Pages

Monday, October 15, 2012

የኛ ኃይል



ዞን ዘጠኝ የተወሰደ


“ፒያሳ፤ መሐሙድጋ ጠብቂኝ” በመሐመድ ሰልማን የተጻፈ እና ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፈ ኢ-ልቦለዳዊ መጣጥፎች ስብስብ ነው፡፡ የዛሬ ዓመት ገደማ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ በተባለ መንግስታዊ ባልሆነ ድርጅት  አማካይነትመጽሐፉን የመገምገሚያ ዝግጅት አምስት ኪሎ በሚገኘው ብሔራዊ ሙዚዬም ቀርቦ ነበር፡፡ በውይይቱ መሐል የመጽሐፉ ዝነኝነት ምንጮች ምን ምን ናቸው የሚል ውይይት የነበረ ሲሆን ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ‹‹ደራሲው የአዲስ ነገር ጋዜጣ ጸሐፊ የነበረ›› መሆኑን እና ‹‹ጽሑፎቹም በአዲስ ነገር ጋዜጣ እና ድረገጽ ላይ ወጥተው የነበሩ›› መሆናቸውን ጠቀሰ፡፡ ውይይቱ የአዲስ ነገር ጋዜጣ መታሰቢያ ይመስል፣ የትዝታ ጫወታው ተጧጧፈ እናም ከውይይቱ ተሳታፊዎች አንዱ የሚከተለውን ሲናገር ረዥም ጭብጨባ አዳራሹን አደመቀው ወጣቱ አስተያየት ሰጪ በንግግሩ መሃል የተጠቀመው እና ጢም ብሎ የሞላውን አዳራሽ በጭብጨባ ያናጋው ንግግር የሚከተለው ነበር፡፡

‹‹ይህ ትውልድ በአዲስ ነገር ጋዜጣ የሚደራደር ትውልድ አይደለም፡፡››

ጉዳዩን አስገራሚ የሚደርገው ወጣቱ ይህንን የተናገረው አዲስ ነገር ጋዜጣ መታተም ካቆመች ከሁለት ዓመታት በኋላ መሆኑ ሲሆን፣ አጋጣሚው የጋዜጣዋ መንፈስ በበርካቶች ልብ ውስጥ በትኩስነት መኖሩን የሚናገር ነበር፡፡

ዛሬ፣ ጥቅምት 5/2005 የዓለም የጡመራ የተግባር ቀን (Blog Action Day 2012) “የኛ ኃይል” በሚል መሪ ቃል ይከበራል፡፡ የጡመራ የተግባር ቀን በየዓመቱ የሚከበር፣ በዓለም ዙሪያ ያሉ ጦማሪዎች በሙሉ በአንድ ሐሳብ ዙሪያ የሚጽፉበት ቀን ነው፡፡ የተጀመረው እ.ኤ.አ. በ2007 ሲሆን በተመሳሳይ  ዓመት ‹‹አካባቢ››፣ በ2008 ‹‹ድህነት››፣ በ2009 ‹‹አየር ለውጥ››፣ በ2010 ‹‹ውሃ››፣ በ2011 ‹‹ምግብ›› በሚል ሲካሄድ ዘንድሮ ደግሞ በ2012 ‹‹የእኛ ኃይል›› በሚል እየተካሄደ ይገኛል፡፡

የዘንድሮው መሪ ቃል፣ ማኅበረሰብ፣ እኩልነት፣ ፀረ-ሙስና እና ነጻነትን በተመለከተ የኛ ኃይል ምን እንደሆነ በመስበክ እንዲከበር ታስቦ የተመረጠ ነው፡፡ አከባበሩ ቀላል ነው፤ አስተባባሪዎቹ እንዳስቀመጡት ‹‹profile someone or a group who inspires you by the way they made a positive influence… (ባመጡት አዎንታዊ ተጽዕኖ ያነቃቃችሁን የሆነ ሰው ወይም ቡድን በመምረጥ ጻፉ…)›› የሚል ነው፡፡

እኛም ጮክ ብለን ስናስብበት እና በጭንቅላታችን ያቃጨለችው አዲስ ነገር ጋዜጣ ብቻ ሆነች፡፡ አዲስ ነገር ጋዜጣ ለሁለት ዓመታት (ከጥቅምት 2000 እስከ ታሕሳስ 2002) ብቻ በስርጭት የቆየች ነገር ግን መራኄ አዘጋጇ መስፍን ነጋሽ የጋዜጣዋን ሁለተኛ ዓመት አስመልክቶ እንደገለፀው ‹‹አጭር ግን ረዥም ዓመት›› የኖረች ያክል የማትረሳ ጋዜጣ ናት፡፡

አዲስ ነገር ጋዜጣ በሌጣ ግለሰብ ተፅዕኖ እና ባለቤትነት የማትመራ፣ በስድስት መሥራች አባላት የተቋቋመች እና በሕፀፅ አታች (critical analysis) ጽሁፎቿ ከፍተኛ ተወዳጅነትን እና ተነባቢነትን ለማትረፍ የበቃች፣ የአንባቢውን ቁጥር ያሳደገች፣ የጸሐፍትን ችሎታ የፈተነች (standard ያኖረች)፣ በየጊዜው በማደግ እና ተፅዕኖ በመፍጠር ላይ የነበረች ጋዜጣ ነበረች፡፡ ጋዜጣዋ በቅንጅት መፍረክረክ ሰሞን ተመስርታ በተለይም ኢሕአዴግን በሚነቅፈው ማኅበረሰብ ውስጥ የነበረው የስሜት ስብራት በመጠገን ከፍተኛ መነቃቃትን ለመፍጠር የቻለች እና በማንኛውም መለኪያ አማራጭ መገናኛ ብዙሐን የሚለውን ማዕረግ ለመቀበል የምትመጥን ናት ለማለት ያስደፍራል፡፡፡

ሃሌሉያ እና Terje S Skjerda የተባሉ የጥናት ባለሞያዎች በግል ጋዜጦች ብቃት ላይ እ.ኤ.አ. በ2009 ባደረጉት እና ሁሉንም የግል ጋዜጦች ሊባል በሚችል መልኩ በነቀፉበት ጥናታቸው ውስጥ አዲስ ነገር ጋዜጣን እንዲህ ሲሉ ነበር የጠቀሷት፡-

[To be fair,…] There are newspapers which have steered away from extremist reporting and instead try to give space for different voices. Late 2007 saw the launch of Addis Neger, a private newspaper which by 2009 has grown to become one of the two largest Amharic weeklies with a weekly circulation of 25,000-30,000 copies. Its profile is serious,balanced and critical journalism with emphasis on commentaries and in-depth stories. Within the professional limitations that exist, Addis Neger and other publications have produced valuable reporting which has challenged the government in the public sphere.

([ሚዛናዊ ለመሆን…] ከፅንፈኛ ሪፖርቶች አፈንግጠው ለተለያዩ ድምፆች ቦታ የሰጡም ጋዜጦች ነበሩ፡፡ በ2002 ከአገሪቱ ሁለት ከፍተኛ ስርጭት ያላቸው (ከ25,000-30,000 ቅጂ) ጋዜጦች መካከል አንዱ ለመሆን የበቃው የአዲስ ነገር ጋዜጣ መመስረት በ2000 አጥቢያ ታየ፡፡ ይዘቱ በአስተያየቶች እና ጥልቅ ታሪኮች ላይ ያተኮረ፣ ቁምነገር አዘል፣ ሚዛናዊ እና ሂስ አዘል ጋዜጠኝነትን የተከተለ ነበር፡፡ በነባራዊው የሙያተኞች እጥረት አዲስ ነገር እና ሌሎችም መንግስትን በሕዝባዊ ክበብ ውስጥ የሚገዳደር እሴት ፈጥረዋል፡፡)

አዲስ ነገር ጋዜጣ፣ መስራቾቿ እና ጋዜጠኞቿ በመሰደዳቸው አሁን መታተም ካቆመች ሦስት ዓመታት እየተጠጋት ነው፡፡ ሁለቱ ጋዜጠኞቿ ዐብይ ተክለማርያም እና መስፍን ነጋሽም በቅርቡ ሽብርተኝነትን በመተባበር የ8 ዓመት እስር ተፈርዶባቸው በስደት ላይ ይገኛሉ፡፡ አዲስ ነገር ጋዜጣ ላይ ይወጡ የነበሩት ጽሑፎች ግን እስካሁንም ተፅዕኗቸው አልበረደም፡፡ ዳንኤል ክብረት፣በእውቀቱ ስዩም እና መሐመድ ሰልማን የአዲስ ነገር ላይ ጽሑፋቸውን መጽሐፍ አድርገዋቸው እንደአዲስ በብዙ ሺህ ኮፒዎች ተሸጠዋል፡፡ እነሠርጸ ፍሬስብሓት በሙዚቃ ላይ፣ እነማስረሻ ማሞ በፊልም ላይ የሚጽፏቸው ሂሶች የአልበሙን እና የፊልሙን ገበያ ከመወሰንም በላይ፣ ባለሙያዎቹ ለሥራቸው እንዲጠነቀቁ፣ ለአድማጭ ተደራሹም እንዲመርጥ የሚያደርጉ ነበሩ፡፡ ዶ/ር ብርሃኔ ረዳኢ በአስቂኝ የአጻጻፍ ስልቱ የሚያቀርባቸው የሕክምና ነክ ጉዳዮች የብዙዎችን ቀልብ እንደገዙ እስከዛሬም ይታወሳሉ፡፡

የአዲስ ነገር በኢትዮጵያ ፕሬስ ላይ የፈጠረችው ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አልነበረም፡፡ እንደ አማራጭ፣ ተወዳጅ እና ተመራጭ ሚዲያ ሆኖ ከመቆየትም፣ በተጨማሪ የንባብ ባሕልን ወደ ፋሽንነት ለማምጣት እንዲሁም የወጣቱን ትውልድ ድምጽ የማሰማትም ሚና ነበራት፡፡ አዲስ ነገር ወደ ንባብ እና ወደ ቁም ነገር ያመጣቻቸው አያሌ ወጣቶች ዛሬም ከአዲስ ነገር አለመኖር በኋላም ሐሳብን በነጻነት ስለ መግለጽ ሲጨነቁ እና ሲጠበቡ ይታያሉ፡፡ በአዲስ ነገር መነሳሳት የተነሳም ወደ ጡመራ እና ውይይት የመጡ፣ ተስፋ ማድረግ የጀመሩም ቀላል አይደሉም፡፡

ከሚዲያው የሚመነጭ ጤናማ የአደባባይ ተዋስኦ በጠፋበት በፕሬሱ የጨለማ ዘመን ማግስት አዲስ ነገርን ማግኘት ለጤናማ ሕዝባዊ ውይይቶች መከፈት አስተዋጽዖ የነበረው ከመሆኑም በላይ ጋዜጣዋ መንግስትን በጠንካራ መልኩ በመተቸት ብትታማም የገዥውን ፓርቲ አቋም የሚያንጸባርቁ ቋሚ አምደኞች ነበሯት፡፡ አሁን በሥራ ላይ የሚገኙ እና ታዋቂ የሆኑ የሚዲያ ተቋማትም ቢሆኑ ራሳቸውን ሲገልጹ አዲስ ነገርን ማነጻጸሪያ ሲያደርጓት ተስተውሏል፡፡

በኢትዮጵያ የፕሬስ /ሐሳብን በነጻ የመግለጽ/ ነጻነት እያሽቆለቆለ ለመምጣቱ የአዲስ ነገር ጋዜጠኞችን እንኳን የሚያሠራ ክበብ አለመፈጠሩ ዐብይ ምስክር ነው፡፡ ዛሬ በዓለም የጡመራ ተግባር ቀን ጋዜጣዋን እና ጋዜጠኞቹን ማስታወስ ያስፈለገንም ለዚሁ ነው፡፡ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት፣ የሕዝብ ድምጽ /የሕዝብን ብሶት/ የሚያስተጋባ፣ የሕዝብን መንፈስ የሚያነቃቃ ጋዜጣ ያስፈልገናል፡፡ አዲስ ነገር ጋዜጣ የፈጠረችው እና ለመግደል የሚያስቸግር መንፈስ ቢኖር ይኸው መንፈስ ነው፡፡ ዓመታት አልፈውም “ዛሬም በአዲስ ነገር የማይደራደር ትውልድ” ለመፍጠር በቅታለችና!!!

No comments:

Post a Comment