Pages

Tuesday, December 31, 2013

የአዲስ አበባ ፍተሻ ከሽብር ያተርፋል?

ሰሞኑን፣ በተለይ የዌስት ጌት ሞል ላይ በአልሻባብ ጥቃት መድረሱን ተከትሎ ጥበቃው ተጠናክሯል። በወቅቱ በድንጋጤ ሲዘነዘሩ ከነበሩ አስተያየቶች ውስጥ ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲህ ዓይነት ጥቃት የማይፈፀመው በደኅንነቱ ሥራ መጠናከር ነው የሚለው አስተያየት አመዝኖ ተደምጧል። መንግሥትም ፀረ–ሽብር እንቅስቃሴ ላይ አተኩሬ የምሠራው ይህንኑ ፈርቼ ነው የሚመስል ትንታኔ በኢቴቪ በኩል አሾልኳል።

ይሄ ሁሉ ይባል እንጂ፣ የዌስት ጌቱ ድንጋጤ አዲስ አበባን ዛሬም በፍርሐት እያራዳት ነው። በተለይም ደግሞ የእግር ኳስ ፈንጠዝያው ዕለት ራሳቸው ላይ ባርቆባቸው ሞቱ የተባሉት አሸባሪዎችና በአልሻባብ ስም በትዊተር ገፅ ፒያሳ እና ቸርችል ቦምብ ቀብረናል ብለው ያልታወቁ ሰዎች የነዙት ወሬ ድንጋጤውን አባብሰውታል። ከዚያም በኋላ ኳስ ግጥሚያዎች ባደባባይ ስክሪኖች እንዳይተላለፉ በማገድ መንግሥትም መፍራቱን አረጋግጧል።

በዚህ ድንጋጤ ወቅት ምክንያቱ በቅጡ ባይገባኝም፣ ብዙ የማኅበራዊ አውታር ተጠቃሚዎች የዚህ ዓይነቱ ጥቃት ሰለባ ይሆናል ብለው የገመቱት ኤድና ሞልን እንደሆነ በግልጽ ሲናገሩ ነበር። ምናልባትም የመዝናኛ ስፍራ ስለሆነና የውጭ ዜጎችም ስለሚበዙበት ዓይን ውስጥ ይገባል በሚል ይሆናል። ኤድና ሞልም መልዕክቱ አሳስቦት ይሁን በመንግሥት ትዕዛዝ "የተጠናከረ ፍተሻ" ጀምሯል።

በነገራችን ላይ አንድ ቀን፣ አንድ ሰው ኤድና ሞል ውስጥ በፌስታል ይዞት የገባውን ዕቃ ረስቶ በመውጣቱ ሁካታና ድንጋጤ ተከስቶ ፊልም እስከማቋረጥም ደርሶ እንደነበር ሰምቻለሁ።
የኤድና ሞል ፍተሻ የተጠናከረ ሰሞን ጥበቃዎቹን 'ያ ሁሉ አብጠርጥሮ መፈተሽ ለምን እንደሆነ' ስጠይቃቸው እዚያ የሚገቡ ኮረዶችና ጎረምሶች ሐሺሽ ይዘው እየገቡ አስቸግረዋቸው እንደሆነ ነገሩኝ። ባይዋጥልኝም ለፍተሻ መተባበሬ አልቀረም። የኤድና ሞል ፍተሻ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቶ አሁን ላፕቶፕ ይዘው የሚገቡ ሰዎች የያዙት ላፕቶፕ መሆኑን ለማረጋገጥ አብርተው ማሳየት አለባቸው።

በሌላ በኩል ጥበቃዎቹ ለሚያደርጉት ክትትል መጋነን የደኅንነት አባላት እጅ አለበት የሚል መረጃም ደርሶኛል፤ ደኅንነቶቹ፣ ፍተሻው የላላበት የሚመስላቸው ቦታ በጋዜጣ ሽጉጥ ጠቅልለው ያሳልፉና ለአስተዳደሩ ፍተሻው ደካማ መሆኑን የሚናገሩበት አጋጣሚ አለ። ስለዚህ ጥበቃዎቹ ይህ እንዳያልፋቸው ሁሉንም አብጠርጥረው በመፈተሽ ያሳልፋሉ።

ይህ ዓይነቱ ፍተሻ፣ በሁሉም ሆቴሎች፣ ሕንፃዎችና አንዳንድ ካፍቴሪያዎች ሳይቀር እየተጠናከረ ነው። መልካም ነው፤ ለደኅንነታችን ሲባል የሚደረጉትን ጥንቃቄዎች በሙሉ ቢያታክቱም በቀና መቀበል ይኖርብናል። ችግሩ፣ 'ደኅንነታችን በርግጥ በዚህ መንገድ ይጠበቃል?' የሚለው ነው።
የዌስት ጌት ጥቃትን ብንመለከት የተፈፀመው በቡድንና በተደራጀ መሣሪያ ሲሆን በኤድና ሞልና ሌሎች የሚደረጉ ፍተሻዎች ግን በሠላማዊ መንገድ፣ በነጠላ ገብተው ጥቃት ለማድረግ ያሰቡ ሰዎችን ብቻ ለማስቆም እንጂ የተደራጁ ሰዎችን ለመግታት አያስችልም።

ጎረቤታሞቹ ጁፒተርና ራዲሰን ብሉ ሆቴሎች ግን እንዲህ ዓይነቱ ወሬ የመጣ ሰሞን የፍተሻ ድንኳኖቻቸውን ከሎቢዎቻቸው ውጪ በመትከል የተሻለ አማራጭ ተከትለዋል። ይህ የተደራጀ አደጋ ከመፈጠሩ በፊት ገና ከደጅ ለመከላከል ያስችላል።

No comments:

Post a Comment