Pages

Saturday, July 2, 2011

የመለስ ፖለቲካ እና የኢትዮጵያ አበሳ ባሳለፍነው 20 ዓመት

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያ መንግስት፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምናምን ማለት እየደበረኝ ነው፡፡ ምክንያቱም ለ20 ዓመታት ሲገዙ የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ የሁሉም ነገር ፈጣሪና ፈላጭ ቆራጭ ናቸው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ ከተባለ እኛንም ስለሚወክል፤ የመለስ ማለትን መርጫለሁ፡፡ “Power corrupts; absolute power corrupts absolutely” (ስልጣን ያበላሻል፤ ፍፁም ስልጣን ደግሞ ፈፅሞ ያበላሻል) እንዲሉ የአቶ መለስ ስልጣን እንዳበላሻቸው ከመናገር አልቆጠብም፡፡ አቶ መለስ ግን ተበላሽተው አልቀሩም ያበላሹት ብዙ ጉዳይም አለ፡፡ ለምሳሌ የሚከተሉት፡-



የኢትዮ-ኤርትራ ጉዳይ
አንድ አገር የነበሩት ኢትዮጵያና ኤርትራ በመለስ ድጋፍ ኤርትራ ስትገነጠል ሁለት ሆኑ፡፡ ወዲያውም በፍቅር ማሽቃበጥ ጀመሩ፡፡ ፍቅራቸው ግን ብዙ አልዘለቀም፤ ከሸፈ፡፡ ጦርነቱ የድሃዋን አገራችንን ብዙ ገንዘብና ብዙ ምስኪን ዜጎች ሕይወት ነጠቀ፡፡ ምን ዋጋ አለው? ተወረረብን የተባለውን መሬት በገንዘብና በደም ማስመለስ ለአቶ መለስ አልተቻላቸውም፡፡ የሔጉ ፍርድ ቤት ውሳኔ የመለስ ፖለቲካ አንዱ ውድቀት ነው፡፡
  
የጎሳ ፌዴራሊዝም  
የመለስ ፖለቲካ ያመጣው የጎሳ ፌዴራሊዝም መልካም ገጽታ የሚታየው በኢቴቪ ብቻ ነው፡፡ ከኢሕአዴግ ዘመን በኋላ ብሔር መጠያየቅ (ጠ ይጠብቃል) እና በብሔር ማሰብ ብርቅ አይደለም፡፡ ብሔር በመታወቂያ ላይ ሳይቀር የዜግነትን ቦታ ወስዷል፡፡ ትልልቅ የመንግስት ወንበሮችን የያዙት ሰዎች ብሔርም ዝነኛ እና የተለየ ክብር አለው፡፡ ወዘተርፈ፡፡ ከዚህ የዘር አስተሳሰብ አባዜ ተከትሎ ብዙ የጎሳ ግጭቶች ተቀስቅሰዋል፡፡ ለምሳሌ በጋምቤላ ክልል በተነሳ የጎሣ ግጭት በአንድ ቀን ብቻ 61 አኙዋኮች ተገድለዋል፡፡ በዚህ ግድያ የመንግስት እጅ እንዳለበት ዓለምአቀፍ ተሰሚነት ያላቸው የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች አረጋግጠዋል፤ ለምሳሌ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፡፡ የመለስ መንግስት ይህን አስተባብሏል፡፡

ድኅረ ምርጫ 97
ከምርጫ ዘጠና ሰባት በኋላ በተነሳው አመፅ ላይ የአቶ መለስ መንግስት ባመነው ብቻ 193 ሰዎች ተገድለዋል፡፡ የምርጫ 97ን ነገር ማስታወስ ለብዙዎቻችን የተዳፈነ ቁስል መቀስቀስ ነው፡፡ ግን አሁን ያን ዓይነት ዕድል ለመፍጠር በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ምክንያቱም የፖለቲካ ምሕዳሩ ጠቧል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የገዢው ፓርቲ አጫፋሪ ከመሆን የተሻገረ ዕድል አይሰጣቸውም፡፡ የተቃውሞ ሰልፍ ማድረግ በአዋጅ ሳይከለከል ተከልክሏል፡፡ መንግስትን በፅሁፍ መተቸት ራስን ለአደጋ ማጋለጥ ሁኗል፡፡ ይሄ ሁሉ መለስ አመጣሽ ፖለቲካ ነው፡፡ እነርሱ ታግለንለታል የሚሉት ስልጣንን የሕዝብ ማድረግ ዘበት ነው ብሏል ሕዝቡ፡፡ ለነገሩ የስልጣን ነገር እንኳን ለቀሪው ሕዝብ አብረው ለታገሉት ራሱ አይቀመሴ ሆኗል፡፡ አሁን ሕዝቡ ለውጥ በምርጫ እንደማይመጣ ታውቆት ለውጥ የሚመጣው በነውጥ እና በነፍጥ ነው የሚል ልባዊ አቋም ይዟል፡፡ የድኅረ ምርጫ 97 አሩር ውል እያለበት አይደፍርም እንጂ፡፡

እስር
ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ማሰር ለአቶ መለስ መንግስት ከባድ ጉዳይ አይደለም፡፡ ወ/ሪት ብርቱካን አቶ ስዬን እንዲፈቱ ፈርዳላቸው ስታበቃ እዚያው በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ራሷ ብርቱካን ታስራ በነበረችበት ወቅት በዘመድ አዝማድ የመጠየቅ መብቷን ተከራክራ ካስመሰከረች በኋላ ማረሚያ ቤቱ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በተግባር ሽሮታል፡፡ አሁን፣ አሁን ግን ፍርድ ቤቱ ራሱ የአቶ መለስ መንግስት ታዛዥ እንጂ የሕግ ተገዢ አይደለም፡፡ በየጊዜው የፖለቲካ እስረኞች በየእስር ቤቱ ይታጎራሉ፤ አንዳቸውም ግን የፖለቲካ እስረኛ እንዳልሆኑ የኢሕአዴግ ልሳን በሆነው ኢቴቪ ይነገራል፡፡ ሃገርን በመክዳት በሉት፤ በማሸበር፣ ለጥፋት በማነሳሳት የሚል ባጅ ይለጥፍባቸዋል፡፡የዚህና መሰል የመለስ ፖለቲካ ብዙዎችን ፖለቲካ በኢትዮጵያ ከኤሌክትሪክም የከፋ እንደሆነ እንዲያስቡ አድርጓቸዋል፡፡ ለምሳሌ እኔ በምፅፋቸው የተቃውሞ እና የብሶት ሐሳቦችን በመፍራት ሳይቀር የኔ የፌስቡክ ጓደኛ መሆን የማይፈልጉ ጓደኞች አሉኝ፤ አስተያየታቸውን ማስፈር የሚያሸብራቸውማ ብዙዎች ናቸው፡፡ እንዲያውም ብዙዎቹ እንዳልታሰር ከፈለግኩ አርፌ እንድቀመጥ ይመክሩኛል፡፡ ተቃውሞ ያሳስራል የሚል እምነት ነግሷል፡፡ በርግጥ በተግባርም እየታየ ነው፡፡

የኑሮ ውድነትን እና ረሃብን የማጥፋት ጉዳይ
መለስ የኢትዮጵያን ሕዝብ በቀን ሦስቴ እንደሚያበሉ ቃል ገብተው ነበር፡፡ አልተሳካም፡፡ የከተማውን ሕዝብ የኑሮ ውድነቱ የገጠሩን ሕዝብ ደግሞ ድርቅ ለረሃብ እያጋለጡት ነው፡፡ የኑሮ ውድነቱ በየዕለቱ እያደገ ነው፡፡ የሚራበው ሰው ቁጥር በየአመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር እንደሆነ መንግስታቸው አይክድም፡፡ ኢንዱስትሪውን ይመራል የተባለው ግብርና እስካሁን ከገበሬውና ከበሬው ጫንቃ ላይ አልወረደም፡፡ የኑሮ ውድነቱን ለመቆጣጠር የአቶ መለስ መንግስት የሚወስዳቸው ርምጃዎች ሁሉ እየወደቁ ነው፡፡ ይሄ ግን መንግስታቸውን ከጉሮሮአችን ሳይቀር እየነጠቀ ተእታ (VAT) ከመውሰድ አላገደውም፡፡

የአሸባሪነት ሕግ
የመለስ ፖለቲካ በኢሳያስ መንግስት ላይ መጨከን አይደፍርም፡፡ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅትም ቢሆን የስዬን አቋም ወስደው የራሳቸው እንዳደረጉት በተስፋዬ ገብረአብ ‹‹የደራሲው ማስታወሻ›› ላይ አንብበናል፡፡ የኢሳያስን መንግስት ለመገልበጥ ከየመን ወደቀይ ባሕር ሊሻገር የነበረ መሳሪያም እንዲያዝ ያደረጉት መለስ እንደሆኑ ሰምተናል፡፡ ይሄ የመለስ አቋም በሕወኀት አባላት ሳይቀር አስተችቷቸዋል፡፡ አሁን ደግሞ ‹‹አዲስ አበባን እንደባግዳድ›› ሊያሸብራት ነበር ያሉንን ሻዕቢያን በአሸባሪነት ዝርዝር ውስጥ ሳያካትቱ ደርሶብን የማያውቀውን አልቃይዳን የኢትዮጵያ አሸባሪዎች ብለው ፈረጇቸው፡፡ የፈለጉትን ይበሉ፤ የሆነ ሆኖ ከዚህ አሸባሪዎች ፍረጃ በኋላ እየተንገዳገደች የነበረችውን በፅሁፍ የመታገል መብት ረሽነው መቀመቅ አውርደዋታል፡፡ ይሄ በኔ ዕይታ የመለስ scandal ነው፡፡ ቅሌት ማለት ባማርኛ ይደብራል መሰል፡፡

No comments:

Post a Comment