(በፍቃዱ ኃይሉ)
"እውነቱን ለመናገር፣ ከፌሚኒዝም ታሪክ ጋር የምጋራቸውም ሆነ የማልስማማባቸው ነጥቦች አሉኝ፤ [ነገር ግን] የሌለኝን ማዕረግ ወስጄ ራሴን [ፌሚኒስት በሚል ሥም] ለማቆላመጥ አልፈልግም።" (የጀርመን የመጀመሪያዋ ሴት ቻንስለር አንጌላ መርኬል፣ እኤአ በ2017 በበርሊን Women20 Summit ላይ “ፌሚኒስት ነዎት ወይ?” ተብለው ሲጠየቁ የሰጡት መልስ።)
"ያኔ ስናገረው ትንሽ እየፈራሁ ነበር። አሁን ግን በደንብ አስቤበታለሁ፤ በዚህ መልኩ ሲታይ ሁላችንም ፌሚኒስቶች መሆን አለብን ማለት እችላለሁ።" (አንጌላ መርኬል እኤአ በ2021 "ሁላችንም ፌሚኒስት መሆን አለብን" በሚለው ንግግሯ/መጽሐፏ የምትታወቀው ናይጄሪያዊት ቺማማንዳ አዲቼ የተሳተፈችበት መድረክ ላይ ተመሳሳይ ጥያቄ ተጠይቀው የሰጡት ምላሽ።)
ፌሚኒዝም በኢትዮጵያ ውስጥ መጠነ-ሰፊ ማኅበራዊ ተፅዕኖ ማሳደር የመጀመሩን ያክል፣ የተቀናጀ የሚመስል ፅኑ ተቃውሞ እና ፍረጃም እየገጠመው ነው።
ነገር ግን በፌሚኒዝም ላይ የሚሰነዘሩ ነቀፌታዎች አዲስም፣ አገር በቀልም አይደሉም። ንቅናቄው ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ በየደረሰበት ማኅበረሰብ እና በየዘመኑ እየተፈተነ፣ እየወደቀና እየተነሳ እዚህ የደረሰ ኅያው ሞገድ ነው። እንዲያውም የሚገርመው፣ ፌሚኒዝምን በመተቸትና ድክመቱን በማጋለጥ ረገድ ከራሳቸው ከፌሚኒስቶቹ የከረረ ሂስ ያቀረበ ሌላ አካል የለም። የንቅናቄው ትልቁ ጥንካሬም ራሱን ከትችት በላይ አድርጎ ባለማኖሩ፣ ሁሌም ራሱን በመፈተሽ መታደስና ማደግ መቻሉ ነው።
ትርጉም፣ ሞገዶች እና የንድፈ-ሐሳብ ልዩነቶች
ፊሚኒስቶች ሁሉ አንድ ዓይነት የችግር አረዳድ፣ የመፍትሔ መንገድ እና የውጤት ዒላማ የላቸውም። ለዚህም ነው አንዳንድ ፌሚኒስቶች “ሊበራል ፊሚኒስት”፣ “ማርክሲስት ፌሚኒስት”፣ “ኢንተርሴክሽናል ፌሚኒስት”፣ “ክርስቲያን/ሙስሊም ፌሚኒስት” ሲሉ የምንሰማቸው። አንዳንዶቹ በአባውራ የሚመራው ቤተሰብ “የጭቆና መሸሸጊያ ነውና ይፍረስ” (abolitionists) ሲሉ፣ ሌሎቹ ደግሞ “የለም፣ ይታደስ” (reformists) ይላሉ።