Pages

Tuesday, September 10, 2013

2005 ቢደገም አልጠላም!


ዓመት በመጣ ቁጥር የግል ስኬቴን የምመዘግብበትና ዓመቱ ሲያልቅ የምለካበት አጭር ጽሑፍ አዘጋጃለሁ፡፡ ብዙ ጊዜ ከመቶ 40 እንኳን አይሳካልኝም፡፡ በሌላ ጽሑፍ በተረክኩት የመታሰር ገጠመኜ (…የቀይ ለባሾቹ ውሎና አዳር…) ፖሊሶች ወስደው ካስቀሩብኝ ብጭቅጫቂ ወረቀቶች መካከል የ2005 ዕቅዴ ይገኝበታል፡፡ በዚህ መሠረት ዓመቱ ቢደገም የማልጠላው አንድም የተሳካ ስለመሰለኝ፣ አሊያም አለመሳካቱን መለኪያ ስለሌለኝ ይሆናል ማለት ነው፡፡

2005 ብዙ የማኅበራዊ አውታር ወዳጆቼ እንደተስማሙበት አስተማሪ ነበር፡፡ እንዲያውም አንድ ወዳጄ እንዳለው ‹‹የዘንድሮው ማንነትህ፣ የአምናውን ቢያገኘው ተበሳጭቶበት በጥፊ ይመታዋል፡፡›› ማኅበራዊ አውታሮች (በተለይም ፌስቡክ) በኢትዮጵያ ወቅታዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሞቀ ሙግት በማስነሳት የአስተሳሰብ እና የውይይት ልምዳችንን ይሞግቱታል፡፡ ፌስቡክ ሰዎች በሙሉ ዕኩል ቢሆኑ ሊፈጠር የሚችለውን ነገር ማሳያ መሣሪያ እየሆነ ነው፡፡ ስንቶች በጥንቃቄና በስንት ልፋት የገነቡት በአንዲት ቃል የሚፈርስበት፣ ስንቶች ሊያፈርሱት የደከሙለት በሌላ አንድ ቃል የሚገነባበት መድረክ ነው፡፡ የሕዝባችን ጥንካሬም ድክመትም የሚስተዋልበት ገጽ ነው፡፡ ፌስቡክ ብስጭታችንን ማደቢያ (anger management) ትምህርት ቤት ነው፡፡ እውነቱም፣ ሐሰቱም ገዝፎ የሚታይበት ዓለም ነው፡፡ ፌስቡክ ከነድክመቱም ቢሆን መደበኛውን መገናኛ ብዙኃን (mainstream media) አጀንዳ እየሰጠ ይመግበው ጀምሯል፡፡

በኢትዮጵያ ፌስቡክ የኢንተርኔት ዕኩያ ቃል (synonym) ሆኗል ማለት ይችላል፡፡ ብዙ ጦማሪዎች ጦማራችን ሲታገድ ፌስቡክ ላይ የምንጽፈው ያንኑ በመተማመን ነው፡፡ እርግጥ ጦማር ላይ የሰፈረውም ጽሑፍ ማኅበራዊ አውታሮች ላይ ካልተጋራ አንባቢ አይጎበኘውም፡፡ ነገር ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ረዣዥም ጽሑፎችን በጦማር ላይ ከማስፈር ይልቅ፣ አጫጭር የማኅበራዊ አውታር ጽሑፎች ተነባቢም፣ አሟጋችም ሆነው በማግኘት ከአጋማሽ ዓመቱ ወዲህ ትጋቴ ቀንሷል፡፡ ቢሆንም በዓመቱ ዞን ዘጠኝ እና የግሌም ጦማር ላይ ያሰፈርኳቸውን ጥቂት ጽሑፎች እዚህ ዘርዝሬላችኋለሁ፡፡ የአምናውን (2004 ሒሳብ ሲዘጋ) እና የካቻምናምናውን (ሁለት ሺህ ሦሰትን በአርባ ሁለት) ዝርዝሮቼን እዚሁ ማየት ይቻላል፡፡

የዘንድሮ ዓመት ስኬታማ ነው ያልኩባቸውን ጥቂት ነገሮች ሳልጠቅስ ማለፍ የለብኝም፤ ምክንያቱም ጽሑፉ ከርዕሱጋ ይጋጭብኛል፡፡ የመጀመሪያው ሊሆን የሚችለው፤ ምንም እንኳን ለታዳጊ ወጣቶች የተጻፈ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን በአገርኛ ቋንቋ የተጻፈ ባይሆንም፣ ምንም እንኳን ልቦለድ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን ብዙዎች ባያውቁትም የበኩር መጽሐፌ (‘Children of Their Parents’) የታተመለኝ በ2005 ነው፡፡ ‹ዞን ዘጠኝ› (ኢ-መደበኛ የጦማሪዎች እና አራማጆች ቡድንም) ከልቤ የማምንበትን ጉዳይ ጮክ ብዬ እንዳወራ፣ ባይበዛም ብዙዎችን የሚያነቃቃ ሥራ እንድሠራ ከዚያም በላይ ተጨማሪ የልብ ወዳጆችን እንዳገኝ የረዳኝ ከመቼውም በላይ በዘህ ዓመት ነው፤ በ2005 ‹ዞን ዘጠኝ› ተራ ቡድን ሳይሆን በብዙ ጎኑ ትምህርት ቤት ነበር፡፡ 2005 ቢደገም አልጠላም፡፡

በ2005 የጻፍኳቸው መጣጥፎች

10. ኢትዮጵያውያን ፍቅር ያውቃሉ? (ከሶልያና ሽመልስ ጋር በጋራ)
12. መክሸፍእንደ ኢትዮጵያ ሚዲያ - መጽሔቶች (ከሶልያና ሽመልስ ጋር በጋራ)
26. ወጣት ወንድ የመሆን ጣጣ (ከእንዳልካቸው ኃ/ሚካኤል ጋር በጋራ)
31. የኛ ኃይል (ከሶልያና ሽመልስ ጋር በጋራ)

No comments:

Post a Comment