Pages

Thursday, November 2, 2017

ማነው አሳሪ? ማነው ፈቺ?

አግባብ ያልሆኑ እስሮች፣ ያልተጠበቁ ፍቺዎች እና የማይታመኑ የፍቺ ክልከላዎች ደጋግመው ቢከሰቱም ሁሌ እንደ አዲስ የሚያወያዩን አጀንዳዎች ናቸው። ኦቦ በቀለ ገርባ የታሰሩት የኦሮሞ ሕዝብን ጥያቄ ያለ ፍርሐት ስላስተጋቡ ብቻ ነው። ይህን የምለው ለይስሙላ አይደለም፤ የፌዴራል ዐቃቤ ሕግ ያቀረበባቸውን ማስረጃ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ አራተኛ ወንጀል ችሎት ተገኝቼ አድምጬያለሁ። ችሎቱ ክሳቸውን ከሽብር ወደ 'በንግግር አመፅ ማነሳሳት' (የወንጀል ሕጉ አንቀፅ 257/ሀ) ዝቅ ሲያደርገው ዋስትና እንደሚያሰጣቸው ግልጽ ነበር። ችሎቱ በዋስትና ጉዳይ ውሳኔ ለመስጠት ከአንድ ቀጠሮ በላይ ሲወስድ አይቼ አላውቅም። እርሳቸውን ግን ደጋግሞ ቀጠሮ ሲሰጣቸው፣ ዳኞች ዋስትናውን መከልከልም ሆነ መፍቀድ የፈሩ ይመስል ነበር። በመጨረሻ የሞት ሞታቸውን ከለከሏቸው እና አረፉ። ይግባኝ ተባለ፣ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ30 ሺሕ ብር የስር ፍርድ ቤት የከለከለውን ፈቀደ። ቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ ቤት እስረኛውን በመፍታት ፈንታ ደብዳቤው ላይ የተጻፈው ቁጥር አደናገረኝ በሚል ሰበብ ሁለት ቀን አሳደራቸው። በመሐል ፋና ሬዲዮ የኦቦ በቀለ ፍቺ በዐቃቤ ሕግ ይግባኝ ባይነት፣ በሰበር ሰሚ ችሎት ታገደ የሚል ዜና ይዞ ወጣ። Déjà vu. 

ሐምሌ ወር 2007፣ በእነዘላለም ወርቅአገኘሁ መዝገብ ሀብታሙ አያሌው፣ አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ዳንኤል ሺበሺ እና አብርሃም ሰለሞን ነጻ ከተባሉ በኋላ የተከሰተው ይሄንኑ ይመስል ነበር። ቤተሰቦቻቸው ሲፈቱ ለመቀበል ቂሊንጦ በር ላይ ሲመላለሱ፣ ማረሚያ ቤቱ ሰበብ ሲፈጥር አቆያቸው፤ በመሐል፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፍቺያቸውን እንዳገደው ተሰማ። ከዚያ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ በዞን ዘጠኝ ጉዳይ ከታሰሩት አምስቱ ድንገት ስማቸው ተጠርቶ ከቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ ቤት ተጠርተው ውጡ ተብለው ነበር። ለቀሪዎቹም ሆነ ለወጪዎቹ በጣም አስደንጋጭ ገጠመኝ ነበር። ዐቃቤ ሕግ የነዚህን አምስቱን ክስ አንስቷል ተባለ። ከሁለት ሳምንት በኋላ ቀሪዎቻችን ፍርድ ቤት ቀረብን፣ ያኔ "ተከላከሉ ወይም በነጻ ተሰናበቱ" መባል ነበረብን። ቀጠሮ ተሰጠን፣ ተደገምን፣ 5 ጊዜ። ጥቅምት የሞት ሞታቸውን ቀሪዎቻችን ፈቱን። የነ ሀብታሙ ጉዳይ በጠበቃቸው ይግባኝ ባይነት ዓመት ያክል ተንዘላዝሎ፣ እነርሱም ተፈቱ። 

ማነው አሳሪ?

ለዚህ ጥያቄ እርግጠኛ መልስ ማግኘት ይከብዳል። ከልምድ ግን መገመት ይቻላል። እኔና ጓደኞቼ ማዕከላዊ በነበርንበት ጊዜ ማዕከላዊ የነበሩት (በቁጥጥር ሥር ያዋሉን) መርማሪ ፖሊሶች ስለኛ የሚያውቁት ጥቂት ነገር ነበር። ወረቀታቸውን እያገላበጡ ሲጠይቁን፣ የሆነ ከጀርባቸው ያለ ሰው እነዚህን ጥያቄዎች ጠይቋቸው ብሎ እንደላካቸው ያስታውቅባቸው ነበር። በሰጠናቸው መልሶች የረኩ መስለው ከሔዱ በኋላ፣ እሳት ለብሰው እሳት ጎርሰው ይመለሳሉ። መልሳችን የላኳቸውን ሰዎች አላረካም ማለት ነው። ይሔ ነገር ለኔ ያመላከተኝ ቢኖር ከኋላቸው አለቆቻቸው መኖራቸውን ሳይሆን፣ የአለቆቻቸውም አለቆች መኖራቸውን ነው። በኔ ግምት 'የመረጃ እና ደኅንነት ቢሮ' (ደኅንነቶች) ከሁሉም የሽብር ነክ እስሮች ጀርባ ናቸው። 

ጠበቆች አዲስ ክሶች በተመሠረቱ ቁጥር 'የሕግ ባለሙያ እንዴት እንዲህ ዓይነት ክስ ያዘጋጃል?' እያሉ ይገረማሉ። ዐቃቤ ሕጎች፣ ለችሎት 'ክሱን አላየሁትም አሁን ነው የደረሰኝ' ሲሉ ሰምቼ አውቃለሁ። የሚሰጡት ሰበብ 'ዐቃቤ ሕግ ተቋም ነው፤ አንዱ ያዘጋጀውን ክስ ሌላው ያስቀጥለዋል' የሚል ቢሆንም አያሳምነኝም። የሽብር ክሶቹን የሚጽፋቸው ረዥም እጅ ያለ ይመስለኛል - ይኸውም ሊሆን የሚችለው የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ብቻ ነው። 

የዳኞች መለማመድ

የሽብር ችሎትን መዳኘት ሕሊና ላለው የሚያሰቃይ ነገር ነው። አብዛኞቹ ተከሳሾች የአሰቃቂ ጥቃት ሰለባ ናቸው። ያንንም ሰሚ ባገኝ በሚል ተስፋ በችሎት ይተነፍሱታል። ክሱ ዝርክርክ ነው። ማስረጃዎቹ አይረቡም። ተከሳሾቹ በችሎቱ ነጻነት አያምኑም። ዳኞቹ በተለያዩ ጊዜዎች የተለያዩ ስሜቶችን ሲያስተናግዱ ይቆዩና ወደኋላ ላይ የተከሳሾቹን ሕመም መረዳት፣ ማባበል፣ ለውሳኔያቸው ረዥም ማብራሪያ መስጠት እና ፈራ ተባ እያሉ አንዳንድ እስረኞችን መፍታት ይጀምራሉ። ወዲያው ግን ይቀየራሉ።  የሽብር ችሎቶች ዳኞች በጣም ቶሎ፣ ቶሎ ከመቀያየራቸው የተነሳ አንዱ የጀመረውን ጉዳይ ሌላ የመጨረሱ ዕድል ሰፊ ነው። 

በገዢዎቻችን እና በዳኞች መካከል ያለውን ግንኙነት ከውጭ ምልከታ ለመመዘን ሞክሬያለሁ። በቀጥታ 'እከሌን ይሄን ያክል ፍረድበት፣ እከሌን ፍታው' የሚባሉ አይመስለኝም። ነገር ግን ዳኞቹ ሲሾሙ መጀመሪያ ለስርዓቱ ያላቸው ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ መግባት የለበትም። አንዳንዶቹ ለገዢው ቡድን ጥብቅና ይሰማቸዋል። በዚያ ላይ ሹመቶች አሉ። በታማኝነታቸው ልክ ነው ቀደምቶቹ የተሾሙት።  በሌላ በኩል፣ በተለይ በሽብር ጉዳይ፣ ተከሳሾች የሚመሠረትባቸው የክስ አንቀፅ በራሱ መልዕክት ነው። አሳሪው ተከሳሹን ምን ያህል ማሰር እንደሚፈልግ በክሱ ያመለክታል። በዚያ ላይ የግል ፍርሐታቸው አለ፤ 'መንግሥት በዚህ የጠረጠረውን እኔ እንዴት ማስረጃ የለም ብዬ እፈታዋለሁ?' ከዚያም ውጪ ምናልባት በውስጥ ስብሰባቸው ላይ 'ጉዳዩ ሲሪዬስ ነው' ይባሉ ይሆናል። ለዚህም ይመስለኛል፣ ዳኞች ከእስረኞቹ ጋር ሲለማመዱ፣ ሐዘኔታ ሲሰማቸው፣ መተዋወቅ ጥርጣሬያቸውን እያጠፋ የመፍታት ድፍረታቸው ሲጨምር አስተዳደሩ የሚፐውዛቸው። አሁን ለምሳሌ የአራተኛው ወንጀል ችሎት ሦስቱም ዳኞቹ ከዚህ ወር ጀምሮ ተቀይረዋል። የ19ኛው ችሎት ዳኞችም በቅርቡ ተቀያይረዋል።

ከዚያ ውጪ ያለው ጫወታ በዐቃቤ ሕግ ሥም ነው። ሲያሻቸው ክሱን ያከብዱታል፤ ሲያሻቸው ያቀሉታል። ሲያሻቸው ክሱን ያቋርጡታል። ሲያሻቸው ምስክሮችን በማፈላለግ ሥም የችሎቱን መደመጥ (እስኞቹ ወኅኒ ተጥለው) ያራዝሙታል (ለዚህ ተባባሪያቸው ምስክሮቹን ማቅረብ ያለበት ፖሊስ ነው)። ሲያሻቸው ፍቺውን በይግባኝ ያሳግዱታል (ለዚህ ደግሞ ተባባሪዎቻቸው የማረሚያ ቤት አስተዳደሮች ናቸው)። 

ማረሚያ ቤቶች ውስጥ የፍቺ ወረቀት መጥቶለት እንዲቆይ የሚፈልጉት ሰው ላይ ሰበብ ይፈጥራሉ። ማረሚያ ቤቶች ውስጥ "ደኅንነት" የሚባሉ ሠራተኞች አሉ። የሥራ ድርሻቸው ምን እንደሆነ አይታወቅም፤ ግን ፈላጭ ቆራጭ ናቸው። እንደሚመስለኝ፣ ዐቃቤ ሕጎች ይግባኝ እንዲሉ (ደኅንነት መሥሪያ ቤቱ) ሲወስን፣ በቀጥታ ለማረሚያ ቤቶቹ የደኅንነት ሠራተኞች፣ እስረኞቹ በሰበብ እንዲቆዩ ትዕዛዝ ይሰጧቸዋል። በዚህ ግዜ ከላይ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ይፈፀማል። ዐቃቤ ሕጎች ይህንን በራሳቸው አይፈፅሙትም ብዬ የምገምተው በምክንያት ነው። አብዛኛዎቹ ወጣቶች ናቸው። ካልታዘዙ በቀር በሥራው ላይ እስከ ይግባኝ ለመሔድ የተዘጋጀ ምንም የሥራ መነቃቃት አይታይባቸውም። እንዲሁ ሥራ አጥተው የገቡ ስልቹዎች ናቸው። ብዙውን ክስ አያውቁትም፤ እንዲያውም ችሎት ውስጥ ሲነበብ ከታዳሚው ጋር እየሰሙ የትየባ ስህተት ገጥሞ እንዲያርሙት ሲጠየቁ ግራ ይጋባሉ።

ታዲያ ማነው ፈቺ?

ድንገት ክሳቸው ተቋርጦ የተፈቱ ሰዎች፤ የሞት ፍርድ፣ የ22 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው በ6 ወይም በ3 ዓመታቸው የተፈቱ ሰዎች አሉ። ይቅርታ ጠይቀው ያልተፈቱ አሉ፤ ይቅርታ ጠይቀው የተፈቱ አሉ። ይቅርታ ሳይጠይቁ የተፈቱ አሉ። መታሰራቸውም አግባብ ስላልነበር፣ መፈታታቸው ብዙዎቻችንን ያስደስተናል። ግን ማነው የሚፈታቸው? በምን መመዘኛ?  የማረሚያ ቤቱ ሥልጣን፣ ከፍርድ ቤቱ ይለያል። ነገር ግን ፍርድ ቤት "የእስረኞችን መብት አትጣስ" ሲባል ጆሮ ዳባ ልበስ የሚለው እና ባለፈው ዓመት የአራተኛው ወንጀል ችሎት ዳኞች "እኛን አትሰሙንም" ብለው ያማረሩት ማረሚያ ቤት ሥልጣን አለው እንዳይባል፤ የለውም። በቀድሞ ታጋዮች የሚመራው ማረሚያ ቤት ለሽብር እስረኞች ከፍተኛ ጥላቻ አለው። ሥልጣን ቢኖረው ስንቶቹ የሙስና እስረኞች (ከቀድሞ ታጋዮችም አሉበት) ለአስተዳደሮቹ በሚሰጡት መደለያ ብዛት ቀዳሚው ተፈቺ ይሆኑ ነበር። ስለዚህ ፈቺ አሁንም የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ነው። መፈታትም የነጻነት፣ ወይም የእስር ዘመንን ማረጋገጫ ሳይሆን የፖለቲካ ጫወታ ነው። አንዳንዴ እየከፋፈሉ እያሰሩ፣ እየከፋፈሉ መፍታት። ሌላ ግዜ ስጋት የሆነውን አቆይቶ፣ ስጋት ያልሆነውን  በመፍታት መደለል። ሌላም፣ ሌላም…

ከዚህ ውጪ ያለው ግምት ብዙም አይስማማኝም። ምክንያቱም፣ አሳሪም የደኅንነቱ ቢሮ፣ ፈቺውም የደኅንነት ቢሮ።

No comments:

Post a Comment