Pages

Tuesday, October 9, 2012

የኃይለማርያም ፲ ተግዳሮቶች

From አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ


የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ኅልፈት ከተሰማ 50 ቀናት ሆኑት፤ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ቃለ መሓላ ከፈፀሙ ደግሞ 18 ቀናት፡፡ እነዚህ ከሁለት ሳምንታት እምብዛም ያልበለጡ ቀናት የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያምን አያያዝ ለመገምገም በቂ አይደሉም ነገር ግን ‹‹ያባት ዕዳ ለልጅ›› በሚለው ብሒል መሠረት የመለስን ፈለግ በመከተል እና ባለመከተል መካከል፣ ሊያመጧቸው በሚችሏቸው ለውጦች እና ሕዝብ/አገር ከሚጠብቅባቸው ነገሮች አንፃር የሚጠብቃቸውን ተግዳሮት ማስቀመጥ ይቻላል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም በተለይ ከቪኦኤ የእንግሊዝኛው አገልግሎት ጋር ባደረጉት የ40 ደቂቃ ቃለምልልስ፥ ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር የተለየ አቋም እንደሌላቸው መታዘብ ይቻላል፡፡ ፓርቲውም ቢሆን የአቶ መለስን ውርስ ለማስቀጠል እንደሚተጋ በተደጋጋሚ ተናግሯል፡፡ በተቃራኒው መለስ የሚባልላቸውን ያህል ውጤታማ እና ፍፁም አልነበሩም፡፡ ለዚህም ምስክሩ ሳይዘጉ የተዉአቸው የሚከተሉት አጀንዳዎች ናቸው፡፡ የአቶ ኃይለማርያም ተግዳሮቶች ሁነው ይቀጥላሉ፡፡

፩ - የምርጫ 2007 ጉዳይ

ምርጫ 2007፣ በ20ዓመት ውስጥ መለስ በበላይነት የማይከታተሉት/የማይመሩት የመጀመሪያው ምርጫ ነው፡፡ ከምርጫ 97 ውጤት አወዛጋቢነት፣ ከምርጫ 2002 የኢሕአዴግ ጠቅላይ ገዢነት በኋላ የሚካሄድ ማንኛውም ምርጫ ቀልብ የሚስብ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ ከዚያም በላይ ደግሞ ለሁለቱም ምርጫዎች እንከን ተጠያቂ የሆኑት መለስ አለመኖራቸው፥ የተለየ ነገር ይኖር ይሆን የሚለውን ጥርጣሬ በር ይከፍትለታል፡፡

ይህንን ጥርጣሬ አዎንታዊ ምላሸ ሰጥቶ ተአማኒነትን ለመጎናፀፍ አቶ ኃይለማርያም ቀላል የማይባል ተግዳሮት ይጠብቃቸዋል፡፡

ተቃዋሚ ፖለቲከኞች በ1987፣ በ1992 እና በ1997 ማግኘት ከቻሉት የፓርላማ ወንበር አንፃር በ2002 ወደ አንድ ወንበር የተመለሱት በፖለቲካው ምሕዳር መጥበብ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ኢሕአዴግ በደፈናው ይህን ቢክድም መከራከሪያ ነጥቦችን ዘርዝሮ እውነታውን ማረጋገጥ ግን ከባድ አይደለም፡፡ ስለዚህ አቶ ኃይለማርያም ባላቸው ስልጣን ሁሉ ተጠቅመው ይህን ምህዳር ማስፋት ወይም ወደነበረበት መመለስ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ፈተናው ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ሕዝባዊ ቅቡልነት የሚያገኝ ምርጫ ከማካሄድም በተጨማሪ በፓርቲው አባሎች እና ደጋፊዎች ኢሕአዴግን ለስልጣን የሚያበቃ የፓርላማ ወንበር እንዲያስገኙለት ይጠበቅባቸዋል፡፡ አለበለዚያ፣ ሕዝቡ ድምፁን ለኢሕአዴግ የነፈገው በከረመ ብሶቱ ቢሆንም እንኳን በእርሳቸው አስተዳደር መሳበቡ የማይቀር ተግዳሮታቸው ነው፡፡

፪ - የሕዳሴው ጉዳይ

የኢትዮጵያ መንግስት በተለይ ከ2000 ወዲህ ያለውን ጊዜ የሕዳሴው ዘመን ብሎ ሰይሞታል፡፡ ከምርጫ 2002 ውጤት በኋላ ደግሞ በአምስት ዓመታት የሚጠናቀቅ፣ ‹‹የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ›› የተሰኘ፣ በጣም አጓጊ፣ ድህነትን ‹ቻው፣ ቻው› ለማለት ያለመ ዕቅድ ተነድፏል፣ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ አንዱ የዚህ አካል ነው፡፡

የ‹ትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ› ሁለት ዓመቱን የጨረሰ በመሆኑ እስካሁን የመጣበት መንገድ በአምስት ዓመት ውስጥ የተባለው ቦታ እንደማያደርስ ያሳብቃል፡፡ የሕዳሴው ግድብ መጀመሪያ በአራት፣ ቀጥሎ በሰባት ዓመታት ያልቃል የተባለ ቢሆንም አንደኛ ዓመቱን ሲያከብር 6 በመቶ ብቻ መጠናቀቁ ስለተነገረ በዚህ ስሌት 16 ዓመት ድረስ ሊፈጅ እንደሚችል ይገመታል፡፡

ከዚህ እውነታ በተቃራኒ መለስ የኢትዮጵያ መሐንዲስ ናቸው በሚል ሲሞካሹ፣ እንከን የማይወጣላቸው እንደነበሩም እየተነገረ ነው፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ፣ ለዕቅዶቹ በታቀደላቸው ጊዜ አለመጠናቀቅ ተጠያቂ የመሆን ተግዳሮት የሚገጥማቸው አቶ ኃይለማርያም ናቸው፡፡

፫ - የኑሮ ውድነት ጉዳይ

የአቶ መለስ አስተዳደር በጣም ሲወቀስባቸው ከነበሩ ጉዳዮች መካከል የኑሮ ውድነት በግንባር ቀደምነት ይታወሳል፡፡ በተለይም የከተማ ኑሮ ውድነት በየዕለቱ እያሻቀበ እና የብር የመግዛት አቅም እየወረደ መምጣቱ ለመንግስታቸው የራስ ምታት መሆኑን የኢሕአዴግ ሰዎችም ቢሆኑ የማይክዱት ሐቅ ነው፡፡ መጀመሪያ ሰሞን መለስ የዋጋ ግዥበቱ የተከሰተው በኢኮኖሚያችን ማደግ ምክንያት የግለሰቦች ፍላጎት በማሻቀቡ መሆኑን የተናገሩ ቢሆንም፣ ቆይተው መንግስት አላግባብ ብዙ ብር ማተሙን እንደምክንያት መጥቀሳቸው ይታወሳል፡፡

የኑሮ ውድነት፣ ከፖለቲካዊ ጥያቄዎች ሁሉ በላይ ሕዝቡን አስቆጥቶ ለለውጥ ሊያነሳሳው ይችላል እየተባለ በሚፈራበት በዚህ ወቅት፣ አቶ ኃይለማርያም የአመራሩን በትር ጨብጠዋል፡፡ ስለሆነም ይህንን ለ10 ዓመታት ያህል በሚያስፈራ ፍጥነት እየገሰገሰ ያለውን የዋጋ ግዥበት መቆጣጠር አለዚያም ውጤቱን መቀበል የኃይለማርያም ሌላኛው ተግዳሮት ነው፡፡

፬ - የዳያስፖራዎች ጉዳይ

መለስ እና ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች ዓይንና ናጫ ሁነው መክረማቸው የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ በተለይም በሰሜን አሜሪካ፣ በአንዳንድ የአውሮፓ አገራት እና በደቡብ አፍሪካ መለስ የሚገኙባቸው ስብሰባዎች ሁሉ በተቃው ሰልፍ ይጥለቀለቁ ነበር፡፡ ዳያስፖራው፣ በሚከፍታቸው የተለያዩ ድረገጾች ምርር ያለ ተቃውሞውን ሲያሰማባቸው ከርሟል፡፡ በጥቅሉ መንግስታቸው የዳያስፖራውን ድጋፍም እውቅናም አጥቷል ማለት ይቻላል፡፡

አቶ ኃይለማርያም ምንም እንኳን የመለስን ጅማሮ የማስቀጠል ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ደጋግመው ቢናገሩም፣ ጠባቸውንም ለማስቀጠል ይሻሉ ብዬ አልገምትም፡፡ ይሁን እንጂ የዳያስፖራውን ልብ መልሰው ለኢሕአዴግ የማራራቱ ጉዳይ ቀላል ተግዳሮት አይሆንላቸውም፡፡

፭ - የተአማኒ ተቋማት ጉዳይ

ወሳኝ የሚባሉት የመንግስት ተቋማት - ለምሳሌ ፍርድ ቤት፣ መገናኛ ብዙሐን (የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን፣ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና ሌሎችም…)፣ የምርጫ ቦርድ፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ ዕንባ ጠባቂ ድርጅት፣ የኢትዮጵያ ሰብዐዊ መብት ኮሚሽን እና ሌሎችም ለመንግስት ወይም ለገዢው ፓርቲ ይወግናሉ የሚል ቅሬታ በኅብረተሰቡ ውስጥ ይንፀባረቃል፡፡ እንዲያውም፣ የመንግስት እና የገዢው ፓርቲ ሥራ ተቀላቅሎ እየተሠራ ነው፤ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች የመንግስትን ኃብት እየተጠቀሙ ነው የሚል ተደጋጋሚ ወቀሳ ይሰማል፡፡ መንግስት ከሷቸው የተረታባቸው፣ ወይም መንግስትን ከሰው የረቱ ተቃዋሚ ግለሰቦች ወይም ድርጅቶች የሉም የሚል ብሶት ይሰማል፡፡

በዚህ ዐውድ ውስጥ ያሉና ተአማኒነታቸውን ያጡ ተቋማት እንዲህ ሁነው መዝለቅ እንደለሌባቸው ይታመናል፡፡ ይህንን እውነታ መረዳትና በቁርጠኝነት መፍትሄ የመፈለግ ወይም ተቋማትን ከፓርቲ ተፅዕኖ የማላቀቁ ተግዳሮትም አቶ ኃይለማርያን እየጠበቃቸው ነው፡፡

፮ - የኤርትራ ጉዳይ

የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ጦርነት ምንም እንኳን በዝምታ ላይ ቢገኝም፣ አንድ ቀን ያገረሽ ይሆን የሚለው ጉዳይ የሁለቱ አገራት ብቻ ሳይሆን የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የዘወትር ስጋት ነው፡፡ እንዲያውም የአቶ መለስን ሞት ተከትሎ ሊቀሰቀሱ የሚችሉ ግጭቶች ይኖሩ ይሆናል የሚሉ ፍራቻዎችም በጥቂቶች አዕምሮ ውስጥ አለ፡፡

ይህም ብቻም አይደለም፣ ለአንዳንዶች የአሰብ ጉዳይ የተዘጋ ጉዳይ ነው፡፡ ጥቂት ለማይባሉት ደግሞ ገና ትኩስ አጀንዳ እንደሆነ ተዳፍኖ አለ፡፡ ተቃዋሚዎች ወደብ ጉዳይ ላይ ቀርተዋል እየተባሉ የሚታሙትም ለዚያው ነው - ጉዳዩ የተዘጋ የሚመስለውን ያክል ያልተዘጋ በመሆኑ፡፡ በዚህ መሓል፣ ሊመለሱ ለሚችሉ ጥያቄዎች መልስ ማፈላለግ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ሰላምን ባለበት ማቆየት፣ ምናልባት ግጭት ቢፈጠር እንኳን ተዘጋጅቶ መጠበቅ እና አገሪቱ ላይ ቀውስ ሳያስቀጥል በፊት መቆጣጠር የአቶ ኃይለማርያም ተግዳሮት ይሆናል፡፡

፯ - የሶማሊያ ጉዳይ

ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ ከኃይለሥላሴ ጊዜ ጀምሮ የሚቆሰቆስ እና የሚከስም ግጭት አላቸው፡፡ አሁን ግን ዋናው ጠብ ከዋናው መንግስት ጋር ሳይሆን፣ ከአል ሻባብ ጋር ነው፡፡ አል ሻባብ በአልቃይዳ ይረዳል በሚል ከኢትዮጵያ ይልቅ ጠላትነቱ ለአሜሪካ ነው፣ ይህንን ያክል ተቀባይነት እንዲያገኝ ያደረገው የአቶ መለስ መንግስት እርሱን ለመውጋት ሶማሊያ መግባቱ ነው የሚሉ ክሶች ተደጋግመው ይሰማሉ፡፡

ኢትዮጵያ አል ሻባብን አባርሬ መጣሁ ብላ ተናግራ ሳትጨርስ አል ሻባብ ከሽግግር መንግስቱ መቋዲሾን መቀማቱ ተሰማ፡፡ አሁንም በድጋሚ የኬንያን ሠራዊት ተከትሎ የኢትዮጵያ ሠራዊት ሶማሊያ ውስጥ ይገኛል፡፡ አል ሻባብ የአቶ መለስን ሞት ተከትሎ ኢትዮጵያ ላይ ዛቻ የሚመስል መግለጫ አውጥቷል፡፡ አሁን በርግጥም አል ሻባብ ጠላታችን ነው፤ ስለዚህ በሕዝብም ሆነ በአገር ላይ ሊያደርስ የሚችለውን አደጋ ቀድሞ መከላከል፣ ሶማሊያን በሠራዊትም ሆነ በሰው ኃይል እየደገፉ በተዘዋዋሪ የኢትዮጵያን ደህንነት የማስጠበቁ ጉዳይ ለኃይለማርያም ቀላል ተግዳሮት አይደለም፡፡

፰ - የፖለቲካ እስረኞች ጉዳይ

አቶ መለስ ኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ እስረኛ የለም ብለው ያምኑ ነበር፡፡ አቶ ኃይለማርያምም ይህንኑ ጉዳይ ለቪኦኤ ሲያስረዱ የታሰሩት ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞች ጉዳይ ሁለት ባርኔጣ የማድረግ ጉዳይ ነው ብለውታል፡፡ በአንደኛው ባርኔጣቸው በሕጋዊ መንገድ ጋዜጠኝነት እና ፖለቲከኝነታቸውን ይተገብራሉ፣ በሌላኛው ባርኔጣቸው በጋዜጠኝነት እና በፖለቲከኝነት ስም ያሸብራሉ ባይ ናቸው አቶ ኃይለማርያም - ተከሳሾቹ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችን፡፡

በዚህ ግን ብዙዎች አይስማሙም፤ የጋዜጠኛ ማኅበራት፣ የሰብዐዊ መብት ተቆርቋሪዎች እና ኃያላን መንግስታት ሳይቀሩ በኦፊሴላዊ መግለጫዎች ይህንን አውግዘዋል፣ እያወገዙም ነው፡፡

እንዲያውም ኢሕአዴግ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ መርሑ፣ በአውራ ፓርቲ ስም ጠቅልሎ በመግዛት ሕልሙ የፈጠረው የፖለቲካ ምሕዳርን የማጥበብ እና ለስልጣኑ የሚያሰጉ ወገኖችን የማፈኛ ዘዴው ነው ብለው ይማረራሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች እውነት የላቸውም ብሎ ማስረጃ መስጠት ለገዢው ፓርቲ ይከብደዋል፡፡ አቶ ኃይለማርያም ሌሎች ጋዜጠኞችን እና ፖለቲከኞችን ያለማሰር ብቻ ሳይሆን፣ የታሰሩትን ማስፈታት እና የተሰደዱትን በማስመለስ ሰላማዊ የተቀናቃኝነት መንፈስ የማዳበር ታላቅ ኃላፊነት እና ተግዳሮት ከፊታቸው ይጠብቃቸዋል፡፡

፱ - የሰብዐዊ መብት እና ዴሞክራሲ ጉዳይ

የአቶ መለስ መንግስት ክፉኛ ሲወቀስባቸው የነበሩት ጉዳዮች በሕገ መንግስቱ የተደነገጉትን ሰብአዊ እና ፖለቲካዊ መብቶችን በመጣስ ነው፡፡ አቶ መለስም ራሳቸው፣ በተለይም በዓለም አቀፍ አደባባዮች ዴሞክራሲያቸው ገና በዕድገት ላይ መሆኑን እና ለልማት ትኩረት በመስጠታቸው የደከሙበተ የቤት ሥራ እንደሆነ ለማስረዳት ሲጥሩ ከርመዋል፡፡ ልማቱ በራሱ ተሳክቷል/አልተሳካም የሚለው ጉንጭ አልፋ ክርክር ቢሆንም፣ ልማትም ሆነ ዴሞክራሲ በሒደት የሚመጡ ነገሮች መሆናቸውን መካድ አይቻልም፡፡ ነገር ግን ለልማቱ ተተግቷል የሚባለውን ያክል ለዴሞክራሲ ያልተተጋበት ምክንያት ምን እንደሆነ አይታወቅም፡፡

ይህ የሰብዐዊ መብት እና የዴሞክራሲ ጥያቄ በተለይም በምዕራባውያን ዘንድ ኃይለማርያምን የሚገዳደር ጉዳይ እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ ምዕራባውያን ከመለስ ጋር በነበራቸው የፀረ - ሽብር የጋራ ወዳጅነት እና በመለስ አንደበተ ርቱዕነት፣ የእርዳታ አሰጣጥ ቅድመ ሁኔታቸው የነበረውን ዴሞክራሲ ዘንግተውት ከርመዋል፡፡ በዚሁ ግን ላይቀጥሉ ይችላሉ፤ ለዚህ እና ለሕዝባቸውም ሲሉ አቶ ኃይለማርያም የዴሞክራሲ እና ሰብዐዊ መብት ጥበቃን ጉዳይ ዋጋ ለመስጠት እንዲተጉ የሚጠበቅባቸው፡፡

፲ - የኢሕአዴግ ውስጥ ጉዳይ

ኢሕአዴግ የአራት ፓርቲዎች ድምር መሆኑ ይታወቃል፡፡ በመለስ አገዛዝ ስር፣ የኅወሓት ሚና ከሌሎቹ የጎላ ሆኖ የቆየ ቢሆንም አሁን ብዙዎች እንደሚገምቱት በኅወሓት የኋላ ግፊት በአቶ ኃይለማርያም አመራር የበፊቱ ሕብረታቸው ይኖራል ብሎ መጠበቅ የዋሕነት ሊሆን ይችላል፡፡ መለስ በሁሉም ፓርቲዎች፣ በተለይም በኀወሓት ተቀባይነት ስለነበራቸው፣ አንዱን ሲጫኑ እንኳን ተቀባይነት የማግኘት ዕድል ነበራቸው፡፡ አቶ ኃይለማርያም፣ በኅወሓት የበላይነት ከሚመራው ሠራዊት አንስቶ ሌሎቹንም ፓርቲዎች የማዘዙ ጉዳይ ትልቅ ተግዳሮት ይሆንባቸዋል፡፡

የኢሕአዴግ ፓርቲዎች ከመለስ ኅልፈት በፊት ወደአንድነት ይዋሃዳሉ ተብለው የነበረ ቢሆንም ባልታወቀ ምክንያት የሚዋሃዱበት ጊዜ ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል፡፡ ያንን የውህደት ዕድል የመምራቱም ሆነ ሁሉንም ፓርቲዎች አቻችሎ በስምምነት የማስቀጠሉ ፈተና በፍፁም ቀላል አይሆንም፤ ካልተሳካላቸው ደግሞ ግንባሩ ሊሰነጣጠቅ እና እንደገዢ መቆም ሊያቅተው ስለሚችል በፓርቲው ውስጥ ምናልባት ሊገጥሟቸው ከሚችሉ ተግዳሮቶች ሁሉ ይህ የበረታ ነው፡፡

እንግዲህ ዋና ዋናዎቹን ብቻ ለመዘርዘር ተሞከረ እንጂ ከዚህም በላይ ተግዳሮቶች እንደሚኖሩባቸው መገመት ቀላል ነው፡፡ ኢሕአዴግ እስካሁን ድረስ ያልተላቀቀውን የጫካ መንፈስ ማጥፋት፣ የፕሬሱን ነፃነት ማጠናከር እና ሌሎችም በርካታ ተግዳሮቶች ይኖሩባቸዋል፡፡

በዚህ ጽሑፍ ተግዳሮቶቻቸውን ብቻ ለመግለፅ ሞከርን እንጂ በርካታ ዕድሎችም አሉዋቸው፡፡ ከመለስ ሞት በኋላ የተፈራውን እና የተወራውን ያህል በፓርቲው ውስጥም ሆነ በመንግስታዊ አስተዳደሩ ላይ የተከሰተ፣ የጎላ ውዥንብር አለመኖሩ ምናልባትም ፓርቲው በውስጣዊ አሠራሩ ዴሞክራሲያዊ ሊሆን ይችላል የሚል አስተሳሰብ ፈጥሯል፤ ያ እውነት ከሆነ ፓርቲው ሌሎቹን ችግሮች በውስጣዊ የአፈታት ዘዴ በመፍታት ጥንካሬውን ጠብቆ መዝለቅ ይችል ይሆናል፡፡

ከዚያ ውጪ ትልቁ ዕድል፣ አቶ ኃይለማርያም በብዙ መድረኮች የመለስን አስተዳደር ስርዓት ‹‹አስቀጥላለሁ›› እያሉ ቢናገሩም ‹‹ይለውጡታል›› ብለው እምነት የሚጥሉባቸው ዜጎች ግን እልፍ ናቸው፤ የነዚህ ሰዎች ተስፋ ኃይለማርያም ለውጥ የሚፈልጉ ከሆነ በተቃዋሚዎች ሳይቀር በቅንነት የሚጠብቃቸው ክፍት ልቦና አኑሮላቸዋል፡፡

1 comment:

  1. Hi Befekadu,
    When I started my new blog two weeks ago, my first article was on what I thought PM Hailemariam needs to focus on.

    I just saw your post on the same subject today and I would say you did it more comprehensively than I thought.

    I like how you provided constructive criticism in a friendly tone.

    Check out my blog at www.newethiopians.com. I will make sure to read yours regularly. I like what I saw today.

    Melkam Ken

    ReplyDelete