Pages

Friday, February 7, 2014

“የደወሉላቸውን ደንበኛ ማግኘት አይችሉም"

የኢትዮ-ቴሌኮሟ ቅርፀ-ድምፅ ከመቼውም ጊዜ በላይ ሰሞኑን "የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም" ትላለች። ዛሬ (ጥር 29/2006) ግን ማለዳውን ሙሉ ስልኮች ሁሉ "ዝም፣ ጭጭ" ብለው ነው ያረፈዱት። አዲስ አበባን ከስሪ-ጂ (ሦስተኛው ትውልድ የስልክ በይነመረብ ግንኙነት አቅም) ወደ ፎር-ጂ (አራተኛው ትውልድ አቅም) ለማሳደግ፣ ሌሎቹን ክልሎች ደግሞ ወደ ሦስት ትውልድ ለማሳደግ ሥራዎች እየተጣደፉ እንደሆነ በሚደሰኮርበት በዚህ ሰዓት ኔትዎርኩ እንደ ክሪስማስ ዛፍ ብልጭ ድርግም ይል ገብቷል።

በነገራችን ላይ እኛ 1·1% የኢንተርኔት ፔኔትሬሽን (ተዳራሽነት) ላይ ቁጭ ብለን 28% ደረስኩ ብላ እንቁልልጭ የምትለን ኬንያ፣ በሁሉም ቴሌኮም ድርጅቶቿ የሚቀርቡት የስልክ አገልግሎቶች ከ3ጂ በላይ ናቸው። (Keeping up with the Joneses has become mission impossible).

ምትሐተ-ኢትዮቴሌኮም

ዛሬ የገጠመኝ ደግሞ ለየት ይላል። ሌላ ሰው'ጋ እደውላለሁ ብዬ አብሮኝ ያለው ሰው'ጋ ደወልኩ፤ ቢጠራም አይነሳም። ምንድን ነው ነገሩ ብዬ ስመለከተው የደወልኩት አብሮኝ ያለው ሰው'ጋ ነው።  "እንዴ የደወልኩት ላንተ ነው፤ አንተ ደግሞ አይሰማህም እንዴ?" ብዬ ሌላኛው ስልክ ላይ መደወሌን ቀጠልኩ። እሱ ደግሞ ኧረ እኔ'ጋ አልደወልክም ብሎ ስልኩን ሲያሳየኝ እኔ ከሌላኛው ሰው'ጋ ማውራት ጀምሬ ነበር። ከዚያ አብሮኝ ያለው ሰው የስልኩን ስክሪን ዓይኔ ላይ አምጥቶ ደቀነው። "befeqe is calling..." ይላል። "ኧረ እኔ ከሌላ ሰው'ጋ እያወራሁ ነው!" አብሮኝ ያለው ሰው ስልኩን ሊያነሳ ሲሞክር እምቢ አለው። ሁኔታውን 'ምትሐተ-ኢትዮቴሌኮም' ብለነዋል።

ስልኮቹ በተመሳሳይ ሰዓት ካልተገናኙ (synchronized ካልሆኑ) ማውራት አይቻልም። እንዲህ ዓይነቱ መቀዣበር የሚፈጠረው ስልኮች ሲጠለፉ ነው። ኢትዮቴሌኮም (ወይም ወዳጆቹ) ስልኬን አይጠልፉም ብዬ ባልጠረጥርም የሁሉንም ሰው ስልክ ይጠልፋሉ ብሎ መጠርጠር ይከብደኛል። ፍላጎቱ ቢኖራቸውም አቅም ያንሳቸዋል። የኔትዎርኩ ችግር ደግሞ ባገር የመጣ ነው።

ጠለፋና ማስፋፋት

ሑዋዌይ በአሜሪካ የደኅንነት ቢሮ የጠለፋ ሶፍትዌሮችን እና ሀርድዌሮችን ይጠቀማል በሚል ከገበያ አግዶታል። የኢትዮጵያ መንግሥት ግን ከዜድቲኢ ጋር አብሮ የሚሠራው የቢሊዮን ዶላር የኔትዎርክ ማስፋፊያ ፕሮጀክት ሸልሞታል። ለኛ መንግሥት መሪዎች የአሜሪካው ዜና የምስራች ነው። እንዲያውም ሳስበው ዶ/ር ደብረፅዮን የሑዋዌይን ኃላፊ "እስኪ የሚወራባችሁን ነገር እኛ ላይ ተግብሯትና ይህን ሕዝብ ሲያወራ እንስማው" የሚሉት ይመስለኛል።

ግሎባል ኢንተርኔት ሴኩሪቲ በሪፖርቱ እንደነገረን ተንቀሳቃሽ ስልኮች በኢትዮጵያ ከ3% (እ.ኤ.አ. በ2008) ወደ 18% በ2012 ተዳርሷል። እድገቱ ሸጋ ነው፤ ከጎረቤቶቻችን አንፃር ካላየነው ማለቴ ነው። ከነዚህ ወስጥም ኢንተርኔት የሚሠሩት ስልኮች 6·2% ብቻዎቹ ናቸው።

እንደ ትራንስፎርሜሽን እና ዕድገቱ ዕቅዱ ከሆነ ግን 40 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ተንቀሳቃሽ ይኖራቸዋል። ዶ/ር ደብረፅዮን እንደነገሩን ደግሞ ሌሎች 16 ሚሊዮን የሚደርሱ 3 እና 4ጂ የሚሠሩ ስልኮች ሲጨመሩ 56 እናዳርሳቸዋለን ተብሏል። ማስፋፊያው ሲጨረስ 85% ሕዝቡን የሚያዳርስ የተንቀሳቃሽ ስልክ እናቀርባለን ተብሎ ታቅዷል። 'See Separate' የተባለ ድርጅት ግን በ2015 እ.ኤ.አ. ቁጥሩ 99·6 ሚሊዮን ይደርሳል ከተባለው ሕዝባችን ውስጥ 34·2 ሚሊዮን የተንቀሳቃሽ ስልክ ተጠቃሚዎች ብቻ እንደሚኖሩ (ከዕቅዱ'ጋ ሲነፃፀር 22 ሚሊዮን ያነሰ እንደሚሆን) በሒደቱ (projection) ገምቷል።

የታቀደው ግብ ቢመ'ታ መልካም ነበር። ግን ከታቀደው በታች ተፈፅሞም፣ ጥራቱ ተጓድሎም እንዴት ይሆናል? እስከዛሬ በሁሉም ዘርፎች ላይ የዘገየንባቸው ነገሮች ላይ ከሚሰጡ እልፍ ሰበቦች ውስጥ 'በተዳራሽነት ብዛት ላይ ስናተኩር ጥራት አመለጠን' የሚለው ይገኝበታል። ሁለቱም ላይ ካላተኮርን ሌላ ምን ላይ አተኩረናል ሊባል ነው?

ከሁሉም ግን ስጋቴ የደወሉላቸውን ደንበኛ ማግኘት፣ በፈለጉት ጊዜ የማይችሉ 56 ሚሊዮን የስልክ ደምበኞች እንዳናፈራ እሰጋለሁ።

No comments:

Post a Comment