Sunday, October 27, 2019
Abandonment of the Democratic Cause!
Monday, September 2, 2019
የእምነት ነጻነት ወይስ አስተዳደራዊ ጥያቄ?
Monday, April 22, 2019
አዲሳባን እንደ የውክልና ጦር ሜዳ…
☞ የአዲስ አበባን የውሃ ፍላጎት ይቀርፋል የተባለ ፕሮጀክት በተዋወቀ ማግስት የኦሮሚያ መንግሥት አልተማከረም ነበር ተብሎ ተሰረዘ (ምክንያቱም ጃዋር ተቃውሞል)
☞ የኮንዶሚኒየም ዕጣ ወጥቶ በኅትመት እንዳይሰራጭ የመስተዳድሩ ጋዜጣ (አዲስ ልሳን) ላይ መታተም ከተጀመረ በኋላ እንዲቋረጥ ተደረገ (ምክንያቱም ጃዋር ተቃውሟል)
***
☞ ጃዋር "ኹለት መንግሥት አለ" ብሎ ነበር፤ "ኹለተኛው መንግሥት" የተባለው ሥራ በማጣት ምሬት በሕዝባዊ አመፅ ሕይወቱን አደጋ ላይ እስከመጣል ሊደርስ የተዘጋጀ ወጣት ነው።
☞ ጃዋር "አዲስ አበባን ቀለበት ውስጥ አስገብተን" ያሻንን ማድረግ እንችላለን ብሎ ነበር፤ ለዚህም "ኹለተኛው መንግሥት የጦር መሣሪያ ነው።
ለመኾኑ ኦሮሚያን እያስተዳደረ ያለው ማነው? አዲስ አበባስ ምን ታድርግ?
ኢትዮጵያ ውስጥ 'የማንነት ጥያቄ' አለ። ግን ብቸኛው ጥያቄ አይደለም፤ መፍትሔውም ብሔርተኝነት ወይም ደግሞ ብሔረ መንግሥት (nation state) መመሥረት አይደለም። እንደውም ከችግርቹ አንዱ ይኸው ብሔርተኝነት እና ብሔረ-መንግሥት ለመመሥረት ታስቦ የሚሠራው ሥራ ነው። ይኹን እንጂ ብሔርተኝነትን በማጦዝ አንዱ ፖለቲካዊ ተፈላጊነቱን (political relevance) ለመጨመር፣ ሌላው ፖለቲካዊ ታማኝነቱን ለማረጋገጥ፣ ቀሪው ደግሞ በአጋጣሚው ሥልጣን ለመንጠቅ ወይም ለማስጠበቅ የሚያደርጉት ርብርብ ከሚበጀው ይልቅ የሚፈጀው እየበዛ ነው። እውነተኛ የሕዝብን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ማዕከል የኾነችውን አዲስ አበባ እና ነዋሪዎቿን እንደታጋች ቆጥሮ በላይዋ ላይ የውክልና (proxy) ጦርነት እየተካሔደባት ነው። በዚህ ሁሉ ትግል ውስጥ ለሥራ አጥ የኦሮሞ ወጣቶችም ይሁን ለአዲስ አበባ ነዋሪዎች ለመስዋዕትነት ከሚያማልላቸው ውጪ ችግሮቻቸውን ለመፍታት ይኼ ነው የሚባል ተስፋ የሚሰጣቸው ወገን እስካሁን የለም።
የአዲስ አበባ ተጎራባች ገበሬዎች ችግር ምንድን ነው?
የአዲስ አበባ ተጎራባች ገበሬዎች ችግር አዲስ አበባ እንደ አውራ ከተማነቷ የአገሬውን ቀልብ ሁሉ መሳቧና አለቅጥ መለጠጧ ነው። ችግሩ አለቅጥ መለጠጧ ብቻ ሳይሆን ስትለጠጥ እና የልማት አገልግሎት ስትሻ የምታፈናቅላቸው መኾኑ ነው። በተጨማሪም አዲስ አበባ ከተማ እንደመኾኗ የተጎራባቾቿን ማንነት እያቀለጠች የምትውጥ መኾኗ እሙን ነው። ይኹንና የከተሞች መስፋፋት የወደፊቱ አይቀሬ ዕጣ ፈንታ ነው። አዲስ አበባም ትሁን ሌሎቹ ከተሞች በዙሪያቸው ያሉ ገበሬዎችን እያከተሙ መዋጣቸው አይቀሬ ነው። የትኞቹም የገበሬ ቤተሰቦች ልጆቻቸው ከተሜ ቢኾኑላቸው አይጠሉም፤ የተሻለ የሕይወት ጣዕም የሚገኘው ከተማው ውስጥ ነውና። ገበሬዎቹ የሚጠሉት ከተሞቹ ሲስፋፉ እነሱንም የከተማው አካል እያደረጉ አለመስፋፋታቸውም ነው። ይኽ እንዳይሆን በኢትዮጵያ ቢያንስ ኹለት ዋና እንቅፋቶች አሉ።
አንደኛው እንቅፋት ገበሬዎችም ይሁኑ ሌሎች በመሬታቸው ላይ የመወሰን ሥልጣን የሌላቸው መኾኑ ነው፤ 'ገበሬዎች መሬት የመሸጥ የመለወጥ ሥልጣን ከተሰጣቸው ከበርቴዎች ገበሬዎቹን በገንዘብ ደልለው መሬት አልባ ያደርጓቸዋል' የሚል ሰበብ የሚሰጠው መንግሥት እና የገዢው ፓርቲ ካድሬዎች የገበሬዎቹን መሬት በሊዝና በትንንሽ ካሣ (አንዳንዴ ካሣውም ሳይከፈል ይቀራል) እያፈናቀሉ የገበሬዎቹን ቤተሰቦች መንገድ ላይ መበተናቸው አለመቅረቱ ነው። ሌላኛው እንቅፋት የፅንፈኞች ጦርነት ነው። በዚህ ጉዳይ ፅንፈኞች የምላቸው "አዲስ አበባን አካታች ማድረግ ያስፈልጋል" የሚለውን የሚቃወሙ በአንድ ወገን እና "አዲስ አበባን የአንድ ብሔረ-መንግሥት አካል" ማድረግ ያስፈልጋል በሚል እዚያ እና እዚህ ወጥረው የያዟት ፖለቲከኞች ችግር በሌላ ወገን ነው።
በሌላ በኩል፣ ፖለቲከኞቹ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የሚያገኙትን በሙሉ በሥጦታ ወይም በዝርፊያ ያገኙት በማሥመሰል ሥራ ተጠምደዋል። በዚህ ፕሮፓጋንዳም ለዒላማቸው ግብ አጎራባቾቿ ከተማዋን 'ሳቦታጅ' እንዲያደርጉ እየገፋፏቸው ነው። በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል ያሉ ግንኙነቶች በገዢና ሻጭ መካከል ያሉ 'ትራንዛክሽኖች' ናቸው። የኮዬ ፈጬ ኮንዶሚኒየም ግንባታንም ኾነ የለገዳዲ የውሃ ግድብ ግንባታን የኦሮሚያ ክልል አስተዳደር ሳያውቅ የአዲስ አበባ አስተዳደር ግንባታ ውስጥ ይገባል ብዬ አላምንም። እንደዚያም ከኾነ ችግሩ የአስተዳደሮቹ ስለኾነ አስተዳደሮቹ አለመቻላቸውን አምነው ለሚችሉ ይልቀቁ፤ አለበለዚያ የሥልጣን እና የጥቅማ ጥቅም አጀንዳቸውን ለማሳካት የከተማዋን እና አጎራባች ነዋሪዎች የግጭት ውጥረት ውስጥ መክተት አደገኛ ቁማር ስለኾነ አቁመው በነጻ ውድድር አሸናፊውን ወገን ሕዝብ የመምረጥ ዕድል ይሰጠው።
የአዲሳባ ችግር ምንድን ነው?
አዲስ አበባ ብዙ ችግሮች ሊኖሩባት ይችላሉ። ከነዚህ ችግሮቿ ውስጥ የአካታችነት ችግር አንዱ ነው ብዬ አምናለሁ። ምንም እንኳን ነዋሪዎቿ ቅይጥ በመኾናቸው እንደ ወጥ መመልከቱ (homogenizing) ስህተት ቢሆንም፥ አንዳንድ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ማኅበረሰብ ክፍሎችን እና ፖለቲካቸውን በጥርጣሬ ማየት ከጥቅል ድክመቶቿ አንዱ ነው፤ ማኅበራዊ ንቃት ላይ ብዙ መሥራት ያሻል። እንዲያም ኾኖ ግን ከሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ሁሉ የተሻለ አካታች የምትባለው ራሷ አዲስ አበባ ነች። ላልተሟላው አካታችነቷ ተጠያቂው ግን በተለያዩ የፖለቲካ ፍላጎት ሽሚያ ዒላማ ተደርጎ የታነፀው ሕዝብ አይደለም። የፖለቲካ ስርዓቶቹ ናቸው። የፖለቲካ ስርዓቶቹ አዲስ አበባ ሁሉንም ወካይ ለማድረግ ትዕምርታዊ መገለጫዎችን ማኖር፣ የኢትዮጵያውያንን የተለያዩ ባሕሎች እና ቋንቋዎችን ማስተዋወቅ እና ማበረታታት የመሣሠሉ ሥራዎችን መሥራት ነበረባቸው።
ከነዚህ ውጪ የፖለቲካ ስርዓቶቹ እና ፖለቲከኞቹ የማንነትን ጥያቄዎችን ከብሔርተኝነት ጋር በማቆራኘት የፈጠሩት ምሥል እና የተረኛ ጨቋኝነት ፍላጎት አባዜ በከተማዋ እና አጎራባቾቿ መገፋፋቱን ተባብሶ እንዲቀጥል አድርጎታል። ይሁን እንጂ በከተማዋ መስፋፋት ላይ የከተማዋ ነዋሪዎች ማድረግ የሚችሉት ምንም ነገር የለም፤ ጉዳዩ አስተዳደራዊ መፍትሔ የሚፈልግ የሥልጣኔ ሒደት ነው። ምክንያቱም ይኽ በማደግ ላይ ያሉ አገራት፣ ከተሞች ሁሉ እውነታ ነው። ለዚህም ነው ንፁኀን ነወሪዎች የፖለቲካ ውክልና ጦር ሜዳ ሰለባ መደረግ የማይኖርባቸው።
የኦሮሚያ መንግሥት ገጽታ…
እንደተናጋሪው ፍላጎት የብሔር ወይም የብዝኀ ብሔር እየተባለ የሚጠራው ፌዴራሊዝም ዘውገኝነትን ተቋማዊ በማድረጉ የሚታማ መኾኑ የአደባባይ ምስጢር ነው። ክልሎች ምንም እንኳን የብዙ ዘውግ ቡድን አባላት የሚኖሩባቸው ቢኾንም የተወሰኑ ብሔሮች ንብረት ተደርገው ነው የሚቆጠሩት። ይህ ለብሔረ መንግሥት አስተሳሰብ ቦታ ሰጥቷል። የዜጎች መንግሥት እንጂ የብሔር መንግሥት አስተሳሰብ ከዓለም እንዲጠፋ ጥረት እየተደረገ ባለበት በዚህ ጊዜ፥ በኢትዮጵያ ግን ዜጎች በተለያዩ "የብሔር" ክልሎች ውስጥ በኹለተኛ ዜግነት ማዕረግ እንዲመደቡ ተገድደዋል።
የኦሮሚያ ክልል አስተዳደር ገጽታም በዚሁ መሠረት የተገነባ ነው። በርካታ የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ ያልኾኑ ዜጎች በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ውስጥ ኦሮሞ ያልኾኑ የኢትዮጵያ ዜጎች የመንግሥት ሥራ አካላ መኾን የማይችሉበት አሠረር በክልሉ ተዘርግቷል። ይኽ ችግር የአዲስ አበባን ተጠሪነት ወደ ኦሮሚያ ለማድረግ የሚጠይቁ ኦሮሞዎችን ጥያቄ እንኳን እንደ አንድ የፖለቲካ ወይም አስተዳደር ጥያቄ ብቻ መመልከት እንዳይቻል አድርጓል። ጉዳዩ እየታየ ያለው የብሔረ መንግሥት ማነፁ ጥረት አንድ አካል ተደርጎ ነው። ስለዚህ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች (ምንም እንኳን አሁንም በቂ ወይም ቅቡልነት ያለው አስተዳደራዊ ውክልና ባይኖራቸውም) የኦሮሞ ፖለቲከኞችን ጥያቄ በጥርጣሬ የሚመለከቱበት ምክንያቶች መካከል ዋነኛው ይኸው ነው።
'ባላደራ' እስከ ምርጫ…
በጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የሚመራው የባልደራሱ ቡድን 'ብቸኛው ሕዝባዊ ውክልና ያለን [ባላደራ] እኛ ብቻ ነኝ' እያለ ነው። በዴሞክራሲያዊ መርሕ ውክልና የሚሰጠው በቂ መረጃ ባለው መራጭ፣ የተለያዩ አማራጮች ቀርበውለት፣ በነጻ እና ፍትሐዊ ምርጫ በተካሔደ የተመረጠ አካል ነው። ይኽንን የባልደራሱ ቡድን አያሟላም። ስለዚህ እኔ 'ብቸኛ' ወይም 'ወኪል' የሚሉትን ባልቀበላቸውም ግን በአሁኑ ሰዓት ከላይ በጠቀስኳቸው ምክንያቶች ሥጋት ውስጥ የገቡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ውስጥ 'ይወክሉኛል' የሚላቸው ሊኖር ይችላል የሚለውን እቀበላለሁ። ነገር ግን በመርሓችን መሠረት የታከለ ዑማ አስተዳደርም ይህንን ባያሟላም፥ 'ይወክለኛል' የሚለው የአዲስ አበባ ነዋሪም መኖሩ አይቀርም። ይልቁንም የታከለን አስተዳደር እንደ ባላደራ መቁጠሩ ሊበጅ ይችላል ብዬ አምናለሁ፤ ምክትል ከንቲባቸውም የራሳቸውን ሚና እንደዛ ቢቆጥሩ የሚበጅ ይመስለኛል።
እንደምናየው የታከለ ዑማ አስተዳደር ሊወስን የሚሞክረውን የኦሮሚያ ክልል እያስቆመው ነው። ኾኖም አዲስ አበባን የመወከል ሕጋዊ ኀላፊነት አንፃራዊ የተሻለ ተቀባይነት ያላቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ተሰጥቶታል። ስለሆነም ይህንን ኀላፊነት 'እንደ ባላደራነት' በመጠቀም የከተማዋ ነዋሪዎች "በርግጥም ይወክለኛል"፣ "እኔን ወክሎ ይከራከርልኛል" የሚሉትን አስተዳደር እንዲመርጡ መራጮች በቂ መረጃ አግኝተው የሚካሔድ ነጻ እና ርትዓዊ ምርጫ እንዲዘጋጅ ኹኔታዎችን ያመቻቹ። ምርጫ ቦርድም ይኽንን ለማስፈፀም ታጥቆ ይነሳ። የባልደራሱ ቡድንም ከዚህ የተለየ የሚጠይቀው ነገር ያለ አይመስለኝም።
Monday, February 11, 2019
ለውጡ እና የመገናኛ ብዙኃን ጉዳይ
Tuesday, January 22, 2019
ስድስቱ የኅትመት ብዙኃን መገናኛዎቻችን ፈተናዎች
Thursday, November 15, 2018
Understanding Privileges
Saturday, November 10, 2018
ምርጫ፦ ቄሮ ‘መንግሥት’ ይሁን ‘ፅንፈኛ’?
በቄሮ ምንነት እና "ድርጊቶች" ላይ በርካታ ውዝግቦች እየተነሱ ነው። ውዝግቦቹ የሚነሱት በሁለት ፅንፎች ነው፦ ፩ኛው ፅንፍ ያሉት ሰዎች "ቄሮ ቅዱስ ነው" ሲሉ፣ ፪ኛው ፅንፍ ያሉት ሰዎች ደግሞ "ቄሮ እርኩስ ነው" ይላሉ። እኔ ደግሞ ቄሮ እኛ ነህ የምንለውን ይሆናል ባይ ነኝ።
እንደኔ እንደኔ የውዝግቡ ሁሉ መንስዔ የቄሮን ምንነት እና የንቅናቄውን ዓይነት፣ እንዲሁም "የትግሉን" ወይም ደግሞ "የድሉን" ባለቤት ካለመረዳት የመጣ ነገር ይሆን ይሆናል በማለት ነው ይህንን ጽሑፍ ለአማራጭ አስረጅነት ያዘጋጀሁት። እግረመንገዴንም ለውዝግቡም ይሁን ለውዝግቡ መንስዔ የሆኑ ተቃርኖዎችን እዳስሳለሁ። ዓላማዬ ከፅንፉ እና ከፅንፉ ወዲህ ዓለም እንዳለ ለማሳየት እንጂ መሞከር ብቻ ሳይሆን ፍረጃችን ተፅዕኖ እንዳለው ማስታወስም ጭምር ነው።
ቄሮ - ሥያሜው ምን ይነግረናል?
'ቄሮ' ቃሉ 'ያላገባ፣ ያልወለደ' ወጣትን ይወክላል። ነገር ግን ወጣት የሚለውን ቃል የሚተኩ ሌሎች የኦሮምኛ ቃላት አሉ። እነዚህም 'ደርደሩማ'፣ 'ደርገጌሳ' እና 'ጎሮምሳ' የሚሉት ቃላት ምሳሌ ይሆናሉ። ቄሮ የሚለው ቃል ምንጩ 'ቄረንሳ' ከሚለው እና ነብር የሚል ትርጉም ካለው ቃል የተቀዳ እንደሆነ ይነገራል። ስለዚህ ቄሮ ማለት እንደነብር ያለ ብርቱ ወጣት ማለት ነው፣ ማለት እንችላለን። ይሁን እንጂ አሁን በተለይ በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ 'ቄሮ የሚለው ቃል ፍቺ 'አብዮተኛ ወጣት' የሚል ትርጉም አለው።
"የቄሮ ንቅናቄ" ውልደት እና ዕድገት
ቄሮ የሚለው ቃል የፖለቲካ መድረኩ ውስጥ የገባው እ.ኤ.አ. በ2011 የአረቡ አብዮት በፈነዳበት ወቅት ነበር። መቀመጫውን ዳያስፖራ ያደረገው ንቅናቄ ከዩንቨርስቲ ተማሪዎች ጋር ግንኙነት በመመሥረት 'ቄሮ ቢሊሱማ ኦሮሞ' የሚባል ኢመደበኛ ማኅበር ፈጠረ። የዚህ ማኅበር አባላት መረጃዎችን በኢሜይል እና በድረገጻቸው እየተለዋወጡ በርካታ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ ቀጠሉ። ሥማቸው በይፋ የተነሳው ግን በ2006 የአዲስ አበባ ከተማ ማስተር ፕላንን ተከትሎ በተነሳው እና ዩኒቨርስቲዎችን ባዳረሰው የተቃውሞ ሰልፍ ወቅት ነው።
ከዚያ በኋላ የተጋጋለው የተቃውሞ ሰልፍ መላው ኦሮሚያን ሲያዳርስ በየአካባቢው ያሉ ወጣቶች ራሳቸውን ቄሮ ብለው መጥራት ጀመሩ። የመጀመሪያው የቄሮ አደራጅ የነበረው (qeerroo.org የተባለ) ድረአምባም ይሁን የፌስቡክ ገጹ አሁን እምብዛም ተከታታይ የላቸውም። ይልቁንም የወጣቶቹ ኅብረት መሪ ተደርጎ በዘልማድ የሚወሰደው የኦኤምኤን ቴሌቪዥን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጃዋር መሐመድ ነው።
ከዚያ በኋላ በኦሮሚያ ክልል፣ በየአካባቢው የሚነሱት ተቃውሞዎች ውስጥ የሚሳተፉ የተደራጁም ይሁኑ ያልተደራጁ ወጣቶች በሙሉ - ራሳቸውን ሲገልጹም ይሁን ሌሎች ሲገልጿቸው - ቄሮ በሚል ሥያሜ ሆነ። ቄሮ በዚህ አካሔድ በማንም ግለሰብ ወይም ቡድን ቁጥጥር ሥር ያልሆነ፣ ነጻ ነገር ግን በኦሮሙማ (ኦሮሞነት) የተሰባሰበ ኢመደበኛ ቡድን ሆነ። ይህ ማለት ግን ወጣቶቹ በፖለቲካ ፍልስፈፍናቸውም ይሁን ብስለታቸው፣ በኢትዮጵያ እና ኦሮሚያ ታሪክም ይሁን ፖለቲካ አረዳዳቸው ወጥ አቋም አላቸው ማለት አይደለም።
ይህ በእንዲህ እያለ በአማራ ክልል የነበረው ሕዝባዊ ተቃውሞ ላይ የሚሳተፉትን ወጣቶች ሥም ለመስጠት ተሞከረ። 'ፋኖ' የሚለው ሥያሜ 'ቄሮ' ከሚለው ጎን ለጎን መጠቀሱ የተለመደ ነገር ሆነ። ያን ጊዜ በቄሮ ሥምም ሆነ በፋኖ ሥም የሚደረገው ነገር በሙሉ፣ ማዕከላዊ መንግሥቱን እስካስጨነቀ ድረስ "ትክክል" ነበር። ይሁን እንጂ መሬት ላይ "ቄሮ ነኝ" የሚሉትን ያክል፥ "ፋኖ ነኝ" የሚሉ ወጣቶች እምብዛም አልነበሩም። እንዲያውም 'ፋኖ' የግንቦት ሰባት ፈጠራ ነው የሚሉ የአማራ ብሔርተኞች ገጥመውኛል። ይሁንና የመንግሥት ባለሥልጣናት ሳይቀሩ አሁን ለምናየው የለውጥ አዝማሚያ አስተዋፅዖ ያበረከቱ ወጣቶችን ሲጠሩ "ቄሮ፣ ፋኖ፣ ዘርማ…" እያሉ መጥራትን 'ፕሮቶኮል' አድርገውታል።
የትግሉ እንዲሁም የድሉ "ባለቤቶች"
የያኔዎቹ ኦሕዴድ እና ብአዴን ተባብሮ ትሕነግ ላይ ማበይ፥ ከወጣቶቹ አመፅ ባልተናነሰ (ወይም በበለጠ መልኩ) ኢሕአዴግን ነቀነቀው። የፓርቲዎቹ ከወጣቶቹ ጋር ያልተጻፈ መግባባት ላይ መድረስ ደግሞ የቀድሞውን ኢሕአዴግን ገድሎ፣ አዲሱን ኢሕአዴግ ወለደ። አሁን ከትሕነግ/ኢሕአዴግ ወደ ኦዴፓ/አዴፓ/ኢሕአዴግ አገዛዝ ተሸጋግረናል። ይሁንና ገና አመፁ አልሰከነም። የትግሉ ባለቤት ተቃዋሚዎች በሙሉ፣ በተለይም አደባባይ የወጡት የኢትዮጵያ ወጣት አመፀኞች ናቸው፤ የድሉ ባለቤቶች ግን የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች፣ በተለይም ኦዴፓ እና አዴፓ ናቸው። ያለእነሱ ከቀድሞ አቋማቸው መቀልበስ፣ እንዲሁም ለማበር መወሰን በኢሕአዴግ ቤት አሁን ያለው ወደ ዴሞክራሲ የመሸጋገር ዕድል ፈፅሞ አይመጣም ነበር ብዬ እገምታለሁ።
ይሁንና ወጣቶቹ የልኂቃን ተቃዋሚዎችን ጥያቄ ከማስተጋባት ባሻገር ለእንዲህ ያለ ነፍስን አሳልፎ እስከመስጠት የሚደርስ ብሶት የዳረጋቸው ሥራ አጥነት እና 'የሪከግኒሽን' ጥያቄ መልስ ቢሰጠው ኖሮ፥ ድሉን የጋራ ድል አድርገን መቁጠር የምንችልበት ዕድል ይኖር ነበር።
አሁን ባለው ሁኔታ ብዙኃን ሥራ አጦች በየአደባባዩ በከፈሉት መስዋዕትነት፥ 'እነዚህ ሥራ ፈቶች ደግሞ መረበሽ ጀመሩ' እያሉ ይበሳጩባቸው የነበሩ ልኂቃን በአንድ በኩል፣ እንዲሁም በሌላ በኩል ደግሞ 'እስከመቼ እንዲህ ተዋርዳችሁ ትኖራላችሁ፣ ታግላችሁ ነጻ ውጡ እንጂ' እያሉ ሲቆሰቁሷቸው የነበሩ ልኂቃን ሥልጣን እየተቆጣጠሩ ሲመጡ ወጣቶቹ ችላ መባላቸው ሐቅ ነው።
ይህ ነገር ምናልባትም የትግሉ "ባለቤቶች" እና የድሉ "ባለቤቶች" ወይም "ተጠቃሚዎች" መካከል መቃቃር ሳያስከትል አይቀርም። ይህ ጉዳይ አዲስ ብሶት የሚወልድ መሆኑም የጊዜ ጉዳይ ነው።
"ጀግኖች" የነበሩ "ፅንፈኞች"
(የውክልና ጦርነት መሣሪያዎች)
በየአካባቢው በሥራ አጥነታቸው ምክንያት ዋጋ አጥተው፣ በአደገኛ ቦዘኔነት ተፈርጀው ከፊሉ ስደት እየበላቸው፣ ከፊሉ ሱስ እየዋጣቸው የነበሩ ወጣቶች ድንገት የተቀጣጠለው ሕዝባዊ አመፅ ማገዶ ነበሩ። ያኔ "ጀግኖች" ተብለዋል። ምክንያቱም ለልኂቃኑ ፖለቲካ ሁነኛ መሣሪያ ነበሩ። ወጣቶቹ ምናልባትም አእምሮ ከሚያላሽቅ የሥራ አጥነት ስሜት ወጥተው፥ ለራሳቸው ያላቸው ዋጋ እና ግምት የጨመረው በዚህ አመፅ ባደረጉት ተሳትፎ ይሆናል። ሕዝባዊ አመፁ ቆሞ ድንገት አገር መረጋጋት ሲጀምር ግን ወደ "መንደር ያሰለቹ አደገኛ ቦዘኔነት" መመለሳቸው ሆነ። ከተሰጣቸው ሥም መውረድ ከባድ ነው። ስለሆነም የአብዮታቸው ጠባቂ ሆኑ - ከሳሽ፣ ፈራጅ እና ቀጪ። የደቦ ፍርድ፤ በዚህ ወቅት ነው በፅንፈኝነት መፈረጅ የጀመሩት።
በዕውቁ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የምትመራው 'ኢትዮጲስ' ጋዜጣ (በጥቅምት 24, 2011 እትሟ) በርዕሰ አንቀፅዋ ቄሮዎችን ለዘብተኛ እና ፅንፈኛ በሚል ከለያየቻቸው በኋላ ፅንፈኞቹን የማስቆም ሥራ መሠራት እንደሚገባ ጠቁማለች። የኢትዮጲስ ስህተት ምናልባት (አንድም) በአገሪቱ የደቦ ፍርዶች እና ወደ ስርዓት አልበኝነት የሚወስዱ እንቅስቃሴዎችን ለቄሮ ብቻ ለይታ መስጠቷ ነው። መቼም በድንጋይ ወግሮ መግደል እና በእንጨት ላይ ዘቅዝቆ መስቀልን የመሳሰሉ የደቦ ፍርዶች አንዱ ከሌላው የሚሻሉበት መንገድ አለ ተብሎ አይታመንም። በዚህ ረገድ ጉዳዩ 'ወጣት ፅንፈኞች' በሚል ሊጠቃለል ይችል ነበር ብዬ አምናለሁ። (ሁለትም) ቄሮ የተጻፈ ፕሮግራም የሌለው፣ አባላቱ በዝርዝር የማይታወቁ፣ አንድ ስትራቴጂ እና ግብ የሌለው የግፉአን ማኅበር መሆኑን ከግምት ውስጥ ያላስገባ መደምደሚያ መሆኑ ስህተት ያደርገዋል። ይህም ማለት ማንም ተነስቶ ቄሮ ነኝ ብሎ ማወጅ እና በዚያ ሥም ወንጀልም ይሁን መልካም ጀብዱ መፈፀም ያስችለዋል ማለት ነው። ብዙኃን መገናኛዎች ግን ቡድኑን ግልጽ ቅርፅ እና መዋቅር እንዳለው እንዲሁም "ተግባሩን" አቅዶ እንደፈፀመ ማኅበር ተመልክቶ "እንዲህ ነው" ወይም "እንዲያ ነው" ማለት የተሳሳተ ትርጉም ይሰጣል። (ሦስትም) የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች - ለምሳሌ የጃዋር "የቄሮ መንግሥት" እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ "ፀጉረ ልውጦችን መቆጣጠር" የመሳሰሉ - ንግግሮች ወጣቶቹን የውክልና ጦርነት ውስጥ እንደከተታቸው ከግንዛቤ ያላስገባ መደምደሚያ መሆኑ ነው።
ፍረጃ እና ተፅዕኖው፤
እስመ ሥሙ ይመርሖ ሀበ ግብሩ
(nomen est omen)
ቄሮንም ይሁን ፋኖን ወይም ሌላ የፖለቲካ ቡድኖችን በተመለከተ ለምናደርጋቸው ፍረጃዎች ማድረግ የሚገባን ጥንቃቄ አለ። ፍረጃ (labeling) በሥነ-ልቦና ግንባታ የሚያሳድረው ተፅዕኖ እንዳለ በርካታ ጥናቶች ያሳያሉ። «እነ እከሌ ይህን አያደርጉም»፣ «እንትን ሆኜ እንዲህ አላደርግም» የሚሉ አባባሎች የሚያስረዱን ቁምነገር ቢኖር የሆኑ ሰዎች ስብስብን የሚገልጽ ማንነትን የምንበይንበት (labeling/defining) መንገድ መልሶ የአባላቱን ድርጊት እንደሚወስን መረዳት እንደሚያሻን ነው። "ቄሮ አብዮተኛ ወጣት ነው" በተባለ ጊዜ አደባባዮችን በተቃውሞ ሰልፎች ንጧል። የለውጥ ጀምበር ሲከፈት "ለውጡን ጠብቁ" ሲባል እንደዚያው ለማድረግ እየሞከረ ነው። ወጣቶቹ በልኂቃኑ የሚሰጣቸውን ሥያሜ ለመመጠን እየተፍጨረጨሩ ነው። "ቄሮ መንግሥት ነው" ብለን ከአቅሙ በላይ ሥራ ከምናሸክመው፣ "ቄሮ የዴሞክራሲ እና የሥልጡን ፖለቲካ ጠበቃ ነው" ብለን በዚህ አቅጣጫ እንዲተጋ ብናደርገው ይመረጣል። "ቄሮ ፅንፈኛ ነው" እያልን ወደዚያ ከምንገፋው "ቄሮ ይህንን አያደርግም" ብለን ብንገስፀው ይሻላል።
ቺርስ ለጥንቃቄ!
The Return to Rule by Law: The Case of Draft CSO Law in Ethiopia
(Befekadu Hailu) [The original version of this piece is written in Amharic; please read the Amharic version for accuracy.] The Ministry...

-
(በፍቃዱ ኃይሉ) ይህን መጣጥፍ ያዘጋጀሁት እያስጴድ ተስፋዬ “ ምክረ-ሀሳብ ለረጋ ፖለቲካዊ ስርአት ” በሚል ላቀረበው ጽሑፍ መጋቢ መልስ ይሆን ዘንድ ነው። በቅድሚያ እያስጴድ ጊዜ ወስዶ እና አሰላስሎ “የተረ...
-
(በፍቃዱ ኃይሉ) አዲስ አበባ ውስጥ ውንብድና ጨምሯል። ይህንን የምለው እንዲሁ በልምድ “ዛሬ ከትላንት ይከፋል” በሚል ዲስኩር ተጠልፌ አይደለም። በራሴ ደርሶ ስላየሁት ነው፤ ያውም በአንድ ዓመት ርቀት ውስጥ ሁለት ጊዜ...
-
( በፍቃዱ ዘ . ኃይሉ ) አምባገነናዊ ስርዓቶች ግለሰብ፣ ፓርቲ፣ መንግሥት እና አገርን ለዜጎቻቸው እንደማይነጣጠሉ አስመስለው ያቀርባሉ። ግለሰቡን ከነካችሁ ፓርቲው ይፈርሳል፣ ፓርቲውን ከነካችሁ፣...