Pages

Monday, July 25, 2011

በዻሳ ወይስ badhaasaa?

የብሔር ፖለቲካ በጣም ስስ (sensitive) ነው፡፡ በቀላሉ ተቆስቁሶ ብዙ ሊጓዝ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ በኢሕአዴግ ዘመን፣ በብሔር ፌዴራሊዝም ከተከፋፈለች ወዲህ እንኳን የብሔር ፍላጎቶችና ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ አላገኙም፡፡ የኦሮሞ ብሔረሰብ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ ከ34 በመቶ በላይ ድርሻ አለው፡፡ (2007 National Census) ሆኖም የኦሮሞ ሕዝብ ለዘመናት የሚገባውን ትኩረት የመነፈጉ ጉዳይ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ለሚሆን ጊዜ ሲያነታርክ ቆይቷል፡፡

የብሔር (በተለይም የኦሮሞ ተወላጆች) ፖለቲካ ጉዳይ የታገሉለትን ያሕል ብዙ መሻሽል ባያስመዘግብም፣ በርካታ አማራጮችን ለፖለቲካው የሚመግቡ ኢትዮጵያውያንን አፍርቷል፤ እነ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ እነ ቡልቻ ደመቅሳ እና እነ ዶ/ር መረራ ጉዲና የዚህ ትሩፋቶች ናቸው፡፡

ለነገሩ የዚህ ወጌ ቁምነገር የብሔር ፖለቲካ በጥቅሉ አይደለም፤ ነገር ግን ከብሔር ፖለቲካ ዘውግ ውስጥ አንዱን መዝዤ መሟገት ቃጥቶኛል፡፡ ጉዳዩ የተቀበረ ቢመስልም ለኔ ግን ገና አልሞተም፤ ልክ በኤርትራ መገንጠል ጉዳይ ላይ መቁረጥ እንዳልቻልኩት ሁሉ - በዚህም ገና አልቆረጥኩም፡፡

በነገራችን ላይ ኢሕአዴግ ‹‹በመቃብሩ ላይ›› ካልሆነ በቀር የማይቀይራቸው በርካታ ጉዳዮች መካከል ይመደባል የዛሬ ጉዳዬ፡፡ ለዚያ ነው ብዙዎቹ ኢትዮጵያዊ ምኞቶቼ እውን እንዲሆኑ ቶሎ የኢሕአዴግ መቃብር እንዲማስ ሌት ተቀን የምመኘው፡፡

አላግባብ ልብ ማንጠልጠሌን ልተወውና
እያወራሁ ያለሁት ስለኦሮሚኛ ቋንቋ ኦፊሴላዊ ፊደል መሆኑን ልንገራችሁ፡፡ አዎ፤ እንደሚታወቀው የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ኦፊሴላዊ ፊደል ላቲን ነው - ባጭሩ ግዕዝ አይደለም፡፡

ለመሆኑ የግዕዝ ፊደልንና ኦሮሚኛን ምን አቆራረጣቸው?
መልሱ በጣም ቀላል ነው፤ ስሜታዊነት! …………. በኦሮሞ የብሔር ፖለቲካ ውስጥ (በተለይም የኦነግ ሰዎች ዘንድ) ‹አቢሲኒያ› እና ‹ሐበሻ› የሚሉት ቃላቶች የጠላት ስያሜዎች ናቸው፡፡ ምናልባት ጉዳዩ የማይገባቸው ሰዎች ካሉ፣ ‹አቢሲኒያ› እና ‹ሐበሻ› የሚሉት ቃላቶች በይበልጥ የሚወክሉት የሰሜን ኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦችን ነው፡፡ የኦሮሞ ተወላጆች አቢሲኒያውያንን እንደ ቅኝ ገዢ (ዝቅ ሲል ደግሞ እንደ ጨቋኝ) ሕዝቦች ከታሪክ በመነሳት ይመድቧቸዋል፡፡ ይሄ አስተሳሰብ ታሪካዊ ድጋፍ ያገኘው በተለይ  የአፄ ቴዎድሮስን ዱካ ተከትለው አፄ ምኒልክ የኢትዮጵያን ግዛት ለማስፋፋትና ለማጠናከር በተንቀሳቀሱ ጊዜ የኦሮሚያን ክልሎች ‹‹ወርረዋል፣ ሕዝቡንም አፈናቅለዋል፣ የባርያ ንግድ ሰለባ አድርገዋል›› በሚል ነው፡፡

ከዚህ ታሪካዊ ቁርሾ በመነሳት የዘመናችን የኦሮሚያ ፖለቲከኞች በግዕዝ ፊደል መጠቀምን እንደሽንፈት በመቁጠር በላቲን ፊደል ለመጠቀም ከደነገጉ ሁለት አሥርት ዓመታት እየሞላቸው ነው፡፡ በዚህ ፅንሰ ሐሳብ ተቃራኒዎቹ ኦነግና ኦሕዴድም ይታረቃሉ፡፡ በርግጥ ጉዳዩን አምርረው የሚቃወሙ ሌሎች የኦሮሞ ፖለቲከኞችም አሉ::

የብልጫ ምርጫ
የኦሮሚኛ ቋንቋ ኦፊሴላዊ ፊደል የግዕዙ ፊደላት እንዲሆኑ ቢደረግ ቋንቋው የበለጠ ተጠቃሚ ይሆናል እንጂ አይከስርም፡፡ ለምሳሌ ያክል በርዕሴ ላይ የተጠቀምኩትን ‹‹በዻሳ›› የሚለውን ቃል እንውሰድ፡፡ (በነገራችን ላይ ‹‹በዻሳ›› ማለት 'ደስታ' እንደማለት ነው፡፡) በቃሉ ውስጥ ‹ዻ› የምትለዋ ቃል በ‹ጣ› እና ‹ዳ› መካከል የሚኖርን ድምጽ ትወክላለች፡፡ ይህንን ድምጽ እና ሌሎችም በርካታ (እንደ ቀ፣ ኘ፣ ዠ፣ ጠ፣ ጨ፣ ፀ እና ጰ ያሉ) ፊደሎችን በላቲን ፊደሎች ለመግለፅ ብዙ ድካም የሚጠይቅ ቢሆንም በግዕዙ ፊደላት ግን በቀላሉ ይቻላል፡፡

በመሰረቱ በእኛ አገር spelling bee (ወይም የስፔሊን ውድድር) የለም፡፡ የሌለበት ዋነኛው ምክንያት በግዕዝ የፊደል አጠቃቀም አንዴ ፊደላቱን አጥንቶ ለጨረሰ ሰው ቃላት አጻጻፍ በድጋሚ መማር ስለማይጠበቅበት ነው፡፡ ስለዚህ ኦሮሚኛን በላቲን ፊደላት ስንጽፍ የሚገጥመን የስፔሊንግ ማስተካከል ድካም ለምን ግዕዝን መግፋት አስፈለገ የሚል ጥያቄ ያጭራል፡፡

የግዕዝ ፊደላት ምርጫ የብልጫ እንጂ የፍላጎት ብቻ አይደለም፡፡

ከወገን ይሻል ባዳ?
የኦሮሞ ተወላጆች ጥያቄዎች ተገቢ መሆናቸው በአብዛኛው አያከራክርም፡፡ ይሁን እንጂ ‹‹በታሪክ ሰሜን ኢትዮጵያውያን ስለጨቆኑኝ፣ ‹ኢትዮጵያ የራሷ ፊደል ያላት ብቸኛዋ አፍሪካዊት አገር› የሚለው መለያዋ እኔን አይወክለኝም›› የሚል መከራከሪያ ግን አሸናፊ አያደርግም፡፡ ሁላችንም መቆርቆር ካለብን ስላለፈችው ኢትዮጵያ ሳይሆን ስለዛሬይቷ እና ስለነገይቱ ኢትዮጵያ መሆን እስካለበት ድረስ የብሔር ፖለቲካም ቢሆን የቁርሾ ፖለቲካ ሁኖ መቅረት የለበትም፡፡

ታሪክን ይዘን የምንሟገት ከሆነ፣ የሰሜኑ የኢትዮጵያ ሕዝብም (ገበሬውም) ቢሆን በአብዛኛው ከአቅሙ በላይ በመገበር እና የነገስታቱ አምላኪ ከመሆን በተሻገረ ተጠቃሚ ሁኖ አያውቅም፡፡ ስለዚህ ‹ጭቆና› የሚለው ቃል መተርጎም ያለበት ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንጂ ለኦሮሚያ ሕዝብ ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ይህም ሆኖ ቢሆን ግን - አንደኛ፤ የጭቆናው ዘመን ስላለፈና እንዲያልፍ እየታገልን ስለሆነ፣ ሁለተኛ፤ የባዕድ ሃገር (የላቲን) ፊደላትን በመጠቀም ከቅልውጥና በተሻገረ የራሴ ብሎ መጥራት መቼም ስለማይቻለን አሁንም የኦሮሚያ ክልል የግዕዝ ፊደልን እንዲጠቀም መታገል ይኖርብናል፡፡

(በነገራችን ላይ የሶማሊያ፣ የአፋር እና ሌሎችም ክልሎች የላቲን ፊደሎችን መጠቀማቸው ከኦሮሚያ ክልል የተለየ ትርጉም አይኖረውም፡፡)

No comments:

Post a Comment