይላል፤ ድንቄም! እና ታዲያ ለምንድን ነው ግለሰቦቹ በአገራት ተከፋፍለው የሚጫወቱት፣ ለምንድን ነው ሲያሸነፉ የአገራቸው ብሔራዊ መዝሙር የሚዘመረው፣ ለምንድን አገራት ባገኙት የወርቅ ቁጥር ደረጃ የሚሰጣቸው? እኛ እንደሆንን የምንደሰተውም ሆነ የምናዝነው ነገሩን ያገር ጉዳይ አርገነው ነው፡፡

ጫወታ ሁለት፤ ኢትዮጵያ በኦሎምፒክ

ኢትዮጵያ የለንደኑን ጨምሮ በ13 የበጋ ኦሎምፒክ ጫወታዎች ላይ ተሳታፊ ሆናለች፡፡ ከነዚህ ውስጥ ከሦስቱ በስተቀር በሁሉም ሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ ገብታለች፡፡ ሜዳልያ ሰንጠረዥ ውስጥ ከገባችባቸው 10 ጫወታዎች ውስጥ አንድም ወርቅ ያላገኘችው በሙኒክ ኦሎምፒክ ነው፡፡

በኦሎምፒክ መድረክ የለንደን ኦሎምፒክን ሳይጨምር 38 ሜዳሊያዎችን ስታገኝ፣ ሲተነተኑ 18 ወርቅ፣ 6 ብር እና 14 ነሐሶች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ (እና በአፍሪካ) የኦሎምፒክ ታሪክ የመጀመሪያውን ወርቅ ያስገኘው አበበ ቢቂላ ሲሆን፣ በሴቶች ደግሞ ደራርቱ ቱሉ ናት፡፡ ኢትዮጵያ ብዙ ሜዳልያዎች (8) ያገኘችው በሲድኒ ኦሎምፒክ ሲሆን፣ በአቴንስ እና ቤጂንግ ኦሎምፒኮች በያንዳንዳቸው ሰባት አግኝታለች፡፡

የለንደን ኦሎምፒክን ሳይጨምር፣ በተገኙት ሜዳሊያዎች ድምር ኢትዮጵያ ከዓለም የኦሎምፒክ አገራት አንፃር 40ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡