Pages

Friday, October 4, 2013

የታክሲዎች የጨረባ ተስካር እና የኔ ብስጭቶች

ጉዳዩ ‘ሲሪዬስ’ ነው፤ በተለይ በአዲስ አበባ። ግን ማንም ደንታ የሰጠው አይመስልም። ዘርፈ ብዙ የትራንስፖርት አገልግሎት ችግሮች በምሬታችን ላይ ምሬት እየጨመሩ ነው። ኪሳራውን ግን እስካሁን አላሰላነውም። ለምን ይህን ጽሑፍ ከአንዲት ወዳጄጋ ሰሞኑን በሰራነው ግምታዊ (ወይም ግብታዊ) ስሌት አንጀምረውም።

አዲስ አበባ ውስጥ ቢያንስ አንድ ሚሊዮን ሠራተኞች አሉ። ከዚያ ውስጥ በቃ 50ሺሕዎቹ ብቻ በትራንስፖርት ችግር አንድ ሰዓት አረፈዱ እንበል፤ 50ሺሕ የሥራ ሰዓት ባከነ ማለት አይደለም? በቀኑ የሥራ ሰዓት 8 ስናካፍለው  በድምሩ በየቀኑ 6,250 ሰው ከሥራው እንደቀረ (ወይም 6,250 የሥራ ቀናት እንደባከኑ) መቁጠር ይቻላል። በዓመት አስሉትማ!

ዛሬን እየኖሩ ስለነገ ስርዓት መያዝ መጨነቅ ይቻላል?

እኛ ሰፈር ጠዋት፣ ጠዋት ከወትሮው የከፋ የታክሲ እጥረትና ትርምስ ካለ፥ ትራፊክ ፖሊስ በአካባቢው አለ ማለት ነው። ታክሲዎቹ ትርፍ ሰው የሚጭኑት ትራፊክ ፖሊስ ሳይኖር ብቻ በመሆኑ የሥራ ሰዓት እና ቀጠሮ የረፈደበት ሰው ትራፊክ  ፖሊሶቹን ሲያይ እንደስርዓት አስከባሪ ሳይሆን እንደ ችግር ፈጣሪ ባይመለከታቸው ይገርማል።

ጠዋትና ማታ (የሥራ መውጫና መግቢያ ሰዓቶች ላይ) የትራንስፖርት አማራጮቹ አቅም ከትራንስፖርት ፈላጊዎቹ ቁጥርጋ አይጣጣምም። ስለዚህ ምንም እንኳን ለትራንስፖርት ዘርፉ ስርዓት መያዝ ሲባል የትራፊክ ሕግጋቱን ማክበር አስፈላጊ ቢሆንም ዛሬን ለመኖር ሲባል አገልግሎት  ጪዎቹም ሆኑ ተገልጋዮቹ ተባብረው ስርዓቱን ይጥሳሉ። ስርዓቱን የመጣሱ ነገር ወደባሕልነት ሊያድግ የሚችል  መሆኑ አሁን የሚያስጨንቀው ሰው የለም።

“200 ሺሕ ብር ያለው ሰው የሚያሾረው ኢንደስትሪ"

አንድ እሁድ ከምሽቱ 2:30 ላይ ቦሌ ቆሜ የአራት ኪሎ ታክሲ እየጠበቅኩ ነበር። ያለወትሮው አካባቢው በጊዜ ጭር አለብኝ። ታክሲ ያገኘሁት ከአንድ ሰዓት ጥበቃ በኋላ ነበር — ያውም አቆራርጬ! አራት ኪሎን ስሄድ ያው ሆነብኝ። ከዚያ እንደኔው ታክሲ የቸገረው መንገደኛ ምስጢሩን ነገረኝ —  “ዛሬ እኮ ማንቼ ደርቢ ስላለበት ነው” በማለት። ለካስ የታክሲ ሾፌሮችና ረዳቶች ኳስ ለማየት ሥራ በጊዜ እየጨረሱ ገብተው ነው። ይሄኔ ነበር አንድ ወዳጄ ሁሌም የሚናገራት ነገር ትዝ ያለችኝ፤ “ሁለት መቶ ሺሕ ብር ያለው ሰው የሚቆጣጠረው የትራንስፖርት ኢንደስትሪ”።

ግለሰቦች የየራሳቸውን ታክሲ እየገዙ እንደፈለጉ ይሠሩበታል ካልፈለጉ ሥራ ያስፈቱታል። የገዛ ንብረታቸው ስለሆነ መብታቸው ነው።  ችግሩ በዘርፉ ስርዓት ያላቸው ማኅበራት እንዲኖሩ መንግሥታዊ ማበረታቻም ሆነ ግልጽ አቅጣጫ አለመኖሩ ነው። አሊያንስ ባስ ሥራ ሲጀምር ደስ ያለኝ በዚያ ተስፋ ነው። ቢያንስ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሳቢያ አገልግሎቱ አይቋረጥም።

ስርዓቱን በየቀኑ እየተደባደቡ/እየተደበደቡ ማስከበር ይቻላል?

የአዲስ አበባ ትራፊክ ጽ/ቤት ሁሉም ታክሲዎች የሚንቀሳቀሱበትን አካባቢ ታሪፍ በይፋ እንዲለጥፉ የሚያዝ መመሪያ አለው። ባለታክሲዎቹ ግን አይተገብሩትም።

ለምሳሌ ከአራት ኪሎ አምባሳደር እና መልስ ዋጋው በመመሪያው መሰረት ዕኩል 1·35 ቢሆንም ስንመለስ ዳገት ነው በሚል ባለታክሲዎቹ 2·70 ይጠይቃሉ። አንድ ተሳፋሪ ‘የለም ዋጋው ይሄ አይደለም፣ አልከፍልም’ ካለ ያለው ዕድል ሁለት ነው፤ ወይ ወርዶ በእግር መሄድ አሊያም መደባደብ። መደባደብ ውስጥ መደብደብም አለ። ለአንድ ቀን አይደለም፣ በየቀኑ።

አንዳንዶች የተሳፋሪውን ተባብሮ አለማደም ተጠያቂ ያደርጋሉ። ስንት ዓይነት ተሳፋሪ አለ? ስንት አንገብጋቢ ጉዳይ ያለበት አለ? ዛሬ ብቻ የመጣ አለ? በየሄደበት በታክሲዎች ለማደም እየተባበረ ዕድሜና ግዜውን ሊያባክን አይችልም። ሁሉም ሰው ብዙ ኑሮ አለበት። ይህንን ስርዓት ለማስከበር ደሞዝ የሚከፈላቸው የምር፣ ለሕዝቡ በሚበጅ መልኩ ማስከበር አለባቸው።

ስርዓቱን ለማስከበር ስርዓቱ የሚፈልገውን ሟሟላትም ያስፈልጋል። በርካታ የሕዝብ ማመላለሻ አማራጮች፣ የባቡርም ይሁን አውራ ጎዳና ግንባታ/እድሳት ገድሎ የማይገድለው አማራጭ መንገድ፣… ከልብ  መታሰብ አለበት። ምክንያቱም በመሐል ቤት ዜጎች እየተጨፈለቁ ነው።

No comments:

Post a Comment