Pages

Wednesday, January 29, 2014

ዓይኔ ነው ላይኔ?



ባለፈው ሰሞንታምራት ላይኔ ታስሮ ከርቸሌ ሲገባ ያየው የደርጉ ለገሠ አስፋውዓይኔ ነው ላይኔ" አለ› የሚል የፌስቡክ ቀልድ ሰምቼ በሳቅ ፍርስ ብዬ ነበር። ዛሬ አመሻሽ ላይ ቤቴ እየገባሁ ሳለ የሰማሁት ነገር ደግሞ ለገሠን በቀልዱ ላይ እንደገረመው ዓይነት አስገረመኝ።

ልማቱ በተፋጠነበት፣ አስተዳደሩ ኮሽ በማይልበት" ~ ምን ነካው ቄሱ?

ሰፈሬየማርያም ጠበል" የሚባል አለ፤ የማርያም ቤተክርስትያን ታቦት ትላንት ጠበሉጋ መጥቶ ያድርና ዛሬ ይመለሳል። ስለዚህ መንገዴ በሰው ተጥለቅልቋል። ዘማሪዎችና ከነሱ በጎላ ድምፅ ሰባኪው ሲያስተምር በቅርብ ርቀት ከታቦት ማደሪያው አካባቢ ይሰማኛል። በመሐል የሆነ ቃል የሰማሁ መሰለኝ። ጆሮ ሰጠሁት፣ አዎ ደገመው። ስለልማት እያወራ ነው። ስለየቱ ልማት?

ልማቱ እንዲህ እየተፋጠነ እንዴት አልናገርም?" ብሎ ጠየቀ። የሚመልስለት አልነበረም፤ ሰባኪ ለነገሩ ይናገራል እንጂ አያዳምጥም። ከዚያ፣ ልማቱ በተፋጠነበት፣ አስተዳደሩ ኮሽ በማይልበት፣ አምልኮ በማይከለከልበት…" እያለ ቀጠለ፤ ንግግሩ እሱን ግምት ውስጥ ከመጣል በላይ ፋይዳ ያለው ግን አይመስልም።ተመልሼ የዚህን ሰው ድምፅ ልቅረፅ ይሆን ወይስ ይለፈኝ› እያልኩ ወደፊት ማዝገሜን ቀጠልኩ። በተዳጋጋሚልማት" የሚለው ቃል የሚጠቀስበት እና ተገንብቶ ያላለቀውባቡር" ሳይቀር ስሙ የተነሳበትስብከት" እየራቀኝ እየራቀኝ መጣ። ኋላ ላይ ያሳሰበኝ ደግሞሰባኪው ካድሬ ሆኖ ነው ወይስ ካድሬው ሰባኪ ሆኖየሚለው ነው። ዛሬ ጠዋት ደግሞ በድምፁ ሌላ ሰባኪ እንደሆነ የለየሁት ሰው ሃይማኖታዊ ብቻ የሆነ ነገር ሲናገር እየሰማሁ አለፍኩ። ሆኖም የማታው አልወጣልኝም።

በዚህ ዓይነት ኢሕአዴጉም፣ ካድሬቄሶቹም ከቀጠሉበት ከዛሬ 10 ዓመት በኋላ የሚኖረው ስብከት እንዲህ ሊሆን ይችላል፡-
እግዚአብሔር አዳምን ከፈጠረ በኋላአዳም ብቻውን መሆኑ ልማታዊ አይደለም፤ ስለዚህ ልማታዊት አጋር እንፍጠርለትብሎ ሔዋንን ፈጠራት።

ከዚያም ልማታዊ ዴሞክራሲ* ይተገበርባት በነበረችው በኤደን ገነት በተድላ እና ደስታ እንዲኖሩ ተፈቀደላቸው። ሆኖም አዳም እና ሔዋን የኒዮሊበራሊዝም አስተሳሰብ ተፀናውቷቸው አትብሉ የተባሉትን እፀበለስ እንደ ሳጥናኤል ባሉ የውጭ ኃይሎች ግፊት በመብላታቸው እና ቀዩዋን መሥመር በማለፋቸው ምድር ወደተባለ እስር ቤት ተጣሉ።

ይህ በሆነ በአምስተኛው ሺሕ አምስት መቶ ዓመቱ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ወደምድር በመላክ ልቡ በኒዮ-ሊበራሊዝም አስተሳሰብ የሸፈተውን አዳምን ሞቶ ወደገነት እንዲገባ መስዋዕትነት ከፈለለት፡፡ አዳምም ሰይጣን ከዚህ ጭንቅ ያወጣኛል፣ በፈጣሪ ላይ ጫና አድርጎ ያስፈታኛል ብዬ አምኜ በድፍረት ለፈፀምኩት ስህተት እግዚአብሔር ይቅር ይበለኝ ብሎ ለመነ፡፡

ሆኖም፣ አዳም መልሶ፣ መላልሶ ወደኒዮ-ሊበራሊዝም ፊቱን ማዞሩን አላቆመም ነበር፡፡ ስለሆነም እግዚአብሔር ሌላኛው ልጁን መሲሕ መለስ ዜናዊን ወደምድር ላከ፤ ቅዱስ መለስ ዜናዊም ስለዝቡ ደኅንነት በረሃ ለበረሃ እየተንከራተቱ ታንክ ተደግፈው መጽሐፍ አነበቡ፡፡ ከዚያም ለሕዝባቸው አብዮታዊ ዴሞክራሲን ሲያስተምሩ ኖረው ተሰዉ፡፡”

---
*
ልማታዊ ዴሞክራሲ ድኅረ መለስ ዜናዊ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ነው። ኢሕአዴግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ›ን በ‹ልማታዊ ዴሞክራሲ› መተካቱን ተከትሎ ኢሕአዴግ የሚለውም ኢሕለዴግ በሚል ቢተካ ጥሩ  እንደሆነ በጥምቀት በዓል ላይ የተገኙ አንዳንድ ምዕመናን ተናግረዋል። (በነገራችን ላይ፣ ‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ› በዚህ ወር ሕትመቱ ተቋርጧል፤ ‹ልማታዊ ዴሞክራሲ› ሆኖ ይመለስ ይሆን?)

No comments:

Post a Comment