Pages

Friday, March 1, 2013

#Ethiopia: የአድዋ [ዕ]ድል


መቶ ዐሥራ ሰባት ዓመት ወደኋላ፤ መጀመሪያ (ከዚህም ዓመታት በፊት) አውሮጳውያን ኃያላን በበርሊን ያደረጉት ‹‹አፍሪቃን የመቀራመት›› ስምምነት ይቀድማል፡፡ ሁሉም የየራሳቸውን ሲወስዱ፣ ጣሊያንም ኢትዮጵያ (እና ሶማሊያ…) ደርሰዋት ነበር፡፡ የመጀመሪያው የጣሊያን ጦር በባሕርምላሽ (የአሁኗ ኤርትራ) በኩል ሲመጣ የወቅቱ የባሕርምላሽ ገዢ የነበሩት የራስ አሉላ እንግዳ (አባ ነጋ) ሠራዊት የጣሊያንን ሠራዊት ዶጋሊ ላይ በተደረገ ፍልሚያ ከ500 ወታደር 100 ብቻ በሕይወት አስቀርቶ መለሰው፡፡ ያኔ የጣሊያን ፓርላማ ተሰበሰበ፤ ተሰብስቦም አላበቃ በ332 ለ40 አብላጫ ድምፅ ወደኢትዮጵያ ተጨማሪ (5000ሺ ወታደር የያዘ) ሠራዊት ለመላክ ወሰነ፡፡

ከዚያ በኋላ ነው የውጫሌ ውል የተከተለው፡፡ ለጠነከረ ወዳጅነት እና ለጋራ ተጠቃሚነት በምኒልክ እና በጣልያን መልእክተኛ መካከል የተፈረመው የውጫሌ ውል ደግሞ አማርኛውና ጣልያንኛው አንድ ዓይነት ትርጉም ይኑረው ቢልም አንቀጽ 17 ‹‹ኢትዮጵያ የጣልያን ሞግዚት›› እንድትሆን በተዘዋዋሪ የሚያታልል ነበር፡፡ ትርጉሙ ሲነቃበት ዐጤ ምኒልክ ውድቅ ከማድረግ አልተመለሱም፡፡ እንግዲህ የአድዋ ጦርነት መነሻ የሚባለው ይህ ቢሆንም፣ ኢትዮጵያ ለኢጣሊያ የበርሊን ስምምነት ሽልማት መሆኗ ግን መሠረቱ ነው፡፡

ጦርነቱ ሲጀመር አገር ዘመተ፡፡ 80,000 ኢትዮጵያውያን ለጦርነቱ ሲወጡ ከነዚህ ውስጥ ቆመህ ጠብቀኝ ጠብመንጃ የታጠቁት ጥቂቶቹ ነበሩ፡፡ ሌላው ጦርና ጋሻውን እየሰበቀ ወጣ፡፡ በጣሊያን በኩል ደግሞ 18,000 ወታደሮች ተሰለፉ፡፡ የአገር ፍቅር፣ የጀግንነት እና የአትንኩኝ ባይነቱ ጦርነት ተጀመረ፡፡ ጀግኖች ተጋደሉ፤ በዕለቱ ጦርነት ማብቂያ ላይ የጣልያን ሠራዊት በአውሮጳውያን የቅኝ ገዢነት ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ እልቂት አስተናገደ፡፡ እስከ 7,000 የሚገመቱ የጣሊያን ወታደሮች ሞቱ፣ 3000 ያህል ተማረኩ፤ በኢትዮጵያ ወገንም 4,000 የሚጠጉ ተሰዉ፣ የቆሰሉት ደግሞ ከ10,000 በላይ ነበሩ፡፡ ድል ለኢትዮጵያ ሆነ፡፡