ሰሞኑን ጉምሩክ ከሚሰሩ ሰዎች የሰማሁት ዜና የተለመደ ዓይነት ቢሆንም፥ እንደተለመደው ከመገረም አልዳንኩም፡፡ ጉምሩክ የላካቸው አሥር ጥንዶች አሥር ስጋ ቤቶች ውስጥ ገብተው ቁርጥ እና ጥብሳቸውን ከበሉ በኋላ ከአሥሩ ስጋ ነጋዴዎች አንዱ ብቻ ደረሰኝ ሲያቀርብ ቀሪዎቹ ዘጠኙ ያለደረሰኝ ሒሳብ በመቀበል ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ስታትስቲክስ ውሸታም ነው ቢባልም፣ በዚህ ስሌት እኮ 90 በመቶ የሚሆኑት የሥጋ ነጋዴዎች ታክስ ያጭበረብራሉ ማለት ነው፡፡
ይህንን ዜና ስትሰሙ ለማን አዘናችሁ፣ ወይም በማን አዘናችሁ? ነጋዴዎቹ ምነው ቀድመው መረጃ ቢያገኙ ወይም ምን ዓይነት መንግስት ነው ያለው ብላችሁ ከተማረራችሁ፥ ለፍርድ የቸኮላችሁ ይመስለኛል፡፡ ነጋዴዎቹስ ቢሆኑ ለሕጉ ለምን አይገዙም?
በኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ያልተመለሱ ሕዝባዊና መንግስታዊ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ሁሉም በእኩል ደረጃ አሳሳቢዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ችግሮች ውስጥ አንዱ የሕግ የበላይነት ጉዳይ ነው፡፡ እኔ እንደማስበው በሕግ የበላይነት ጉዳይ ሁላችንም እንስማማለን፡፡ ልዩነታችን በአተገባበሩ ላይ ነው፡፡ ሌላው በዚሁ ማዕቀፍ ውስጥ ያለው ጥያቄ የሕግ የበላይነት ከማን የሚለው ነው - ከሕዝቡ፣ ከመንግስት ወይስ ከሁለቱም?