Skip to main content

የመፈረጅ ፍራቻ እና የመፈረጅ አደጋ


አንድነት ለፍትሕና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ባሳለፍነው እሁድ (ግንቦት 12፤ 2004) ‹‹የስነጥበብ ሚና በማሕበረሰብ ውስጥ›› የሚል የውይይት መድረክ በብሔራዊ ቴያትር አዳራሽ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ ውይይቱን የመሩት ፀሃፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ፣ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማሕበሩ አበረ አዳሙ፣ ቀራፂ በቀለ እና ሰአሊ እሸቱ ጥሩነህ ነበሩ፡፡

እነዚህ የበቁ ባለሙያዎች ጥበብ ለማሕበረሰቡ፣ ማሕበረሰቡም ለጥበብ ማበርከት ይችላሉ ያሏቸውን ጠቁመዋል፡፡ ውይይቱ የተሟሟቀው ግን ዝግጅቱ ከመጠናቀቁ አንድ ሰዓት በፊት ታዳሚዎች ጥያቄዎችን ማንሳት ከጀመሩ በኋላ ነው፡፡

በውይይቱ ውስጥ አከራካሪ የነበረው ነጥብ የኪነጥበብ ሰዎች ሐሳባቸውን ለመግለፅ የመፍራት ጉዳይ ነበር፡፡ እኔም ይህን ጽሁፍ እንድጽፍ መንስኤ የሆነኝ ይኸው የፍራቻ ጉዳይ ነው፡፡

ፀሃፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ በሙያቸው የተካኑ መሆናቸው አጠያያቂ አይደለም፡፡ ይሁንና በውይይቱ መክፈቻ ላይ የያዙትን ጽሁፍ ማቅረብ ከመጀመራቸው በፊት ግልፅ ማድረግ የሚፈልጉት ነገር እንዳለ ተናገሩ፡፡ ‹‹እኔ የማንም ወገንተኛ አለመሆኔን ግልፅ ማድረግ እፈልጋለሁ፤›› አሉ፡፡ በንግግራቸው መሃልም ኪነጥበብ የማሕበረሰብ ሃያሲ ነች ካሉ በኋላ ‹‹ፖለቲካ ውስጥ አታስገቡኝ እንጂ ፖለቲካም ሃያሲ አለው›› አሉ፡፡

አያልነህ ሙላቱ አርአያ ሊባሉ የሚችሉ የጥበብ ሰው ቢሆኑም በፅንሰ ሐሳብ ደረጃ ፖለቲካውን ጥበብ መተቸት የምትችልበትን መንገድ ለመናገር አልደፈሩም፡፡ እኔም ይህንን ዓይነቱን ፍራቻ - የአያልነህ ሙላቱ ፍራቻ - በሚል ርዕስ ልጽፈው ማሰብ ጀመርኩ፡፡ ርዕሱን ያስቀየሩኝ ምክንያቶች እኒህ ናቸው፤ (1) አያልነህ ሙላቱ ከአድማጮች ለተነሱ ጥያቄዎች ሲመልሱ ኪነጥበብ የአንድ ድርጅት ንብረት አትሆንም ማለቴ እንጂ ለእውነት ወግና ከመንግስት ጋርም ቢሆን ትጣላለች፤ ‹‹አለበለዚያ ግን ገደል ትግባ!›› ብለው በማስተባበላቸው፣ (2) ሰአሊ እሸቱ ጥሩነህ ‹‹እናንተ መስማት የምትፈልጉትን መስማት ስለምትፈልጉ እንጂ ገለልተኝነት ፍራቻም ጥላቻም አይደለም›› ብለው መናገራቸው ስላሳመነኝ እና (3) ግለሰብ ላይ ብቻ ማፍጠጡ ተገቢ ስላልሆነ ነው፡፡

ይሁን እንጂ የአያልነህ ሙላቱን ስጋት መተቸቴን አቆማለሁ ማለቴም አይደለም፡፡ እርሳቸው ምናልባት የጋበዛቸው ኢሕአዴግ ቢሆን ኖሮ ‹‹ለነገሩ የማንም ወገንተኛ አይደለሁም፤›› ይላሉ ብዬ አልጠብቅም፡፡ ምክንያቱም ጋባዡ ራሱ የሚፈራው አካል ነውና የፍራቻ መፈክሩ ቦታ የለውም፡፡

የአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቪዥን ከንቲባው በሊዝ ጉዳይ ጥቂት ሰዎችን ሲያነጋግሩ አንድ አስተያየት ሰጪ ወጣት የተናገረው - የአያልነህ ሙላቱን ፍራቻ ያስታውሰናል፡፡ ወጣቱ ንግግሩን የጀመረው እንዲህ ብሎ ነው፤ ‹‹ይሄ መቃወም አይለም፤ እኔ እንደውም የኢሕአዴግ ደጋፊ ነኝ፡፡ ልማት አለ፡፡ ግን ለምንድን ነው መንግስት…›› ጥያቄውን ጠየቀ፡፡ በሚያስታውቅ ሁኔታ ወጣቱ በኢሕአዴ ተማርሯል፡፡ ነገር ግን የተማረረበትን መናገር ወይም መቃወም ሕይወቱን የሚያስከፍለው ነገር እንደሆነ ተሰምቶታል፡፡ መቃወሙ ከእነእከሌ ጋር እንዳያስፈርጀው ሰግቷል… ስለዚህ የኢሕአዴግ ደጋፊ መባልን መረጠ፡፡

እርግጥ ነው ይህ ዓይነቱ ስጋት ተቃዋሚዎች ዘንድም እየተከሰተ እንደሆነ አስተውያለሁ፡፡ ተቃዋሚዎችን ለመተቸት መሞከርም ወደ ወዲያኛው ወገን የሚያስፈርጅ ወንጀል እየሆነ የላይኛውን ቤት ባሕል ታችቤቶች ሲርመጠመጡበት ማየት የማይገባ ድርጊት ነው፡፡

ወደ ውይይቱ ስንመለስ፤ አቶ አበረ በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጵያ ደራሲዎች ችግር የሚጽፉትን የሚያነብላቸው ሰዎች ችግር እንጂ ፍራቻ እንዳልሆነ ተከራክረዋል፡፡ እንዲያውም የደራሲዎቻችንን ጽሁፍ አንብቡ እና ፍራቻ ካለበት፣ ስለወቅታዊ ቀውሶች ካልጻፉ ታዘቡን ዓይነት ውርርድ ከታዳሚው ጋር ተወራርደዋል፡፡ ‹‹ደራሲው ተበድሮና ሕይወቱን ለአደጋ አጋልጦ የሚፅፈው መጽሃፍ በአንባቢ ድርቅ ተመትቷል፡፡››

ኢሕአዴግ ሕዝቡን እንዲፈራው የሚያደርገው ባልተጻፈ አዋጅ እንደሆነ አቶ አበረ የገባቸው አልመሰለኝም፡፡ ምክንያቱም የማይፈራ ሕዝብ ካለ ጠያቂም ሕዝብ ይኖራል፡፡ እስካሁን (ከብርሃንና ሰላም አዲስ የስምምነት ደንብ በፊት) ምንም ዓይነት የተጻፈ የሳንሱር ደንብ አልነበረም፡፡ ሆኖም የተዘዋዋሪ ዛቻ፣ ማስፈራሪያና ሽንቆጣዎች አሉ፡፡ ይህንን መረዳት ያልቻሉት (ያልፈለጉት) የደራሲያን ማሕበር አባል (በርግጥ ውይይቱ ላይ የተገኙት ማሕበሩን ወክለው እንዳልሆነ መግቢያቸው ላይ ገልፀዋል፤) ከታዳሚው ጋር በቅድመ ምርመራ ‹አለ!-የለም!› እሰጥ አገባ ውስጥ ገብተው ነበር፡፡

ቀራፂ በቀለ ንግግሩን ከመጀመሩ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአርቲስቶች ጋር ሲወያዩ መገኘቱን ገልፆ ‹‹እዚያ ልሄድ እንደሆነ የሰሙ ሰዎች ‹እሱ ነገር እኮ አደጋ አለው› ብለውኝ ነበር፡፡ አሁንም እዚህ ልመጣ እንደሆነ ሲሰሙ ‹እሱ ነገር እኮ አደጋ አለው› አሉኝ፤›› ካለ በኋላ ‹‹የት ነው ታዲያ አደጋ የሌለው?›› የሚል ጥያቄ አንስቶ ነበር፡፡ እኔም ይህንን ጽሁፍ መደምደም የምፈልገው በተመሳሳይ ጥያቄ ነው - የት ነው አደጋ የሌለው?

Comments

  1. ለምን ሀሳብህን አልጨረከውም?የመፈረጅ ፍራቻ እና የመፈረጅ አደጋ ነው?

    ReplyDelete

Post a Comment

Popular posts from this blog

The "Corridor Development" is a Façade of the Prosperity Party

Befekadu Hailu I have seen a news report claiming that 40% of central Addis Ababa will be demolished for the corridor development; I am not able to confirm the validity of the news but it sounds real to me given the size of massive operations in the demolition of old neighborhoods and construction of bike lanes, green areas, and glittering street lights. I like to see some beauty added to my city but cannot help mourning the slow death of it too. Addis Ababa was already in a huge crisis of housing and the demolition of houses is exacerbating it. Apparently, Prime Minister Abiy Ahmed is eager to showcase his vision of prosperity by demonstrating how fast his administration can do magic by beautifying the front sides of the streets with lights, new pavements, and painted fences ("to fake it until he makes it" in my friend's words). Therefore, he and his party do not care about the miserable human stories behind the scenes and they will harass you if you tell it (Azeb Woku...

መጽሐፍ የሚወጣው፣ የተዋነይ ዘ ጎንጅ 5 መሥመር ቅኔ

ጎንጅ ቅኔ ያጠናበት ደብር ሥም ነው። ደብረ ጥበብ ጎንጅ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም። ተዋነይ የባለቅኔው ሥም ነው። (የግዕዝ ትርጉሙ "ዋናተኛ" ማለት ነው።) ሊቁ ተዋነይ የልኅቀቱን ያክል እምብዛም አይወራለትም፤ ነገር ግን በዘመኑ ወደር የሌለው ልኂቅ ስለመሆኑ ሥራው ይናገራል። የሕይወት ተፈራ "Mine to Win" የተሰኘ ድርሰት መቼቱን በዐፄ ዮሓንስ ንግሥና ዘመን፣ በጎጃም/ጎንደር የቅኔ መማሪያ ደብሮች ያደረገ ልብወለድ ነው። ልቦለዱ የቅኔ ትምህርት ስርዓትን ያስተዋውቀናል፤ በበኩሌ የቅኔ ትምህርትን እና የቅኔ ሊቃውንት ታላቅነት ቀድሞ ከነበረኝ ግንዛቤ የበለጠ እንዲሆን አድርጎኛል። በተለይ የተዋነይ ዘ ጎንጅ (በውኑ ዓለም የነበረ ባለቅኔ) ተከታይዋ አምስት መሥመር ቅኔ መጽሐፍ የሚወጣት እንደሆነች ልቦለዱ አሳሰበኝ። ወይም በአጭሩ ብዙ ምዕራባውያን ስንት መጽሐፍ የጻፉለት ፍልስፍናን በአምስት መሥመር ይዟል። የቅኔው ትርጓሜ የመጽሐፍ ቅዱስን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ፈጣሪ ኅልውና ይሞግታል። “የአምን ወይገኒ ኵሉ ዓለም በዘፈጠረ ለሊሁ ብዙኃን እንዘ ይገንዩ ይስግዱ ቅድሜሁ ለነጽሮ ዝኒ ነገር እሥራኤል ከመይፍርሑ ሙሴ ፈጠረ ፈጣሪሁ ወ ፈጣሪ ፈጠረ ኪያሁ።” (ተዋነይ ዘ ጎንጅ። ምንጭ፣ሕይወት ታደሰ ወደአማርኛ የተረጎመችው የሕይወት ተፈራ መጽሐፍ) ትርጉሙን በኋላ እመለስበታለሁ። ስለተዋነይ መጀመሪያ የሰማሁት የበውቀቱ መጽሐፍ ላይ ነበር። እሱም በጨረፍታ - “የሌሊት ዜማዎች” የሚለው ግጥሙ ውስጥ። በውቀቱ ተዋነይን በግጥሙ ግርጌ ማስታወሻው አስተዋውቆን ያልፋል፣ “ተዋነይ በቅኔ ቤት አፈ ታሪክ ሞትን በግዝት ለሰባት ዓመታት ያቆመ ጀግና ነው"። ከዚያ በኋላ፣ አዲስ አድማስ ላይ የወጣ አንድ ጽሑፍ ተዋነይ የተላከበትን ...

የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ

በፍቃዱ ዘ . ኃይሉ “የአዲስ አበባ ብሔርተኝነት” ቢኖር ኖሮ መሪው ልጅ ሚካኤል ይሆን ነበር። አሁን አሁን እሱ ስለ አዲስ አበባ የዘፈናቸውን ዘፈኖች ቁጥር ራሱ በትክክል መቁጠር ይቸግረኛል። ለአዲስ አበባ ከተዘፈኑ ዘፈኖቹ ውጪም በየዘፈኑ ውስጥ የሚጨማምራቸው መልዕክቶች በራሳቸው መወድሰ አዲስ አበባ ናቸው። ለምሳሌ፣ በቅርቡ በለቀቀው ‘አዲስ አራዳ’ በተሰኘው አልበሙ ውስጥ ‘የድሬ ልጅ’ የሚል ዘፈን አለው። ዘፈኑ የተዘጋጀው ያው የአዲስ አበባ እህት ተደርጋ የምትቆጠረውን ድሬ ዳዋን ለማወደስ ነበር። ልጅ ሚካኤል ግን የአዲስ አበባ ፍቅሩ ያመልጠውና የሚከተለውን ያቀነቅናል፦ “መጣልሽ በሏት፣ ድሬ ድረስ፣  ከአዱ ገነት፣ ከሸገር፣ ከአዲስ ደረሰ፣... የሸገር ልጅ አራዳ ነው፣ ሰው አክባሪ፣ ሰው ወዳዱ፣ ቀላጅና ተረበኛ፣ ፍቅር ይዞ የሚተኛ፣ ‘አለው’ የለ፣ ‘የለው’ የለ፣ ከሁሉ ጋ፣ ግባ ጀባ...፤” ፤ ልጅ ሚካኤል በዚህ አልበሙ ብቻ አዲስ አበባን የሚያውድሰባቸው ሌሎችም ዘፈኖች አሉ፤ ‘ አዲስ አራዳ ’ የሚለው የአልበሙ መጠሪያ እና ‘ሸገር’ የሚሉት ዘፈኖቹ ዋነኞቹ ናቸው። ታዲያ እንዲህ በአዲስ አበባ ፍቅር የሚቃጠለው ልጅ ሚካኤል "ሊነግረን የሚፈልገው ምንድን ነው?" የሚለው ጥያቄ ደጋግሞ ይመጣብኛል። ይህ የልጅ ሚካኤል አዲስ አበባ ምንነትን ለመረዳት የሚጥር ፖለቲካዊ መጣጥፍ ነው። ‘አዲሱ አራዳ’ ማነው? በዚህ ዘፈኑ በብዙዎቻችን ዕድሜ የትዝታ ማኅደር ውስጥ የሚገኙ ነገር ግን በአዲስ አበባ ልማት ሥም የፈረሱ እና እየተረሱ ያሉ ሰፈሮችን ሥም ያነሳሳል። ዘፈኑ በግጥሙም በዜማውም፣ የሐዘን እንጉርጉሮ ያለበት ነው። ምሳሌ እንውሰድ፦ “ጨርሰሽ ስትወጪ ከቡፌ ዳ’ላጋ፣ ጠብቂኝ እንዳልል፣ ቆመሽ መሐሙድ’ጋ፣ አገር ...