Skip to main content

እውትም ‘ሰሚ ያጡ ድምፆች!’


መጀመሪያ እንዲህ ነበር፤
“የኛ ሙሽራ ኩሪ ኩሪ፣
አገባሽ አስተማሪ፡፡”

ከዚያ በኋላ፤
(በጓደኛዬ እርዳታ ርዕሱን ያስታወስኩት የዶ/ር በፍቃዱ ‹ሰሚ ያጡ ድምፆች› ላይ እንደሰፈረው)
መምህራን በየክፍለሃገራቱ ተሰማርተው የነበረ ቢሆንም ደሞዛቸው 202 ብር (ቱኦቱ) ብቻ ነበር፡፡ መምህራኑ ይቺን ‹ቱኦቱ› ምን ከምን እንደምን እንደሚያደርጓት ይቸግራቸው ነበር፡፡ ስለዚህ እንደመፍትሔ ሌላ መምህርት በማግባት ወጪን በመጋራት ገቢን 404 ብር (ፎር-ኦ-ፎር) ለማደረስ ይጥሩ ነበር፡፡ (ትዳር ትርጉሙ ገቢን ማሳደግ ወይም ወጪን መጋራት እንጂ ፍቅር አልነበረም ማለት ነው፡፡) ይሄ ነገር እየተለመደ ሲመጣ የመምህር ሚስት መምህርት (ወይም የመምህርት ሚስት መምህር) ‹ፎሮፎር› የሚል ቅፅል ተሰጣቸው፡፡ “ፎሮፎሬን ተዋወቃት” ማለት ልክ “ባለቤቴን ተዋወቃት” እንደማለት ሆነ፡፡

ትንሽ ከረምረም ሲል ደግሞ፤

ባል ሳታገባ ዕድሜዋ እያመለጣት የመጣች ሴት ስትገኝ መንደሬው “ምነው ቆንጂት ምንስ ባል ቢጠፋ መምህር አጣሽ?” ይባል እንደጀመር ዶ/ሩ በዚያው መጽሃፋቸው ላይ መግለፃቸው ይታወሰኛል፡፡

ሰሞኑን፤
መምህራኑ ክብራችንን የሚነካ ነው ያሉትን - ለዲፕሎማ ምሩቅ የ31 ብር እና ለዲግሪ ምሩቅ የ73 ብር የደሞዝ ጭማሪ ያደረገው መንግስት “ጭማሪው የመምህርነትን ሙያ ክብር የሚያስጠብቅ ነው” እያለ ነው፡፡

እንዴት ነው ነገሩ?
መምህራን ሀገር መሪ ናቸው፡፡ እነርሱ የሚፈጥሩት ትውልድ ነው ሃገርን የሚረከበው (የሚመራው)፣ መምህራን ቤተሰብ መረን የለቀቀውን ልጅ ነው አር’ቀው (አቅንተው/አርቅቀው) የሚያሳድጉት፣ መምህራን የእያንዳንዱን ዜጋ ሕይወት መስመር የማስያዝ ሥራ ነው የሚሰሩት፡፡ የመምህርነትን ያህል ኃላፊነቱ የከበደ ትውልድን የመቅረጽ ሚና የመጫወት ዕድል የሚሰጥ የሥራ ዓይነት አስቤ አይመጣልኝም፡፡

እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ከላይ መግቢያችን ላይ ባየነው መልኩ ‹የመምህራንን ማሕበራዊ ዋጋ እንዲያሽቆለቁል ያደረገው ማን ነው?› ብለን የጠየቅን እንደሁ÷ መልሱ ደሞዛቸው መሆኑን እናስታውሳለን፡፡  

የመምህራን ደሞዝ አነስተኛነት የሥራ ዘርፉ ብቃታቸው ከፍ ያሉ ባለሙያዎች ወደዘርፉ እንዳይገቡና ብቁ ዜጎችን እንዳያፈሩ እየተከላከለ ነው፡፡ ውስጡ ያሉትም ሸሽተው እንዲወጡ፣ ባይወጡም ኃላፊነታቸውን በትጋት እንዳይወጡ ለሞራል ልሽቀት ዳርጓቸዋል፡፡ በዚህ አካሔድ የተሽመደመደው የትምህርት ጥራታችን ባለህበት እርገጥ ማለቱን አያቆምም፡፡ ያውም ባለበት መቆም ከቻለ፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ አገራችን በድህነት እና በኋላ ቀርነት ውራነቷን አስጠብቃ ትኖራለች ማለት ነው፡፡

ሰሞኑን የተደረገው የደሞዝ ጭማሪ በጣም አሸማቃቂ ነው፤ ምናልባትም መምህራኑ ይሄ ከሚጨመርላቸው ‹ቆይ ጠብቁ› ቢባሉ የሚሻላቸው ይመስለኛል፡፡ ኢሕአዴግ የቀድሞዎቹን የመምህራን ማሕበር አመራሮች ከምርጫ 97 በኋላ አሽቀንጥሮ ቢጥላቸውም በእጅ አዙር አዳዲስ አመራሮችን ሾሟል፡፡ አመራሮቹም እውነትም ለሹያሚያቸው ታማኝነታቸውን ለማረጋገጥ ይመስላል የደሞዝ ጭማሪው ተገቢና በቂ እንደሆነ እየደሰኮሩ ነው፡፡ ደግነቱ መምህራኑ ማሕበሩ አይወክለንም ማለት ጀምረዋል - ለእነርሱ የማይሟገት ማሕበር እንዴትስ ይወክላቸዋል?

የኢትዮጵያ መንግስት በአምስት ዓመቱ መጨረሻ፣ በብሔራዊ ባንክ  የአንድ ትሪሊዮን ብር ተቀማጭ ለማድረግ ሕልም አለው፡፡ መልካም ሕልም ነው፡፡ ቢሆንም የሰው ስጋ እየበላ የሚያስቀምጠው ብር ለማን እንደሚሆን ግልፅ ማድረግ አለበት፡፡ የመምህራኑ የደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ የመኖር ጥያቄ እንጂ የቅንጦት ጥያቄ አይደለም፡፡ መምህራኑ ብር እና ክብር ያስፈልጋቸዋል፡፡

አለበለዚያ ግን፤ መንግስት መዘንጋት የማይኖርበት አንድ ነገር አለ፡፡ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መውደቅ ጀርባ፣ ከመንግስቱ ኃይለማርያም መውደቅ ጀርባ እና አሁንም በቅርቡ ከምርጫ 97 ወንበር ነቅናቂ የምርጫ ሒደት ጀርባ መምህራን ጉልህ ሚና ነበራቸው፡፡ አሁንም ቢሆን አምስት ለአንድ የተቦደኑትን ተማሪዎች የሚያስተምሩት፣ ኢሕአዴግ መልምሎ የሾማቸው ዳይሬክተሮች ሳይሆኑ፣ ብሶተኞቹ መምህራኖች መሆናቸውን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡

ያቺ ደጋግመን የሰማናት ቀልድ በጆሮዬ እያቃጨለች አስቸገረችኝ፡፡ ትምህርት በሬዲዮ ላይ ነው፡፡ የሬዲዮዋ መምህር ስለብር ኖቶች እያስተማረች እያለች÷ “እባክዎ መምህር፣ ለተማሪዎቹ የመቶ ብር ኖት አውጥተው ያሳዩዋቸው፤” ትላለች፡፡ መምህሩ ግን ጭጭ - መቶ ብር ከየት ይመጣል?

መምህራን ክብራቸውን ለማስጠበቅ በአቋማቸው መፅናት አለባቸው፡፡ አሁን የአንዳንድ ትምህርት ቤት መምህራን አድማ ቢመቱም፣ ፀጥ ለጥ ብለው ሥራቸውን የቀጠሉ መምህራን መኖር ትግሉን ሕብረት ያሳጣውና ያኮላሸዋል፡፡ ስለዚህ መምህራን የገዛ ክብራቸውን በገዛ አቋማቸው የሚወስኑበት ገደል አፋፍ ላይ ቆመዋል፡፡ ክብራቸውን ገደል ይከቱት ይሆን ወይስ?

ጉዳዩ የአገር ጉዳይ መሆኑን ተማምነናል፡፡ እኛም ከመምህራን ጎን በመቆም ለአገር ጉዳይ ተቆርቋሪነታችንን እናስመስክር፡፡

Comments

Popular posts from this blog

The "Corridor Development" is a Façade of the Prosperity Party

Befekadu Hailu I have seen a news report claiming that 40% of central Addis Ababa will be demolished for the corridor development; I am not able to confirm the validity of the news but it sounds real to me given the size of massive operations in the demolition of old neighborhoods and construction of bike lanes, green areas, and glittering street lights. I like to see some beauty added to my city but cannot help mourning the slow death of it too. Addis Ababa was already in a huge crisis of housing and the demolition of houses is exacerbating it. Apparently, Prime Minister Abiy Ahmed is eager to showcase his vision of prosperity by demonstrating how fast his administration can do magic by beautifying the front sides of the streets with lights, new pavements, and painted fences ("to fake it until he makes it" in my friend's words). Therefore, he and his party do not care about the miserable human stories behind the scenes and they will harass you if you tell it (Azeb Woku...

የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ

በፍቃዱ ዘ . ኃይሉ “የአዲስ አበባ ብሔርተኝነት” ቢኖር ኖሮ መሪው ልጅ ሚካኤል ይሆን ነበር። አሁን አሁን እሱ ስለ አዲስ አበባ የዘፈናቸውን ዘፈኖች ቁጥር ራሱ በትክክል መቁጠር ይቸግረኛል። ለአዲስ አበባ ከተዘፈኑ ዘፈኖቹ ውጪም በየዘፈኑ ውስጥ የሚጨማምራቸው መልዕክቶች በራሳቸው መወድሰ አዲስ አበባ ናቸው። ለምሳሌ፣ በቅርቡ በለቀቀው ‘አዲስ አራዳ’ በተሰኘው አልበሙ ውስጥ ‘የድሬ ልጅ’ የሚል ዘፈን አለው። ዘፈኑ የተዘጋጀው ያው የአዲስ አበባ እህት ተደርጋ የምትቆጠረውን ድሬ ዳዋን ለማወደስ ነበር። ልጅ ሚካኤል ግን የአዲስ አበባ ፍቅሩ ያመልጠውና የሚከተለውን ያቀነቅናል፦ “መጣልሽ በሏት፣ ድሬ ድረስ፣  ከአዱ ገነት፣ ከሸገር፣ ከአዲስ ደረሰ፣... የሸገር ልጅ አራዳ ነው፣ ሰው አክባሪ፣ ሰው ወዳዱ፣ ቀላጅና ተረበኛ፣ ፍቅር ይዞ የሚተኛ፣ ‘አለው’ የለ፣ ‘የለው’ የለ፣ ከሁሉ ጋ፣ ግባ ጀባ...፤” ፤ ልጅ ሚካኤል በዚህ አልበሙ ብቻ አዲስ አበባን የሚያውድሰባቸው ሌሎችም ዘፈኖች አሉ፤ ‘ አዲስ አራዳ ’ የሚለው የአልበሙ መጠሪያ እና ‘ሸገር’ የሚሉት ዘፈኖቹ ዋነኞቹ ናቸው። ታዲያ እንዲህ በአዲስ አበባ ፍቅር የሚቃጠለው ልጅ ሚካኤል "ሊነግረን የሚፈልገው ምንድን ነው?" የሚለው ጥያቄ ደጋግሞ ይመጣብኛል። ይህ የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ ምንነትን ለመረዳት የሚጥር ፖለቲካዊ መጣጥፍ ነው። ‘አዲሱ አራዳ’ ማነው? በዚህ ዘፈኑ በብዙዎቻችን ዕድሜ የትዝታ ማኅደር ውስጥ የሚገኙ ነገር ግን በአዲስ አበባ ልማት ሥም የፈረሱ እና እየተረሱ ያሉ ሰፈሮችን ሥም ያነሳሳል። ዘፈኑ በግጥሙም በዜማውም፣ የሐዘን እንጉርጉሮ ያለበት ነው። ምሳሌ እንውሰድ፦ “ጨርሰሽ ስትወጪ ከቡፌ ዳ’ላጋ፣ ጠብቂኝ እንዳልል፣ ቆመሽ መሐሙድ’ጋ፣ አገር ...

መጽሐፍ የሚወጣው፣ የተዋነይ ዘ ጎንጅ 5 መሥመር ቅኔ

ጎንጅ ቅኔ ያጠናበት ደብር ሥም ነው። ደብረ ጥበብ ጎንጅ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም። ተዋነይ የባለቅኔው ሥም ነው። (የግዕዝ ትርጉሙ "ዋናተኛ" ማለት ነው።) ሊቁ ተዋነይ የልኅቀቱን ያክል እምብዛም አይወራለትም፤ ነገር ግን በዘመኑ ወደር የሌለው ልኂቅ ስለመሆኑ ሥራው ይናገራል። የሕይወት ተፈራ "Mine to Win" የተሰኘ ድርሰት መቼቱን በዐፄ ዮሓንስ ንግሥና ዘመን፣ በጎጃም/ጎንደር የቅኔ መማሪያ ደብሮች ያደረገ ልብወለድ ነው። ልቦለዱ የቅኔ ትምህርት ስርዓትን ያስተዋውቀናል፤ በበኩሌ የቅኔ ትምህርትን እና የቅኔ ሊቃውንት ታላቅነት ቀድሞ ከነበረኝ ግንዛቤ የበለጠ እንዲሆን አድርጎኛል። በተለይ የተዋነይ ዘ ጎንጅ (በውኑ ዓለም የነበረ ባለቅኔ) ተከታይዋ አምስት መሥመር ቅኔ መጽሐፍ የሚወጣት እንደሆነች ልቦለዱ አሳሰበኝ። ወይም በአጭሩ ብዙ ምዕራባውያን ስንት መጽሐፍ የጻፉለት ፍልስፍናን በአምስት መሥመር ይዟል። የቅኔው ትርጓሜ የመጽሐፍ ቅዱስን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ፈጣሪ ኅልውና ይሞግታል። “የአምን ወይገኒ ኵሉ ዓለም በዘፈጠረ ለሊሁ ብዙኃን እንዘ ይገንዩ ይስግዱ ቅድሜሁ ለነጽሮ ዝኒ ነገር እሥራኤል ከመይፍርሑ ሙሴ ፈጠረ ፈጣሪሁ ወ ፈጣሪ ፈጠረ ኪያሁ።” (ተዋነይ ዘ ጎንጅ። ምንጭ፣ሕይወት ታደሰ ወደአማርኛ የተረጎመችው የሕይወት ተፈራ መጽሐፍ) ትርጉሙን በኋላ እመለስበታለሁ። ስለተዋነይ መጀመሪያ የሰማሁት የበውቀቱ መጽሐፍ ላይ ነበር። እሱም በጨረፍታ - “የሌሊት ዜማዎች” የሚለው ግጥሙ ውስጥ። በውቀቱ ተዋነይን በግጥሙ ግርጌ ማስታወሻው አስተዋውቆን ያልፋል፣ “ተዋነይ በቅኔ ቤት አፈ ታሪክ ሞትን በግዝት ለሰባት ዓመታት ያቆመ ጀግና ነው"። ከዚያ በኋላ፣ አዲስ አድማስ ላይ የወጣ አንድ ጽሑፍ ተዋነይ የተላከበትን ...