Pages

Friday, August 10, 2012

ጫወታ ስለ ‘የኦሎምፒክ ጫወታዎች’


እንደመታደል ሆኖ ከ200 በላይ አገሮች ጋር ተፎካክረን እስከ 20ኛ የሚደርስ ደረጃ የምናገኝበት ብቸኛው መድረክ የኦሎምፒክ ጫወታዎች ነው፡፡ (ማን ነበር ‹የምንወዳደረውም ሆነ የምናሸነፈው በአትሌቲክስ ብቻ፣ ከአትሌቲክስም በሩጫ ብቻ፣ ከሩጫም በረዥም ርቀት ብቻ› ብሎ ከዓመታት በፊት ‹ጭብጨባ አታብዙ› ያለን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ? እርግጥ ነው፣ ዘንድሮስ አልተሳካም እንጂ አጭር ርቀትም፣ ዋናም ሞካክረናል በሉልኝ!!!)

ጫወታ አንድ፤ የኦሎምፒክ ፉክክር ፖለቲካ

የዓለምአቀፍ ኦሎምፒክ ኮሚቴው በኦሎምፒክ ቻርተሩ ምዕራፍ አንድ ክፍል ስድስት ላይ ‹‹የኦሎምፒክ ጫወታ ፉክክሮች በግለሰቦች ወይም በቡድኖች ብቻ እንጂ በአገራት መካከል አይደለም…›› ይላል፤ ድንቄም! እና ታዲያ ለምንድን ነው ግለሰቦቹ በአገራት ተከፋፍለው የሚጫወቱት፣ ለምንድን ነው ሲያሸነፉ የአገራቸው ብሔራዊ መዝሙር የሚዘመረው፣ ለምንድን አገራት ባገኙት የወርቅ ቁጥር ደረጃ የሚሰጣቸው? እኛ እንደሆንን የምንደሰተውም ሆነ የምናዝነው ነገሩን ያገር ጉዳይ አርገነው ነው፡፡

ጫወታ ሁለት፤ ኢትዮጵያ በኦሎምፒክ

ኢትዮጵያ የለንደኑን ጨምሮ በ13 የበጋ ኦሎምፒክ ጫወታዎች ላይ ተሳታፊ ሆናለች፡፡ ከነዚህ ውስጥ ከሦስቱ በስተቀር በሁሉም ሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ ገብታለች፡፡ ሜዳልያ ሰንጠረዥ ውስጥ ከገባችባቸው 10 ጫወታዎች ውስጥ አንድም ወርቅ ያላገኘችው በሙኒክ ኦሎምፒክ ነው፡፡

በኦሎምፒክ መድረክ የለንደን ኦሎምፒክን ሳይጨምር 38 ሜዳሊያዎችን ስታገኝ፣ ሲተነተኑ 18 ወርቅ፣ 6 ብር እና 14 ነሐሶች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ (እና በአፍሪካ) የኦሎምፒክ ታሪክ የመጀመሪያውን ወርቅ ያስገኘው አበበ ቢቂላ ሲሆን፣ በሴቶች ደግሞ ደራርቱ ቱሉ ናት፡፡ ኢትዮጵያ ብዙ ሜዳልያዎች (8) ያገኘችው በሲድኒ ኦሎምፒክ ሲሆን፣ በአቴንስ እና ቤጂንግ ኦሎምፒኮች በያንዳንዳቸው ሰባት አግኝታለች፡፡

የለንደን ኦሎምፒክን ሳይጨምር፣ በተገኙት ሜዳሊያዎች ድምር ኢትዮጵያ ከዓለም የኦሎምፒክ አገራት አንፃር 40ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡

የለንደን ኦሎምፒክ ፓርክ
ጫወታ ሦስት፤ ኢትዮጵያዊ ኦሎምፒክ በጾታ

ከለንደን ኦሎምፒክ በፊት በተደረጉ ጫወታዎች …. ሜዳሊያ በወንዶች እና … ሜዳሊያ በሴቶች ለኢትዮጵያ ገቢ ተደርገዋል፡፡ ከባርሴሎና ኦሎምፒክ ወዲህ እስከ ቤጂንግ በሴቶች 14 ሜዳሊያ በወንዶች ደግሞ 13 ሜዳሊያዎች ተገኝተዋል፡፡ በዘንድሮው የለንደን ኦሎምፒክም እስካሁን በተገኙት አራት ሜዳሊያዎች ውስጥ ከአንዱ ነሐስ በስተቀር ሦስቱ በሴቶች የተገኙ ናቸው፡፡

ጫወታ አራት፤ የኦሎምፒክ ድል ኢኮኖሚ

በኦሎምፒክ ድል ብዙ ገንዘብ አይገኝም፤ ክብር እና ስም እንጂ፡፡ በኦሎምፒክ ድል ግን የአገራት ኢኮኖሚ ይገለጣል፡፡ ኢኮኖሚያቸው ትልልቅ የሆኑ አገራት ብዙ ሜዳሊያዎችን የማግኘት ዕድላቸው የሰፋ ነው፡፡ ለምሳሌ የተባበሩት የአሜሪካ አገራት (United States of America) 3ተኛ ከወጣችበት የሞንትሪያል ኦሎምፒክ በቀር በሁሉም አንደኛ ወይም ሁለተኛ ስትወጣ ኖራለች፡፡ በምጣኔ ሐብት ደረጃ መጤ የምትባለው ቻይና ደግሞ ከአትላንታ ኦሎምፒክ ጀምሮ በአገሯ እስካሰናዳችው ያለፈው የቤጂንግ ኦሎምፒክ ድረስ ከአራተኛ ጀምራ፣ ሦስተኛ፣ ሁለተኛ፣ እያለች አንደኛ ለመሆን በቅታለች - ልክ እንደGDPዋ ዕድገት ማለት ነው!

ጫወታ አምስት፤ ኢትዮጵያ በለንደን ኦሎምፒክ

ኢትዮጵያ ለለንደን የበጋ ኦሎምፒክ የላከቻቸው ስፖርተኞች ቁጥር 34 ነው፡፡ ሁለቱ ዋናተኞች ሲሆኑ ቀሪዎቹ አትሌቶች ናቸው፡፡ እስካሁን በኦሎምፒክ ታሪካችን በ10,000 ሜትር ሴቶች አራት የወርቅ ሜዳሊያ ስናገኝ አራቱም አንድ ቤተሰብ ውስጥ ገብተዋል፡፡ ሁለቱን ጥሩነሽ ዲባባ በቤጂንግ እና ለንደን ኦሎምፒክ ስትወስድ፣ አክስቷ ደራርቱ ቱሉ ደግሞ የባርሴሎናውን እና የሲድኒውን ወስዳለች፡፡ ሜዳሊያዎችን አንድ ቤተሰብ ውስጥ በማስቀረት ታሪኩ በቀለም የራሱ ድርሻ አለው፤ የ10,000 ሜትር ነሐስ አጥልቋል - ለንደን ላይ፡፡

በሴቶች ማራቶን ደግሞ በአፍሪካ የመጀመሪያውን የኦሎምፒክ ወርቅ ፋጡማ ሮባ በአትላንታ ኦሎምፒክ ካመጣች በኋላ በአራተኛው ኦሎምፒክ ዘንድሮ ቲኪ ገላና ወደቤቱ መልሳዋለች፡፡ በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ በመሰናክል ዝላይ (3000 ሜትር) በሶፊያ አሰፋ ሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ ለመግባት በቅተናል፡፡ በዘንድሮው ኦሎምፒክ ሴቶች ወንዶችን በውጤት እያስከነዱ ነው፤ መጨረሻውስ?

No comments:

Post a Comment