Pages

Sunday, February 2, 2014

ጥር መጣ ሙሽራ ቀንጥሱ

በጥር ወር ገበሬው ሰብሉን ሰብስቦ የሚጨርስበትና ሠርግ የመደገስ አቅሙ የሚጎለብትበት ወቅት ነው። በዚሁ ተለምዶ ከተሜውም ለሠርግ ጥርን የሚመርጠው ይላሉ የአገራችን የልምድ አንትሮፖሊጅስቶች።

እንደሠርግ እጅ፣ እጅ የሚለኝ ነገር እየጠፋ ነው። ወይ ባሕላዊ አይሆን፣ ወይ ዘመናዊ እንዲሁ የጨረባ ተስካር ብቻ ሰው ሰብስቦ እዩኝ ማለት - ማለት የኛ አገር ሠርግ ትርጉም ሆኗል። ደግሞ የወገኝነቱ አበዛዝ!

ባለፈው ሒልተን ሆቴል ፊት ለፊት አፍሪካ ፓርክ አጠገብ ሙሽሮች የፎቶ ስርዓት እያደረጉ ነበር። ይህ እንግዲህ ከሠርጉ ዕለት ውጪ ለማስታወሻ የሚነሱት ፎቶ ላይ መሆኑ ነው፤ አጃቢ የለም።  አስፋልቱ ላይ ሙሽሪት ተዘርፍጣ፣ ሙሽራም እሷን እየተንከባከበ የሚያስመስለውን ድርጊት እያደረገ ፎቶ ሲነሱ አይቼ ሳበቃ በማየቴ እኔ አፈርኩ። ሚስቴ እንዲህ ዓይነት ነገር እናድርግ ከምትለኝ ጋብቻው ይሰረዝ ብትለኝ ውለታ እንደዋለችልኝ እቆጥረዋለሁ።

የከተሜ ሠርጎች ከሠርጉ በፊት የስቱዲዮ ፎቶ መነሳትን ባሕል አድርገውታል። ስቱዲዮ ውስጥ፣ የተለመዱ የፎቶ አነሳስ ወጎች አሉ። ጥንዶቹ በፍቅራቸው ዘመን አድርገዋቸው የማያውቋቸውን (ለምሳሌ ሙሽራይቱ የሙሽራውን ከረባት እየጎተተች) ለማስታወሻ ፎቶ ይነሳሉ። እኔ የምለው፤ እነዚህ ጥንዶች ወደፊት ማስታወስ የሚፈልጉት ሆነው የማያውቁትን ነገር ነው እንዴ? ስቱዲዮዎቹ በውሸት ጥርብ ግድግዳዎች፣ እንስሳት፣ የሙዚቃ መሣሪያዎችና ጌጣጌጦች ያሸበረቁ ዓይነት ሲሆኑ ጥንዶቹ በኪራይ ልብስ "የውቡ ቤት" ፈርጥ ሆነው ይነሳሉ። ይህንኑ ፎቶም ለልጆቻቸው ማስታወሻ ብለው ሊያሳዩ ያቆያሉ።

ሠርጎች ባብዛኛው ወግ የሚበዛባቸውና ለታይታ የሚደረጉ ሆነዋል። አማራጭ አጥተው ከተጋቡ አስመሳይ ተፋቃሪዎች ጀምሮ ዕድሜ ልካቸውን ከፍለው የማይጨርሱትን ብድር ተበድረው ድል ያለ ድግስ የሚደግሱ ሠርገኞች ድረስ ቲያትሩ ብዙ ነው። አንዳንዶች ሠርግ የሚደግሱት "እወቁልኝ" ለማለት ሳይሆን "እዩልኝ" ለማለት ይመስለኛል። "አታገባም ብላችሁ ያማችሁኝ እነከሊት እርር በሉ አገባሁ…፣ ባለፈው በመርሴዲስ አገባሁ ብለሽ የተቆላሽብኝ እከሊት፥ ያው እኛም በሊሞ ተጋባን…" እየተባባሉ ይመስለኛል።

በዚህ ወር ካየኋቸው ሠርገኞች መካከል ቦሌ መንገድ ላይ ባመሻሹ ብርድ እየተፈጁ በክፍት ጂፕ መኪና ቆመው ሲሄዱ ያየኋቸው ጥንዶች በጣም ካሳዘኑኝ ውስጥ ይመደባሉ። ካሜራ በሌለበት፣ ማንም ሥራዬ ብሎ በማያስተውላቸው ሁኔታ ምን ልሁን ብለው ነው በብርድ የሚገረፉት? የታይታ ፍቅር ተመልካች በሌለበትም ያደክማል።

ትዳር ቀላል ኃላፊነት የሚጠይቅ እርምጃ አይደለም፤ ሠርግ ብቻ የሚመስላቸው ግን እልፍ ናቸው። መሠረታዊ የቤት ዕቃ ያላሟሉ ሰዎች ለሠርግ ድግስ ሊሞዚን በ30 ሺሕ ብር ይከራያሉ። 500 ሰው ጠርተው ውስኪ ይራጫሉ። ለዚህ መደገፊያ "ሠርግና ሞት አንድ ነው"፣ "ዓለምሽ ዛሬ ነው…" እያሉ ይዘፍናሉ። ኑሯቸው ግን የሚጀምረው ከሠርጉ ዕለት ቀጥሎ ነው። ጥንዶች የተጋቡ ዕለት የሕይወታቸውን አቅጣጫ ለመቀልበስ ወደሚያስቸግር አቅጣጫ እንደሚቀይሩ ሠርጉ እስኪያልፍ አይገባቸውም።

አንዱ ላገባ፥ ሌላው ገደል ገባ!

ከሠርግ ሰቀቀኖች ሁሉ የሚከፋው የወዳጅ ጓደኞች ፈተና ነው። በተለይ ሚዜ ተደርገው የሚመረጡ ሰዎች በዚህ የኑሮ ውድነት ኪሳቸው ይነቀላል። ሚዜዎች የራሳቸውን ወጪ እንዲሸፍኑ ስለሚገደዱ ለወዳጅነታቸው ሲሉ ተበድረውም ተለቅተውም ቢሆን አላስፈላጊ ወጪ ውስጥ ይዘፈቃሉ። የወጪው አበዛዝ ደግሞ ወሰን የለውም። የየራሳቸው ሁለት ወይም ሦስት አልባስ እና ከሠርጉ ጋር የተያያዙ ሌሎች ወጪዎች ይኖራሉ። ለሚዜነት የተተዉ ጓደኞች ሳይቀሩ ይመለመላሉ። እኔ በግሌ፣ ጓደኞቼን ሲያገቡ እንዳያስቸግሩኝ ከምጠይቃቸው ጉዳዮች አንዱ ለሚዜነት እንዳያጩኝ ነው - ካጩኝ ለተሻለ ቁምነገር ይጩኝ።

የሕዝብ መብት ነፋጊ ሙሽሮች

ዛሬ፣ ዛሬ በየአደባባዩ ቅድሚያ እየወሰዱ አደባባይ ሦስቴ የሚሽከረከሩ ሙሽሮች የከተማ ትራፊክ ሲያጨናንቁ ማንም አሌ አይላቸውም፣ እነሱም አይጨንቃቸውም። ከሁሉም ከሁሉም የሚያበሽቀው ግን ከተማውን ሁሉ በጡሩምባቸው መረበሻቸው ነው። የነሱ ሠርግ የከተሜው ሁሉ ጉዳይ ይመስል መንገደኛውን ሁሉ በጩኸት በመረበሽ ይዝናናሉ። በተለይ በዚህ ወር ቅዳሜና እሁድ አደባባይ አካባቢ ጥቂት ሰዓት መቆየት ያማርራል።

በአገራችን፣ በተለይም በከተሞች የተፋቺዎች ቁጥር ከተጋቢዎች ቁጥር ጥቂት ነው የሚያንሰው። ጥንዶች ሠርጋቸው እንዲያምር የሚከፍሉትን ያክል መስዋዕትነት ትዳራቸው እንዲሰምር ቢተጉ ኖሮ የፍቺ ቁጥር በእጅጉ ይቀንስ ነበር። መደምደሚያዬ ነው።

No comments:

Post a Comment