Pages

Tuesday, September 24, 2013

የ‘ያ ትውልድ’ መጽሐፍ ማሳተም ለ‘ይህ ትውልድ’ ምኑ ነው?

ከክፍሉ ታደሰ መጽሐፍ በመዋስ በተለምዶ ‘ያ ትውልድ’ እያልን የምንጠራው ትውልድ በ1966ቱ አብዮት ወቅት ወጣት የነበረውን ትውልድ ነው። አሁን በቅርቡ ከተጻፉት ውስጥ፣ (1) ዻንዲ — የነጋሶ መንገድ፤ (2) ሕይወት ተፈራ —   ‘Tower in The Sky’፤ (3) ዶ/ር መረራ ጉዺና — ‘የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የሕይወቴ ትዝታዎች’፤ (4) ኢ/ር ኃይሉ ሻወል — ‘ሕይወቴና የፖለቲካ እርምጀዬ’ (?)፤ (5) ቡልቻ ዸመቅሳ—  My Life and My Vision ይገኙበታል። እዚህ ውስጥ ያልጠቃቀስኳቸውም ሌሎችም ብዙ አሉ። ሆኖም ማውራት ለምፈልገው የጠቀስኳቸው ይበቁኛል።

ከጠቀስኳቸው የ‘ያ ትውልድ’ ጸሐፍት ውስጥ የአሁኑ ፖለቲካ ውስጥ የሌለችው ሕይወት ተፈራ ብቻ ነች። ሆኖም ሁሉም የሚጋሩት አንድ ነገር ያለ ይመስለኛል፤ የ‘ያ ትውልድ’ ፀሐይ እየጠለቀች መሆኑን በማመናቸው። ይህን ማመናቸውን በግምት ነው የምናገረው። ነገር ግን እነዚህ ሁሉ የሕይወት ልምድን ማጋራቶች አንድም ከእርምጃዎቻቸውና ስህተቶቻቸው እንድንማር፣ አሊያም ደግሞ ሕልሞቻቸውን ከግብ እንድናደርስ ነው። የተጻፉት መጽሐፍት በቂ ባይሆኑም ‘ይህ ትውልድ’ ግን ያለበቂ ትምህርትም ቢሆን አገሪቱ እጁ ላይ መውደቋ አይቀርም። ትውልዱ ይህን አውቆ ተዘጋጅቷል?

“እናቸንፋለን” ወይስ “እናሸንፋለን”?

መጽሐፍ እየጻፈ ያለው ‘ያ ትውልድ’ ብቻ ሳይሆን ‘ይህ ትውልድ’ም ጭምር ነው። (ይህ ትውልድ የምለው ከሀያዎቹ አጋማሽ እስከአርባዎቹ አጋማሽ ያለውን ነው።) ለምሳሌ የልደቱ አያሌው ‘ሦስተኛው አማራጭ’፣ የግርማ ሰይፉ ‘የነፃነት ዋጋው ስንት ነው?’፣ የአንዱዓለም አራጌ ‘ያልተኬደበት መንገድ’ እና ሌሎችም እየወጡ ነው። የነዚህኞቹ ከነዛኞቹ የሚለየው አማራጭ መንገዶች ማመላከት ላይ ወይም ያልተኬደበትን መንገድ ማፈላለግ/ማመላከት ላይ ያተኩራል። የተሄደበትን ከያኛው፣ ያልተሄደበትን በይህኛው ማለት ነው።

‘ይህ ትውልድ’ ከ‘ያ ትውልድ’ ስህተት መውሰድ የሚገባው የመጀመሪያው ትምህርት በጥቂት ልዩነት ጎራ ለይቶ አለመቀጣቀጥን ነው ባይ ነኝ። ‘ያ ትውልድ’ በአንድ ርዕዮተ ዓለም፣ በአንድ ዓይነት ሕልም በቃላት አጠቃቀም ውስጥ ለውስጥ በአንጃነትና በሌላም በሌላም ሲከፋፈልና ሲቆራቆዝ እዚህ ደርሷል —  ቢያንስ እስከ ምርጫ 97። ልዩነትን አቻችሎና ተወያይቶ የመፍታት፣ ከነልዩነትም ቢሆን  (ከ“እናቸንፋለን”፣ “እናሸንፋለን” ዓይነት ትናንሽ የቃላትና አተረጓጎም ልዩነት ይልቅ) በዋነኛ አገራዊ ጉዳዮች (ዴሞክራሲ ማምጣት፣ ድህነትን ማጥፋት… የመሳሰሉት) ላይ ማተኮር ያስፈልጋል።
“እኔ ያልኩት ካልሆነ” የሚለው የቃል ሐረግ ካልሞተ የ‘ያ ትውልድ’ ፀሐይ ብትጠልቅም የ‘ይህ ትውልድ’ ፀሐይ አትወጣም።

እናሸንፋለንም፣ እናቸንፋለንም

አንተ ወይም እኔ (እኔ ወይም ሞት) ሞቷል። አሁን ያለው አማራጭ እኔንም አንተንም አካታች የሆነ አማራጭ ብቻ ነው፤ አንዱ ሲያሸንፍ/ሲያቸንፍ ሌላው የማያጎድልበት፣ ሁሉም የሚያሸንፍበት/የሚያቸንፍበት ነው።

ይሄ ትውልድ በኔ እምነት ከያ ትውልድ ይሻላል። በቀኖና የሚነገሩት የ‘ያ ትውልድ’ ድርሳናት ‘ይህን ትውልድ’ የሚያጣጥሉት በያ ትውልድ መለኪያ እየመዘኑት ነው። ይህ ትውልድ የራሱ መንገድ አለው ብዬ አምናለሁ።  ስለአንባቢነት የሚወራውም ቢሆን ተጨባጩን እውነታ ያላገናዘበ ብዥታ ነው ብዬ የምረዳው። ብዙኃኑ ያኔም ሆነ አሁን ኖሮ አላፊ ነው። ልሒቁ ነው ለውጥ የሚያመጣው። ማንም ማንንም የማያጠፋበት የለውጥ መንገድ ደግሞ በዚህ ትውልድ እጅ አለ ብዬ አምናለሁ።
መልካም የለውጥ መንገድ!

No comments:

Post a Comment