Pages

Tuesday, July 10, 2012

እውነቱ እና ፍርሃቱ


የፍራቻ ፖለቲካ እና የፖለቲካ ፍራቻ - ጥንድ በኢትዮጵያ መሪዎችና ሕዝቦች መሀል የተጋረጡ የጦር መሳሪያዎች ናቸው፡፡ ሕዝቡ ካልፈራ ፖለቲከኞቹ የፍራቻ ፖለቲካ ይጫወታሉ፣ ፖለቲከኞቹ የፍራቻ ፖለቲካ ካልተጫወቱ ሕዝቡ ፖለቲካን ይፈራል፡፡ የሁለቱም ውጤት አንድ ነው፤ ውጤቱም ሕዝቡ መሪዎቹን የሚያስከፋ ነገር መናገርም ሆነ መተግበር ይፈራል፡፡

የፍራቻ ፖለቲካ፤ በገዢው እና ተቃዋሚዎቹ
ጥንት፣ ወትሮም ንጉሥ የማይከሰስ በመሆኑ መንግስታት ሕዝቦቻቸውን ማስፈራራታቸው የደንብ ያህል ነበር፡፡ ‹‹የተማረ ይምራን›› መባል ከተጀመረበት እና ደርግ የንጉሡን መንበር ከተረከበበት ጊዜ ወዲህም ግን ‹‹ደንቡ›› አልቆመም፡፡ ደርግ ‹‹አብዮቱን›› ሊቀለብሱ የሚንቀሳቀሱትን በሙሉ እንደማይምራቸው በሕዝብ ፊት ምሎ ዘመተባቸው፡፡ አብዮቱን ከሚቀለብሱት እንዳንዱ ላለመሆን የፈራ በሙሉ የኢሠፓ አባል ሆኖ በወንድሙ ላይ ዘመተ፡፡ ቀሪው ‹‹መሀል መስፈር›› የፈለገውም፣ ከፍራቻው’ጋ እንደተሟገተ 17 ዓመታት ኖረ፡፡

ኢሕአዴግ ቀርቶ የፍራቻ ፖለቲካ የቀረ ከመሰለ በኋላ ግን መልኩን ቀይሮ መጣ፡፡ አብዮቱን መቀልበስ፣ ሕገመንግስቱን መቀልበስ በሚል ተተካ፡፡ መንግስት የተቃወመውን ሁሉ በሆነ ስም በመፈረጅ ስለሚወነጅል፣ ላለመፈረጅ የሚሰጋው ሁሉ ወደወጣበት ምሽግ ተመልሶ ገባ፡፡ ‹‹ፖለቲካ እና ኮረንቲ›› የሚለው አባባል የተፈጠረው ያኔ ነው፡፡

የፍራቻ ፖለቲካን፣ ኢሕአዴግ በሌላም አካሔድ ይጫወትበታል፡፡ እንደገዢው ፓርቲ ዲስኩር ከሆነ፣ ኢሕአዴግ ከወረደ ወይም ተቃዋሚዎች ወደስልጣን ከወጡ የብሔር ብሔረሰቦች ጥያቄ/ነፃነት ተዳፍኖ ይቀራል፣ የሃይማኖቶች እኩልነት አደጋ ላይ ይወድቃል፣ ልማቱ ይደናቀፋል… ወዘተ፣ ወዘተ፡፡

የዚህኑ ግልባጭ ተቃዋሚዎችም ይጠቀሙበታል፡፡ ኢሕአዴግ ካልወረደ ብሔር ብሔረሰቦች እርስ በእርሳቸው ይባላሉ፣ የኢትዮጵያ አንድነት እመቃብር ይወርዳል፣ ሃይማኖተኞች ጽንፈኛ ይሆናሉ፣ ኢኮኖሚው ተጣምሞ ይቀራል… ወዘተ፣ ወዘተ፡፡ ሙግቶቹ እውነትነት ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ነገር ግን የፖለቲካዊ ጫወታም ሆነ የምጣኔ ሃብታዊ ትንታኔ እና ትንቢት ለማይገባው ምስኪን ግን ያኛው ከመጣ፣ ይሄኛው ከወረደ ወይም ያኛው ካልመጣ ይሄኛው ከሰነበተ ነገሩ ሁሉ ምስቅልቅሉ ወጥቶ፣ ሕዝቦች ሁሉ አደጋ ላይ ወድቀው…በሚል ፍርሃት ሙሉ ራዕይ ታቅፎ ይቀራል፡፡ ለሁሉም እንደመፍትሄ የሚቆጥረው ደግሞ ሽሽት /ስደትን/ ነው፡፡

የፖለቲካ ፍራቻ፤ በተመልካቹ ሕዝብ
2011 Legatum Prosperity Index፤ ኢትዮጵያን ከ110 አገሮች ጋር አወዳድሮ በብልፅግናዋ 108ኛ ባስቀመጠበት ሪፖርቱ Safety & Security ንዑስ ዘርፍም 106ተኛ ይበቃሻል ለማለት ያበቃውን ምክንያት ሲዘረዝር፣ “The Ethiopian government has been known to engage in political violence and, globally, Ethiopia is the country where expression of political views is perceived by the population to be most restricted. This may be contributing to the rate of flight of professionals, intellectuals, and political dissidents, which is among the 20 highest rates in the world.” (‹‹የኢትዮጵያ መንግስት በፖለቲካዊ አመጾች ላይ እጁን በማስገባት ይታወቃል፣ በዓለምአቀፍ ደረጃም ኢትዮጵያ ፖለቲካዊ አመለካከትን ማንፀባረቅ በጣም የተገደበባት አገር ተደርጋ በዜጎቿ ትታሰባለች፤ ይህ ምናልባትም፣ ከዓለማችን ችግሩ የከፋባቸው 20 አገራት መካከል ኢትዮጵያን ላሰለፋት፥ የባለሙያዎች፣ ምሁራን እና ፖለቲከኞች ስደት መንስኤ ሳይሆን አይቀርም፡፡››) ብሏል፡፡

Personal Freedom ብሎ በሰየመው ንዑስ ዘርፍም ኢትዮጵያ ውራ (110ኛ) ሆናለች፡፡ ሲዘረዝረውም እንዲህ ብሎ ነው፤ “Ethiopia ranks among the bottom 10 countries for citizens’ freedoms in expression, belief, association, and personal autonomy.” (‹‹ኢትዮጵያ ለዜጎቿ ሐሳብን፣ እምነትን፣ ማሕበርን፣ እና  የመግለፅ ነፃነት፣ እና የግል አቋምን ለማንፀባረቅ ከማይመቹ የዓለማችን 10 አገሮች ተርታ ትሰለፋለች፡፡››)

ሐሳብን ለመግለፅ ካለመቻል ጀርባ ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን የማይገልፁት/ለመግለጽ የሚፈሩት ፖለቲካዊ አመለካከታቸውን ብቻ አይደለም ሃይማኖታዊ፣ ፆታዊ ጉዳዮቻቸውንም ጭምር ነው፡፡ ለዚህ አንዱ አስተዋፅዖ አዋጪ ‹‹የመቻቻል ምሳሌ›› የሚባለው ነገር ግን ‹‹መቻቻልን›› በጥያቄ ምልክት ውስጥ ያስቀመጠው ባሕላችን ነው፡፡ ‹‹መቻቻል›› በአገራችን አናሳው ብዙሐኑን ሲችል በሚል እሳቤ ተውጦ መክረሙ አጨቃጫቂ አይደለም፡፡ ስለዚህ አፈንጋጭ አመለካከቶች እውነታ ቢኖራቸውም እንኳን ተቀባይነት አይኖራቸውም፣ ሌላው ቀርቶ አፈንጋጭ አሳቢው ከሐሳቡ’ጋ ተግባብቶ እንዳይኖር ዱላ ይበዛበታል፡፡ ይህ ባሕል የወለደው ፍራቻ ፖለቲካዊ አስተሳሰብን የማንፀባረቅ፣ አንፀባርቆ ተቀባይነት የማጣት ፍራቻን ይወልዳል፡፡

ሕዝባችን ይፈራል፣ እንዲፈራም ታሪኩ ያስገድደዋል፤ ነገር ግን የሚፈራው በብትር የሚቀጣውን መንግስት ብቻ ሳይሆን በቃላት እና በማግለል የሚቀጣውን የራሱን ማኅበረሰብም ጭምር ነው፡፡ በዚህም የራሱን ሐሳብ ለራሱ አፍኖ በማለፍ ለአገሪቱ ለውጥ የሚበጁ በርካታ አማራጭ ሐሳቦችን አፍኖ ገድሏል፡፡ ይህንን ዓይነቱን ሕዝባዊ ፍራቻ አምባገነን መንግስታት ይፈልጉታል፣ እንዲለመልም እንጂ እንዲኮሰምን አያደርጉም፡፡ ለአምባገነን መንግስታት፣ ፍርሃት ከሰራዊቱ ይልቅ ሕዝቡን ከተቃውሞ ያቅብላቸዋል፡፡

በአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ደፋር ጋዜጠኞች፣ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች እና አፈንጋጭ ሃይማኖተኞች ሲገደሉ ነበር፣ እየታሰሩ እና እየተሳደዱ ነው፡፡ ይህ እውነታ ግን ከሕዝባዊው የፍራቻ አድማስ የበለጠ አይደለም፡፡ በግሌ የኢሕአዴግ መንግስትን ካጠነከሩት ጉዳዮች መካከል የሕዝቡ ፍራቻውን ከእውነተኛው ስጋት (risk) በላይ ማግነን እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ለዚህም ነው ይህንን መጻፌ!

"መፍራት ያለብን ብቸኛው ነገር ፍርሃትን እራሱን ነው" እንዲሉ ፍራንክሊን ዲ. ሩዝቬልት፣ ፍርሃታችንን እንፍራው፡፡

2 comments:

  1. Thanks Befekadu,

    I think that is the only ethiopian problem specially at this particular moment. It suffices to see the arab spring, the syrian crisis. These people do not know what "Fear" means. They are risking their lives, they are dying but they still continue.

    ሁሌም እኮ ድፍረት ካለ, risk አለ. ያልተበጠበጠ አይጠራም::

    ReplyDelete