Friday, August 25, 2017

መጽሐፍ የሚወጣው፣ የተዋነይ ዘ ጎንጅ 5 መሥመር ቅኔ

ጎንጅ ቅኔ ያጠናበት ደብር ሥም ነው። ደብረ ጥበብ ጎንጅ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም። ተዋነይ የባለቅኔው ሥም ነው። (የግዕዝ ትርጉሙ "ዋናተኛ" ማለት ነው።) ሊቁ ተዋነይ የልኅቀቱን ያክል እምብዛም አይወራለትም፤ ነገር ግን በዘመኑ ወደር የሌለው ልኂቅ ስለመሆኑ ሥራው ይናገራል። የሕይወት ተፈራ "Mine to Win" የተሰኘ ድርሰት መቼቱን በዐፄ ዮሓንስ ንግሥና ዘመን፣ በጎጃም/ጎንደር የቅኔ መማሪያ ደብሮች ያደረገ ልብወለድ ነው። ልቦለዱ የቅኔ ትምህርት ስርዓትን ያስተዋውቀናል፤ በበኩሌ የቅኔ ትምህርትን እና የቅኔ ሊቃውንት ታላቅነት ቀድሞ ከነበረኝ ግንዛቤ የበለጠ እንዲሆን አድርጎኛል። በተለይ የተዋነይ ዘ ጎንጅ (በውኑ ዓለም የነበረ ባለቅኔ) ተከታይዋ አምስት መሥመር ቅኔ መጽሐፍ የሚወጣት እንደሆነች ልቦለዱ አሳሰበኝ። ወይም በአጭሩ ብዙ ምዕራባውያን ስንት መጽሐፍ የጻፉለት ፍልስፍናን በአምስት መሥመር ይዟል። የቅኔው ትርጓሜ የመጽሐፍ ቅዱስን እና የመጽሐፍ ቅዱሱን ፈጣሪ ኅልውና ይሞግታል።
“የአምን ወይገኒ
ኵሉ ዓለም በዘፈጠረ ለሊሁ
ብዙኃን እንዘ ይገንዩ ይስግዱ ቅድሜሁ
ለነጽሮ ዝኒ ነገር እሥራኤል ከመይፍርሑ
ሙሴ ፈጠረ ፈጣሪሁ
ወ ፈጣሪ ፈጠረ ኪያሁ።”
(ተዋነይ ዘ ጎንጅ። ምንጭ፣ሕይወት ታደሰ ወደአማርኛ የተረጎመችው የሕይወት ተፈራ መጽሐፍ)
ትርጉሙን በኋላ እመለስበታለሁ። ስለተዋነይ መጀመሪያ የሰማሁት የበውቀቱ መጽሐፍ ላይ ነበር። እሱም በጨረፍታ - “የሌሊት ዜማዎች” የሚለው ግጥሙ ውስጥ። በውቀቱ ተዋነይን በግጥሙ ግርጌ ማስታወሻው አስተዋውቆን ያልፋል፣ “ተዋነይ በቅኔ ቤት አፈ ታሪክ ሞትን በግዝት ለሰባት ዓመታት ያቆመ ጀግና ነው"። ከዚያ በኋላ፣ አዲስ አድማስ ላይ የወጣ አንድ ጽሑፍ ተዋነይ የተላከበትን መልአከ ሞት ደጃፉ ላይ በምትሐት 7 ዓመት አቁሞት በማርያም አማላጅነት ነው ገብቶ ነፍሱን እንዲወስድ የፈቀደለት የሚል አፈ ታሪክ አለ ይለናል። በሌላ በኩል ዕፀ ሕይወት አግኝቶ ነገር ግን በአጠቃቀም ስህተት ግማሽ ሰውነቱ ሞቶ ግማሹ ሲኖር፣ ፈጣሪውን ለምኖ ነው ሙሉ ለሙሉ የወሰደው የሚል ሌላ አፈ ታሪክም አለ። የኋላ ኋላ ቴዲ አፍሮም አንድ ዘፈኑ ላይ ሥሙን ጠቅሶት ያልፋል።

በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን የተጻፈው የአለቃ ተክለየሱስ ዋቅጅራ "የኢትዮጵያ ታሪክ" (በሚል በሥርግው ገላው የተሰናዳው መጽሐፍ) ላይም ሥሙን እንዲሁ በአጭሩ ተጠቅሶ አገኘሁት። እንዲህ ይላል፣ “ዐፄ በካፋ በዘመኑ ከክፉ ሥራ በቀር ፩ ቀን በጎነት ሥራ አልሠራም። ያን ግዜ ተዋነይ የሚባል የጎንጅ ደብተራ ጠንቋይ ነበረው። ሙያው ከርሱ ጋራ ነበረ። በካፋም ፱ ዓመት ነግሦ [በ1723] በክፉ ሞት ሞተ።" ተዋነይን የቀድሞ ታሪክ የሚያስታውሰው እንዲህ ነው ማለት ነው? በርግጥም ይህን መሰል ቅኔ እየጻፈ መልካም ሥም ቢኖረው ነበር የሚገርመኝ። የፍቅር እስከመቃብሩ "ጉዱ ካሣ" የእውነተኛ ባለታሪክ ቢሆን ኖሮ (የእውነተኛ ሰው መነሻ ተደርጎ ነው የተጻፈው የሚሉ አሉ) በታሪክ የሚታወሰው እንደቀውስ ነበር። ከዚህ አንፃር የተዋነይ ዘ ጎንጅ እንደ ጠንቋይ መታወስ ላይገርም ይችላል። በነገራችን ላይ፣ ተዋነይ የዐፄ በካፋ አማካሪ ከመሆኑ በፊት የንጉሡን ምግብ ዕፀ መሰውር ለብሶ (እንዳይታይ ሆኖ) ይበላባቸው ነበር የሚባል አፈ ታሪክም አለ።

Sunday, August 20, 2017

የተዋሐደን ፆተኝነት

ይህ ጽሑፍ ስለ ፍትሕ ነው። አንባቢዎቼን በትህትና አስቀድሜ የምጠይቀው ነገር ቢኖር የፆታ፣ የሃይማኖት፣ የባሕል፣ የፖለቲካ ወገንተኝነት መነፅሮቻችሁን አውልቃችሁ በፍትሕ መነፅራችሁ እንድታነቡኝ ነው።

የተዋሐደን ፆተኝነት ስንል ምን ማለታችን ነው? ምንጮቹ ምን ምን ናቸው? ውስጣችን ያለው ይህ ፆተኝነት ምን ያህል ችግር ይፈጥራል? የተዋሐደንን ፆተኝነትን እንዴት እንቅረፈው?

መግባቢያ ስለፆተኝነት

ፆተኝነት ማለት በአጭሩ ‘ፆታዊ መድልዖ’ ማለት ነው። በዓለማችን እጅግ የተንሰራፋው ለወንዶች የሚያደላው ወይም አባታዊው ስርዓተ ማኅበር ነው። (እርግጥ እጅግ ጥቂት ሆኑ እንጂ እናታዊ ስርዓተ ማኅበሮችም አሉ፡፡ ለምሳሌ ሕንድ አገር ሜጋላያ ስቴት ውስጥ የሚገኙት ጎሳዎች ሀብት የሚተላለፈው ከእናት ወደሴት ልጅ ነው፡፡ በዚህ ስርዓተ ማኅበር የትምህርትና መሰል ዕድሎች ከወንዶች ይልቅ ለሴቶች ይመቻቻሉ፡፡ ይህን ምሳሌ በዓለም ከተንሰራፋው አባታዊው ስርዓት አንፃር ከቁብ ሳልቆጥረው ላልፍ እችል ነበር። ነገር ግን የእነዚህ ጎሳዎች እናታዊ ስርዓት ከትውልድ ትውልድ እየተላለፈ እዚህ መድረሱ አባታዊው ስርዓትም ሆነ እናታዊዋ በማኅበራዊ ብሒል የሚገኙ እንጂ ተፈጥሮ ያከፋፈለችን ሚና አለመሆኑን ስለሚያሳይ ነው።) የአገራችን ስርዓተ ማኅበር ከጥግ እስከ ጥግ አባታዊ ነው። ይህንን ስርዓተ ማኅበር ለመቀልበስ እና ፍትሐዊ ስርዓተ ማኅበር ለመመሥረት የሚደረጉ የተደራጁም ይሁን ያልተደራጁ ንቅናቄዎችን ሴታዊነት እንላቸዋለን። (‘እንስታዊነት’ የእንግሊዝኛውን ‘Feminism’ በቀጥታ የሚተካ ቢሆንም፣ አማርኛችን ስርዓተ ፆታ (gender) ያልተጫነው ‘ሴት’ የሚል ሥነ ተፈጥሯዊ (biological) ልዩነቱን ብቻ የሚገልጽ ቃል ስላለው ‘ሴታዊነት’ የሚለውን መርጫለሁ። በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ሴታዊነት ማለት “ፆታዊነትን መቃወም እንዲሁም ሴቶች ከወንዶች ዕኩል መብትና ዕኩል ዕድል እንዲያገኙ መታገል” የሚል ብያኔ ይኖረዋል።)

የተዋሐደን ፆተኝነት…

ስልካችንን የኋላ ኪሳችን አስቀምጠነው ብንሰረቅ ማነው ተወቃሹ? እንዝህላልነታችን ወይስ ሌብነቱ? በመርሕ ደረጃ ሌብነት በማንኛውም ሁኔታ ነውር ነው። ይህ ምሳሌ “ነውር ማለት ሁላችንም በራሳችን ላይ እንዲደረግብን የማንፈልገው ነገር ነው” የሚል ብያኔ እንድናገኝ ይረዳናል። ስለዚህ "ቤታቸውን ከፍተው ሰውን ሌባ ያሰኛሉ" የሚለው አባባል የሌብነትን ነውር አቃልሎ ያሳያል እንጂ አያስቀረውም። ልክ እንደዚህ ሁሉ የሴት ልጅ መደፈርን ነውርነትም እንዲህ በሰበብ ሊያስተባብሉ የሚሞክሩ ብዙ ናቸው። ነገር ግን በአገራችን ኢትዮጵያም ሆነ በአህጉራችን አፍሪካ ለሴቷ መደፈር እራሷኑ ተጠያቂ ማድረግ የተዋሐደን ፆተኝነት ማሳያ ነው። ዩጋንዳ በየካቲት 2006 አጭር ቀሚስ የሚከለክል ሕግ አውጥታ ነበር። ከዚያ ቀደም ብለው የወጣቶች ሚኒስትሩ "ጨዋነት የጎደለው አለባበስ የለበሱ ሴቶች ሲደፈሩ ከራሳቸው በቀር ማንም ተጠያቂ መሆን የለበትም" ብለው ተናግረው ነበር። ተመሳሳይ ንግግሮች በሁሉም የአፍሪካ አካባቢዎች የተለመዱ ናቸው። በአገራችንም፣ አንዲት ሴት በወንድ ጥቃት ደረሰባት የሚለው ዜና ሲሰማ ገና፥ “ምን አድርጋው?” የሚለው ምላሽ ይከተላል። ጥያቄው፣ ሴት ልጅ ምክንያታዊ ጥቃት ይገባታል ከሚል የተዋሐደን አስተሳሰብ የሚመነጭ ነው። ለጥቃቱ ከማዘናችን በፊት ቀድሞ የሚመጣብን ጥያቄ “ምን አድርጋው?” የሚለው ከሆነ የተዋሐደን ፆተኝነት ሥር የሰደደ ነው ማለት ነው፡፡

በቅርቡ ይፋ የሆነ (ነገር ግን ውጤቱ ከቀደምት ጥናቶች ጋር የሚመሳሰል) ጥናት እንደሚያስረዳን፣ በኢትዮጵያ 63% የሚሆኑት ሴቶች "ባል ሚስቱን ወጥ ካሳረረች፣ ከጨቀጨቀችው፣ ሳትነግረው ዙረት ከሔደች ወይም መሰል ጥፋት ካጠፋች… ቢመታት ምንም አይደል" ብለው ያምናሉ። ባንፃሩ አሳማኝ ምክንያት ካለ ሴት ልጅ መመታት አለባት ብለው የሚያምኑት 28% የሚሆኑት ወንዶች ብቻ ናቸው። ለምን ሴቶች የገዛ ራሳቸውን ጥቃት ተገቢ ነው አሉ። ለምን ከሴቶቹ ቁጥር ያነሱ ወንዶች መምታቱ ተገቢነት ላይ ተስማሙ? መልሱ ቀላል ነው። የተዋሐደን ፆተኝነት የገዛ ጥቃታችንን በራሱ ተቀባይነት እንዳለው ነገር እንድንቀበለው ያታልለናል። ወንዶች ከሴቶች የተሻለ፣ የትምህርትና የመረጃ ዕድል ስላላቸው የሴት ልጅ ጥቃት በማንኛውም ሁኔታ ተገቢ አለመሆኑን መረዳታቸውንም ውጤቱ ይጠቁመናል። በዚህም ፆተኝነት በትምህርት የሚቀረፍ ነገር መሆኑን በቀላሉ ማየት ይቻላል።

የተዋሐደን ፆተኝነት ከማኅበረሰቡ የተማርነው፣ የኑሮ ዘዬያችን የተገነባበት እና በየዕለቱ የምንከተለው ነገር ግን ጨርሶ የማናስተውለው ከመሆኑ የተነሳ "ትክክለኛ" የሚመስለን ነገር ነው። ሆስፒታል ሔደን ነጭ ጋዋን የለበሰች ሴት ስትገጥመን [ነርስ እንደሆነች እርግጠኛ በመሆን] "ሲስተር" የምንላት፣ ነጭ ጋዋን የለበሰ ሲገጥመን "ዶክተር" የምንለው የተዋሐደን ፆተኝነት አስገድዶን ነው። አንድ ቀን መሳሳታችንን ብናውቅ እንኳን ደግመን መሳሳታችንን እንቀጥላለን፡፡ በተመሳሳይ የቢሮው ሥራ አስኪያጅ እንዲሁ ስናስበው ወንድ አድርገን ነው፤ ጸሐፊዋን ደግሞ ሴት። "ማናጀሩ የታል?" ስንል ወንድ እንደሆነ አንጠራጠርም። የኩሽና ሥራ በጥቅሉ የሴት ነው ብለን ነው የምናስበው፡፡ ምግብ አብሳይ ስንባል በምናባችን ሴት እንስላለን፤ የትልቅ ሆቴል ሼፍ ስናስብ ግን ወንድ ነው በምናባችን የሚመጣው፡፡ ምክንያቱም ምግብ አብሳይነትም  ቢሆን ደረጃው እያደገ ሲመጣ ለሴት እንደማይገባ የተዋሐደን ፆተኝነት ሹክ ይለናል፡፡

Wednesday, June 28, 2017

"ዘውጌኝነት" እና "ዘውግ-ዘለልነት"…?

የዘውግ ብሔርተኝነትም ይሁን ኢትዮጵያዊ ኅብረብሔርተኝነት አተያዮች በዘውግ ላይ የተመሠረቱ ናቸው። ሁለቱም ዜጎችን የሚመለከቱት የዘውግ ምንዝር (ethnic subjects) አድርገው ነው። ስለዚህ ይለያያሉ ማለት አይቻልም።
ለብዙዎቹ ችግሮቻችን ፍቱን መድኃኒት አድርጌ የምወስደው፣ ጉዳዩን በዘመን ቁመት እና በዓለም ሕዝቦች ታሪክ አግድም መመልከት ነው። ዓለም በበቂ ሁኔታ የምንማርባቸው ስኬቶች እና ውድቀቶች አሏት። ዘውጌኝነት፣ ብሔርተኝነት እና ዜግነት የመሳሰሉትም የብቻችን ጉዳዮች አይደሉም። ዓለም በየፈርጁ የዳከረችበት እና እየዳከረችበት ያለ ችግር ነው። ስለዚህ ጥያቄውን በቅጡ ለማበጃጀትም ይሁን፣ አዋጭ መልስ ለመፈለግ ከሰው ልጆች እንደአንድ የሚያደርገንን ታሪክ የምናውቀውን ያክል ማሰስ ያስፈልጋል። ይህን ከጠቆምኩ በኋላ ወደ የበኩሌን ለመሞከር ወደ አጀንዳዬ እዘልቃለሁ።

የዘውግ ብሔርተኝነት ምንድን ነው?

የዘውግ ብሔርተኝነት (ethnonationalism) የአንድ ዘውግ (ethnic) ቡድን ነጻ አገር እንዲመሠርት ወይም ከመገንጠል ወዲህ ያለውን የራሱን ዕድል በራሱ እንዲወስን ለማስቻል የሚደረግ ፖለቲካዊ ንቅናቄ ነው።

የዘውግ ማንነት በኢትዮጵያ ልማዳዊ አሠራር በወላጆች ማንነት ነው የሚወሰነው። እናትና አባታቸው ከተለያዩ ዘውጎች የተወለዱ ዜጎች በተለምዶ የአባታቸውን የዘውግ ሐረግ ነው የሚወርሱት። ዜጎች በአንድ ክልል ተወልደው፣ የአካባቢውን ቋንቋ፣ ባሕልና ወግ አውቀው ቢያድጉም ከአካባቢው ዘውግ የተለየ ዘውግ ካላቸው ወላጆች ከተወለዱ የአካባቢው ዘውግ አላቸው አይባልም። ማለትም፣ ለምሳሌ በኦሮሚያ ከአማራ ልጆች ተወልደው ያደጉ ልጆች በዘውግ ብሔርተኞች እንደኦሮሞ አይቆጠሩም። በሕግ የመምረጥ እና መመረጥ መብት ቢኖራቸውም በልማድ ተቀባይነት የማግኘት ዕድላቸው ግን አነስተኛ ነው። ነገሩን ይብስ ውስብስብ የሚያደርገው ደግሞ በሌሎች ማኅበረሰቦች መሐል የሚያድጉ ልጆች ከአደጉበት ማኅበረሰብ ይልቅ ዘውጋቸውን ከወላጆቻቸው በደም ለመውረስ የመፈለጋቸው ልምድ ነው፡፡

የዘውግ ብሔርተኝነት ንቅናቄዎች ከዘር (race) ንቅናቄዎች ጋር በትይዩ ሊታዩ ይችላሉ። ምንም እንኳን በኢትዮጵያ ያሉ ዘውጎች በፊት ቅርፅና የቆዳ ቀለም ሊገለጽ የሚችል ልዩነት ባይኖራቸውም (የዘር ልዩነት ባይኖርም)፣ የሚያነሷቸው ጥያቄዎች ግን ተቀራራቢነት አላቸው። ሁለቱም "በማንነታችን ምክንያት የመብት እና ዕድል አድልዎ ይደረግብናል" ይላሉ። የሚገጥሟቸውም ተግዳሮቶችም ተቀራራቢነት አላቸው፤ ለምሳሌ ያክል 'Black Lives Matter' (የጥቁር ነፍስም ዋጋ አለው) በሚለው የጥቁሮች ንቅናቄ ላይ 'All Lives Matter' (የሁሉም ሰው ነፍስ ዋጋ አለው) ነው መባል ያለበት እንደሚሉት ሁሉ፣ በኛም አገር ለምሳሌ 'Because I am Oromo' (ኦሮሞ ስለሆንኩ) እንዲህ ደረሰብኝ በሚለው ፈንታ 'Because I am Ethiopian' (ኢትዮጵያዊ በመሆኔ) ነው መባል ያለበት የሚል ትችት ይቀርብባቸዋል።

Wednesday, June 14, 2017

የቂሊንጦ እሳት፣ ወላፈኑን የቀመሱት እና በሰበቡ የተከሰሱት

(ፎቶ፤ ደህናሁን ቤዛ)

ይህ ታሪክ በደርግ ዘመን የተፈፀመ አይደለም። በኢሕአዴግ ዘመን የተፈፀመ የበደል ታሪክ ነው።… የምነግራችሁ ታሪክ በአስቸኳይ ግዜ አዋጁ "ለተሀድሶ ሥልጠና" ወደ አዋሽ ሰባት የፖሊስ ካምፕ የተጓዝኩትን ያስታውሰኛል። "ከሥልጠናው" ሰነዶች በአንዱ ላይ፣ በደርግ ግዜ ይፈፀሙ የነበሩትን የሰብኣዊ መብት ጥሰቶች "ሰምቶ ማመን የማይችል ትውልድ ተፈጥሯል" ይላል። አባባሉ የኢሕአዴግን በትር እየቀመሱ ለኖሩ በጣም ያስቆጣል። ቀጥሎ የማወራላችሁ ታሪክ የደናሁን ቤዛ ታሪክ ነው። ደናሁን ደርግን የማያውቅ ወጣት ነው። ኢሕአዴግን ብቻ እያየ አድጎ ኢፍትሐዊነቱን መቀበል ያቃተው የመርሃዊ፣ ጎጃም ልጅ ነው።

ደናሁን በእነዘመኑ ካሴ በእውቄ መዝገብ፣ በፀረ ሽብርተኝነቱ አዋጅ ከተከሰሱት 9 ሰዎች 3ኛው ነው። ባለፈው ሳምንት የእስር ግዜውን ጨርሶ በፍቺ ተሰናብቷል። ከአባሪዎቹ መካከል አሸናፊ አካሉ በቂሊንጦ እሳት አነሳሽነት ክስ ተመሥርቶበታል። አንሙት የኔዋስ የተባለው ደግሞ ይህንን ለዐቃቤ ሕግ ከሚመሰክሩት መካከል ሥሙ ተጠቅሷል።
ቁጥቡን ደናሁንን የተፈታ'ለት አግኝቼው ነበር። ብዙ ነገር ተጨዋወትን። ሸዋሮቢት ወስደው በካቴና አስረው ሰቅለው ሲገርፉት ካቴናው የእጁ ወርች ላይ፣ እግሩ የታሰረበት ገመድ ደግሞ ከቁርጭምጭሚቱ በላይ ያወጡትን ሰምበር እያሳየኝ ነበር። ይህ ድርጊት ከተፈፀመበት 9 ወር ገደማ ቢሆንም ጠባሳው እስካሁን ከሰውነቱ አልከሰመም። ነገር ግን በዚህ ሁሉ ስቃይ ውስጥ ምንም ያልሠራውን ወንጀል ባለማመኑ ይመስላል፣ ወይም ደግሞ ምናልባት ሌሎች እስረኞች ሥሙን ስላልጠቀሱ ከጓደኞቹ ቀላቅለው አልከሰሱትም፤ አባብለው ምስክር እንዲሆንባቸውም ማድረግ አልቻሉም።

የደናሁን ጀብዱ
የደናሁን ጥንካሬ የመጣው፣ ምናልባትም ካለፈው ልምዱ ይሆናል። ደናሁን እንዳጫወተኝ በትውልድ አካባቢው ያለውን ኢፍትሐዊነት ከጓደኞቹ ጋር መቃወም የጀመረ ሰሞን ከመኢአድ ሰዎች ጋር እየተገናኘ ማውራት ጀምሮ ነበር። አንድ ቀን ግን ድንገት በደኅንነት ሠራተኞች በቁጥጥር ሥር ዋለ። ወዲያው አንድ ትዕዛዝ ተሰጠው። "በል ጓደኞችህን ደውልና ቅጠራቸው።" ደናሁን ደወለ፤ "ሃሎ እከሌ፣ እኔ ተይዣለሁ እራሳችሁን አድኑ።" ከዚያ በኋላ አንድ ቀን ሲደበደብ አደረ። እስከ ማግስቱ ጓደኞቹ ስልኩ ላይ መደወል ተያይዘዋል። ደኅንነቶቹ ሁለተኛ ትዕዛዝ ሰጡት፣ "በል አንሳውና አምልጫለሁ፣ የት ላግኛችሁ?" በላቸው አሉት። 'እንግዲህ ከዚህ በላይ አልችልም፤ ከገባቸው ይግባቸው' ብሎ እንደታዘዘው አደረገ። "እዛ የምናውቀው ቤት ና" አሉት። ሒድ ምራ ተባለ። ደናሁን ከኋል ከኋላው ታጅቦ እየመራ እያለ፣ ጓደኞቹን አሳልፎ መስጠት አላስቻለውም። ድንገት ፈትለክ ብሎ ሮጠ። ጓደኞቹንም ጠርቶ አብረው አመለጡ። በግዜው የታያቸው አማራጭ መሸፈት ብቻ ነበር። እዚያው የተገኘው ጫካ ውስጥ፣ የተገኘውን መሣሪያ ይዘው ሸፈቱ። የደናሁን እናት ለመያዣነት አንድ ቀን ታሰሩ። ደናሁን አሁንም ሳይማረክ ሲቀር ተፈቱ፤ ደናሁን ሌሊት ሔዶ ዓይናቸውን አየ። ከዚያ በኋላ በሌላ ቀን በተቀነባበረ ዘመቻ ከነጓደኞቹ በቁጥጥር ሥር ዋለ።

Wednesday, May 24, 2017

Captivity in the Name of ‘Defamation’!

(The origional version of this story is published in Amharic on Ethiopian Human Rights Project website.)

The past year ended with two notable controversies between the press and Ethiopian Orthodox Church (EOC). The first one was concluded with a rare rule from an Ethiopian court that served justice to the press. The second one, undeservedly awarded the EOC a victory against a journalist who reported what happened, as it happened.

The first was 100% critical comment against the patriarch of EOC who, according to the writer Daniel Kibret, is negligent when corruption is spread in the church. The latter is a news report (pictured below) that referred to a letter written by community and priests of St. Mary’s Church, which is also a seat for the EOC patriarch.

The critical opinion written by the renown Daniel Kibret was published on Sendek newspaper; while, the news report was published on Ethio-mihidar newspaper, known for giving space to dissent voices of Ethiopia. Editor-in-chief of Sendek, Frew Abebe, acquitted on January 25, 2017 from the ‘defamation’ charge by the patriarch of EOC. However, editor-in-chief of Ethio-midihdar, Getache Worku, found ‘guilty’ of another but related ‘defamation’ charges against EOC’s St. Mary church administration and sentenced to 1 year of imprisonment and fine of ETB 1,500 on 15 November 2016; furthermore, his newspaper is also subjected to ETB 10,000 fine for running the news. In the case of Sendek newspaper, it was only the editor-in-chief against whom the charge was pressed; in the case of Ethio-mihidar newspaper, on the other hand, the publishing firm itself is accused of ‘running the defamation story’ in addition to the editor-in-chief.

Monday, May 1, 2017

የረቂቅ አዋጁ ዓላማ ምንድን ነው?

“የኦሮሚያ ክልል በፊንፊኔ/አዲስ አበባ ላይ ያለውን ሕገ መንግሥታዊ ልዩ ጥቅምን አስመልክቶ የተዘጋጀ የጥናት ሰነድ” የሚል ባለ 46 ገጽ ሐተታ እና በዚሁ መሠረት የተዘጋጀ ረቂቅ አዋጅ በኢንተርኔት ተለቀዋል፡፡ አዘጋጁ ኦሕዴድ የሚመራው የኦሮሚያ መንግሥት ነው ተብሎ ቢገመትም በኦፊሴላዊ መንገድ ስላልተለቀቀ እርግጠኛ መሆን አልተቻለም፡፡ እስካሁን ድረስ ማስተባበል የነበረበት መንግሥታዊ አካል ስላላስተባበለ እና ከውዥንብሩ መውጣት ስላልቻልን እንዲሁም ረቂቁ ትችት ስለሚያስፈልገው፣ ረቂቅ አዋጁ ላይ የሰፈሩት አንዳንድ ጉዳዮች አሳሳቢነት ላይ ያለኝን አስተያየት አሰፍራለሁ፡፡

የኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 49/5 እንዲህ ይነበባል፣ “የኦሮሚያ ክልል፤ የአገልግሎት አቅርቦት ወይም የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምንና የመሳሰሉትን ጉዳዮች በተመለከተ እንዲሁም አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሐል የሚገኝ በመሆኑ [የተነሳ] ሁለቱን የሚያስተሳስሩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ያለው ልዩ ጥቅም ይጠበቅለታል፡፡ ዝርዝሩ በሕግ ይወሰናል፡፡”

የረቂቅ አዋጁም በመግቢያው ላይ ዓላማውን “ዝርዝሩ በሕግ ይወሰናል” በተባለው መሠረት እንደሆነ ይናገራል፤ “የጥናት ሰነዱም” የተዘጋጀው ሕገ መንግሥቱን መሬት ላይ በማውረዱ ሒደት እንደሆነ ያትታል፡፡ ቢያንስ ጥናቱ፣ በአዲስ አበባ ማስፋፊያ ማስተር ፕላን ሳቢያ ተቆስቁሶ ለብዙ ንፁኃን ሕይወት ማለፍ መንስዔ የሆነውን በርካታ ጥያቄዎችን ያነገበው ሕዝባዊ አመፅ እንደምክንያት በመጥቀስ እውነት ለመናገር መድፈር ነበረበት፡፡ የዚህ ሰነድ ባለቤት ኦሕዴድ ቢሆንም የሕወሓትን ይሁንታ ሳያገኝ እዚህ ደረጃ እንደማይደርስ መገመት ቀላል ነው፡፡

Wednesday, April 19, 2017

‘ኢትዮጵያዊ ርስበርስ መባላቱን፥ ነብር ዥንጉርጉርነቱን ሊለውጥ ይችላልን?’

ትላንት
     ነብይ ባገሩ አይከበርም
ዛሬ
     ነብይ ባገሩ አይኖርም
ነገ
     ነብይ ባገሩ አይፈጠርም
(በዕውቀቱ ሥዩም)

ፌስቡክ የትውልዳችን ማንነት ገመና ገላጭ ነው። የመግቢያዬ ግጥም ገጣሚ፣ በትውልድ ፈርጥነቱ ሊወደስ ሲገባው፥ የሚናገረውን እንኳ በማያውቅ መደዴ ሲዘለፍ መዋል የጀመረው ፌስቡክ ላይ ከወጣ ወዲህ ነው። ነገሩ የኛ ትውልድ፣ የፌስቡክ መንደር ድክመት ብቻ ነው ብዬ ባምንና ባልፈው ደስ ይለኝ ነበር። ነገር ግን እንደጨጓራ ራሱን የበላው 'ያ ትውልድ'ም፣ የ'ያ ትውልድ' አሳዳጊም፣ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ያው ሆኖ መሰለኝና ብዕሬን ለቁዘማ መዘዝኩ።

አሁን ኢትዮጵያ 'ፈላስፋ' ነበራት ለማለት የምናጣቅሰው፣ ፈረንጆቹ "ኢትዮጵያዊ አይደለም" ሲሉ 'ዘራፍ' ብለን የምንሟገትለት ዘርዐ ያዕቆብ፣ በሐሳቡ ምክንያት ከትውልድ አገሩ አኵሱም ተሰዷል፣ ለማኝ ሆኖ ዋሻ ውስጥ ኖሯል፣ ጎንደር ዘልቆ ራሱን ቀይሮ ዕድሜውን ለመጨረስ ተገዷል። እርግጥ ነው ይህ መልካም ሰው የማሳደድ አባዜ የዓለም አባዜ ነበር። ይሁን እንጂ አባዜው ዛሬ ለቀሪው ዓለም 'ነበር' ሲሆን ለኛ ግን 'ነው' ሆኖ ዘልቋል። የግሪኩ ሶቅራጠስ፣ አፍላጦንን፣ አፍላጦን አሪስጣጣሊስን… እየተኩ ሲያልፉ የእኛዎቹ ዘርዐ ያዕቆብ እና ወራሹ ወልደ ሕይወት በወላድ አገር ምትክ አጥተው መካን ሆነው ቆመዋል። ከዓለም በከፋ ኢትዮጵያ ውስጥ አዲስ ሐሳብ ይዞ መምጣት በንጉሡም፣ በጳጳሱም፣ በምዕመኑም ያስቀጣል(ነበር)። ልዩነቱ ይኼ ነው።

በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ጊዜ ለንጉሥ አንሰግድም ያሉት አባ እስጢፋኖስ እና ደቂቆቻቸው ዕጣ ፈንታ መስዋዕትነት ነበር። በየዘመኑ የተለዩትን፣ የተሻሉትን ስንገድል ነው የኖርነው። እንደካሮት ቁልቁል የማደጋችንም ምሥጢር ይኸው ይመስለኛል። ዐፄ ዮሓንስ ፬ኛ በሐሳብ ልዕልና እንደሚያምን ሰው ታሪካዊውን የቦሩ ሜዳ የሊቃውንት ሙግት ካሰናዱ በኋላ አሸናፊውን ራሳቸው ቀድመው የሚደግፉትን ቡድን አድርገው ሲያበቁ፣ ፍርዳቸው የተቃወመውን ሁሉ ምላሱን እዚያው አስቆርጠዋል።

Transforming Ethiopia’s Exclusionary Constitution into an Inclusive One

Before introducing my proposal, I would like to explain my motivation for writing this now. One of the outcomes of the National Dialogue o...