Showing posts with label Entertainment. Show all posts
Showing posts with label Entertainment. Show all posts

Tuesday, February 25, 2014

ብዙአየሁ “የማ[ላ]ቃትን" ሴት አስናፈቀኝ

"የሚጣፍጥ ሕመም ስሜት ነው፣ ቅር የሚል ደስታ፣
ሙሉው ጎዶሎ ነው ትርጉሙ ትዝታ፤"
ወትሮም፣ እመንገዴ ላይ "ትዝታ" ሙዚቃ የተከፈተ እንደሆን ሁሉም ነገር ቅዝቅዝ፣ ፍዝዝ፣ ድንግዝ ይልብኛል። አረማመዴ፣ የጄ ውዝዋዜ፣ ሁለ ነገሬ ስክን ብሎ ልክ እንደ ዝግታ የተንቀሳቃሽ ምስል እንቅስቀሴ (slow motion) ይሆንብኛል።
"ከኔ አንጀት ይመስል፥ የተሰራው ክሩ
ይረበሻል ሆዴ፥ ሲገረፍ ክራሩ፤"
የላይኞቹን የግጥሙን [የሕዝብ?] ስንኞች ከመስማቴ በፊት የብዙአየሁ 2ተኛው ትራክ የሰጠኝ ስሜት ይህንኑ ነው። መጀመሪያ ላይ ያደመጥኩት ጠዋት፣ ጠዋት ማኪያቶ የምጠጣበት ካፌ ውስጥ ነበር። የዚህ ጽሑፍ ከፊሉ የተጻፈውም እዚያው ነው። ዲጄውም የኔ ዕጣ ሳይገጥመው አይቀርም፤ ይደጋግመዋል። አስተናገጋጆቹም አብረው እያዜሙ ያስተናግዳሉ። በኋላ ላይ ግን በየታክሲው ሁሉ አደምጠው ጀመር።

አሁን በዚሁ ዜማ የተሰየመው 'ሳላይሽ' የተሰኘው ሙሉ አልበም አለኝ፤ ነገር ግን ከዚህንኛው ዘፈን በቀር ትዝ የሚለኝ ሌላ ዘፈን የለም። እርግጥ ዘፈን ሳደምጥ የሆነ ሥራ እየሠራሁ ወይም የሆነ ዐሳብ እያሰብኩ ስለሚሆን ሙሉ ልቤን አልሰጠውም። ልክ እንደዚህኛው ልቤን የሚገዘግዘኝ  ካልመጣ በቀር የሰማሁት ምን እንደሆነ የማወቅ ዕድሉም ላይኖረኝ ይችላል።

ሙዚቃ ለኔ ስሜት ቆስቋሽ ከሆነ አሪፍ ሙዚቃ ነው ማለት ነው። የሚቀሰቅሰው ስሜት የምንም ይሁን፣ የምን በዜማው ሰው ማስቆዘምም ሆነ የሙድ ማፍታታት ማድረግ ከቻለ አለቀ! በእነሰርፀ ፍሬ ስብሐት ግምገማ ግን ከዚህ የተለየ ሊሆን ይችላል።…

ወደተነሳንበት ወግ ስንመለስ ብዙአየሁ እንዲህ ይላል፦
"ተስለሻል እንዴ ባይኔ በመሐሉ፣
አንቺ ብቻ እኮ ነሽ በሚታየኝ ሁሉ፤"
ዓይኔን ጨፍኜ ትታየኛለች እንዴ ብዬ ሳስብ አትታየኝም። ከዚያ ዘፈኑን የወደድኩት በዜማው ውበት እንጂ በገዛ ትዝታዬ አይደለም ብዬ አልኩ፤ ጥያቄው ግን "ትታየኛለች/አትታየኝም" ብዬ ያልኳት በስመ ፆታ ሔዋን ነው ወይስ…? ከዚህ ጥያቄ በኋላ ነው የዚችን ጽሑፍ ርዕስ "የማላውቃትን" ካልኩት በኋላ 'ቃ'ን ለይቼ በሳጥን ቅንፍ ውስጥ ያሰርኳት፤ ብትወጣም ስህተት የለውም እንደማለት።

ግጥም ያለው ዜማ ስንሰማ የምንወደው ግጥሙን ነው ዜማውን የሚለው ጥያቄ ሁሌም እንደፈተነኝ ነው። ብዙ ጊዜ ራሴን፣ ከዘፈን ግጥሞች ጋር አቆራኝቼ አገኘዋለሁ። ለምሳሌ የአብዱ ኪያርን ዜማዎች የምወዳቸው በግጥሞቹ ነው። ግን ደግሞ መልሼ ግጥሞቹን ያለዜማ ስሰማቸው ጣዕም አልባ ይሆኑብኛል። ስለዚህ ዜማ የሚወደደው ከግጥሙ ተጣምሮ ነው ወደሚለው ድምዳሜ ያጠጋጋኛል።
ሙዚቃ በጥቅሉ ባይኖር ኖሮ ዓለማችን የተለየ ማኅበራዊ ገጽታ ይኖራት ነበር ብዬ አምናለሁ። ገጽታው ምን ዓይነት ሊሆን እንደሚችል አልገምትም፤ እኔ ግን የምወደው ዓይነት የሚሆን አይመስለኝም። 

ትዝታ ግን አሁንም ይለያል። ትዝታን የኢትዮጵያውያን typical መለያ አድርጌ እወስደው ነበር። ያለፈ ነገር እንወዳለን። ዛሬ የፈለገ ቢሻል እንኳ "የዛሬን አያርገውና…" ማለታችን አይቀርም፤ "ድሮ ቀረ" ከአፋችን አይጠፋም። ከዛሬ ይልቅ የድሮው ትዝታ ይመስጠናል፣ ልጆቻችንን ዘመናዊ ዥዋዥዌ እያጫወትን የራሳችን የአፈር ሸርተቴ ይናፍቀናል። ተረስቶ እንዲቀር አንፈልግም። የትዝታ ዜማ ነገር ግን አሁንም ይለያል። ሌሎቹ ዓለማት ባይኖራቸው እንጂ ቢኖራቸው ኖሮ እንደሚወዱት አያጠራጥርም። በተለይ ጎልማሳ ለሆነ ሰው፣ ትዝታ ፍቱን መድኃኒት ነው። እንደኛ ሕመሞቹን ያለ ምንም ሥነልቦናዊ ዕርዳታ ለሚያክም ሰው፣ የትዝታ ዜማ ከሙድ አራቂነትም በላይ ነው። ለዚህም ነው የትዝታ ንጉሡ ማሕሙድ 'መዝገበ ቃላቱ ትዝታ ባይኖር ኖሮ የፍቅር ዕድሜው ያጥር ነበር' ያለን በዜማው።

በቃ የብዙአየሁ ዜማ ማለት ከላይ የቀባጠርኩትን ሁሉ የሚያስቀባጥር ነው።

Thursday, January 9, 2014

“ገዳይ ሲያረፋፍድ፣ ሟች ይገሰግሳል!”

የማላየው የአማርኛ ፊልም የለም፣ ሁሉንም እያየሁ መበሳጨት ልምዴ ነው፡፡ ሁሉንም አይቼ ‹ቂም› እያጠራቀምኩ በአደባባይ የተሳደብኩበትም ጊዜ እንዲሁ ብዙ ነው፡፡ ‹‹ገዳይ ሲያረፋፍድ›› የሚለውን ፊልም ገና ከመውጣቱ በፊት ወድጄው ነበር፤ በሁለት ምክንያት - አንድም በርዕሱ፣ አንድም በፖስተሩ፡፡ የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል ሆኖ ነው መሰለኝ ፊልሙም ተነስተው የሚያጨበጭቡለት ዓይነት ነው፡፡ ስለፊልሙ ለመጻፍ የተነሳሳሁባቸው ሁለት ምክንያቶች ናቸው፡፡ አንደኛው የሚያበሳጩኝን ፊልሞች ስሳደብ ከርሜ የሚያስደስተኝን ለማሞገስ ምላስ ሲያጥረኝ ራሴን ስለታዘብኩት ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት በቀደም ዕለት ዮፍታሔ ሲኒማ አካባቢ ሁለት ወጣቶች ሲያወሩ የሰማኋቸው ስላናደደኝ ነው፡፡


አንዱ፤ ‹ገዳይ ሲያረፋፍድ›ን እንዳታየው፣
ሌላው፤ ለምን?
አንዱ፤ ያስጠላል፡፡

እኔ በማላውቃቸው ሰዎች ጣልቃ ገብቼ፤ ‹አይተኸዋል?› አልኩት ‹አንዱ› በማለት የተገለጸውን አንዱን፡፡

አንዱ፤ ‹አላየሁትም፤ ግን ሰዎች ማስታወቂያውን አይተው አስጥንቅቀውኛል…›

እንግዲህ ይታያችሁ፤ እሱ ራሱ እንኳን ማስታወቂያውን አላየውም፡፡ የአገራችንን ፊልሞች እንደኔ ለትዝብት ብቻ ለማየት ላልቆረጠ ሰው፣ እየተጠቋቆሙ ማየት የተለመደ ነው፡፡ የዚህ ዓይነቱ ጥቆማ ግን ከደረጃ በታች ነው፡፡ ስለዚህ እኔ ሁለቴ ያየሁት ሰውዬ ብመሰክር ይሻላል፡፡ ለልጆቹ የሰጠኋቸው መልስ ‹‹አንደኛ ነው፤ እዩት›› የሚል ነበር፡፡ የቻልኩትን ያክል ለማጋነን ፈልጌ ነበር፡፡ ግን የምሬን ነው፡፡

‹ገዳይ ሲያረፋፍድ› በጣና ኢንተርቴይመንት የቀረበ የናኦድ ለማ ፊልም ነው፤ በፊልሙ ላይ የከተማ ገጽታ ብቻ ሳይሆን የሰለቸናቸውን የከተማ ተዋናዮችንም አናያቸውም፡፡ ፊልሙን ለመውደድ ያበቃኝም አንዱ ይኸው እርምጃው ነው፡፡ ብዙኃኑ የማያውቀውን የከተማ ባለፀጎች ሕይወት ከሚያስኮመኩሙ የፍቅር ኮሜዲዎች በአንዴ ዘሎ ወደገጠር መቼት፡፡ ደፋር ደግሞም የተዋጣለት እርምጃ ነበር፡፡

ፊልሙ ውስጥ እያንዳንዱ ገፀ-ባሕሪ የየራሱን ሚና ድንቅ አድርጎ ከመጫወቱም በተጨማሪ ዳይሬክተሩ ለእያንዳንዷ ዝርዝር እንቅስቃሴ የሰጠበት ሁኔታ ውጤታማ አድርጎታል፡፡ የገጠር ሕይወት እውቀት ለሌለው መማሪያ፣ ላለው ደግሞ ትዝታ ይሰጣል፡፡ የሴቶች እና የወንዶች የገገጠር ቤት፣ መስክ ውስጥ ሚና፤ ማኅበራዊ አኗኗሩ፣ እምነቱ፣ ወዘተርፈው በጥንቃቄ የሚገለጽበት ፊልም ነው፡፡

ጠቅላላ ታሪኩ አገር ባስቸገረ ሽፍታ ላይ የሚያተኩር ነው፡፡ ሽፍታው ቅምጥ አለችው፤ ቅምጡን ሊቀላውጥ የከጀለ አንድ ገበሬ ከሽፍታው ጋር የሚፋጠጥበት ታሪክ ነው፡፡ በትወናው ላይ የአገሬው ሰዎች ተሳትፈውበታል፡፡ ከአነጋገራቸው ጀምሮ መላ አኗኗራቸውን በአንድ ሰዓት ተኩል እጥር፣ ምጥን፣ ጥፍጥ አድርጎ ያቀርበዋል፡፡

መጀመሪያ ላይ እንደገለጽኩት፤ ገና ፊልሙን ሳላየው በፊት ርዕሱን ወድጄው ነበር፡፡ ርዕሱን ግን የወደድኩት፣ በሌላ እሳቤ ነበር፡፡ ‹ገዳይ ሲያረፋፍድ የቀረ ይመስላል› በሚል የራሴ መደምደሚያ ሰጥቼው፡፡ ነገርዬው ከራሴ ጋር በተገጣጠመ ነው፡፡ የማኅበራዊ አውታር የመንግሥት ተቺ እንደመሆኔ ጓደኞቼ ‹ዶሮ አስረዝመው ሲያስሯት የፈቷት ይመስላል› እያሉ ይቀልዱብኛል፡፡ መንግሥታችን የተበሳ ጨ ዕለት ጉድህ ፈላ እንደማለት፡፡ ልክ በዚያ ስሜት ነበር እኔም ርዕሱን የወደድኩት፤ ፊልሙ ግን በሚከተለው ሀገራዊ ዜማ ላይ ተመስርቶ ነው የተሰየመው፤ እዩትና ትወዱታላችሁ፡፡

‹‹ገዳይ ሲያረፋፍድ ሟች ይገሰግሳል፣
አንዱም የመሞቻው፣ አንዱም መሰደጃው ደርሷል፡፡›› (ግጥሙን ተሳስቼ ሊሆን ይችላል)

Sunday, April 15, 2012

የቴዲ አፍሮን አልበም ያልገዛሁባቸው 5 ምክንያቶች


ባለፈው ሳምንት የቴዲ አፍሮን አልበም እንድንገዛ የሚያስገድዱንን 5 ምክንያቶች አንብቤ ነበር፤ አላሳመኑኝም እንጂ! ስለዚህ አልገዛሁም፡፡ ባልገዛም አዳምጬዋለሁ፡፡ በርግጥ ሳይወጣ በፊት ላለመግዛት መወሰኔ በራሱ፣ ከወጣ በኋላ ለምን አልገዛሁትም ብዬ የምናገረው ነገር ሰሚን ላይማርክ ይችላል ግን ምንአገባኝ፡፡ ግን ምናልባት ‹ገንዘብ ቸግሮት የቴዲን አልበም አልገዛም› ብለው የሚያሙኝን ሰዎች ዝም ለማሰኘት ምክንያቴን እደረድራለሁ፡፡ (በነገራችን ላይ ትላንት ከኢትዮፒካሊንክ እንደሰማሁት÷ ያቺ እንኳን የፕሬዚደንት ግርማ ወልደጊዮርገስን የሕይወት ታሪክ በዶኩመንተሪ እሰራለሁ ስትል የነበረችው አምለሰት ሙጪ ስንት ሳዱላዎች የተጋደሉለትን ቴዲን በእጇ አደረገችው ማለት ነው በቃ?)

ፌሚኒዝም በኢትዮጵያ፦ የሚታደሉት ወይስ የሚታገሉት?

​( በፍቃዱ ኃይሉ ) ​ " እውነቱን ለመናገር፣ ከፌሚኒዝም ታሪክ ጋር የምጋራቸውም ሆነ የማልስማማባቸው ነጥቦች አሉኝ፤ [ ነገር ግን ] የሌለኝን ማዕረግ ወስጄ ራሴን [ ፌሚኒስት በሚ...