Friday, October 28, 2011

“ይህ - የታገልንለትን ጉዳይ አለማወቅ ነው”

ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያም በአንድ ወቅት በፈፀሙት ድርጊት ተፀፅተው ይቅርታ ይጠይቁ እንደሁ በገነት ‹ማስታወሻ› ላይ ሲጠየቁ ‹‹ማንን ነው ይቅርታ የምጠይቀው? ወያኔን? ወያኔ እኔን ይቅርታ ጠይቆኛል?...ይህ የታገልንለትን ጉዳይ አለማወቅ ነው›› በማለት ጥያቄውን በጥያቄ መልሰዋል፡፡ መንግስቱ በአስተዳደራቸው ማክተሚያ ሰሞንም፣ በመንግስት መገናኛ ብዙሐን እንዲህ ብለው ነበር፡፡ ‹‹ለአገሬና ለወገኔ ይበጃል ብዬ ባደረግኩትና በተሳተፍኩባቸው ተግባሮች ሁሉ በግሌ ሕሊናዬን የሚወቅሰኝ ነገር የለም›› ብለዋል፡፡

‹‹መ››ንግስቱ እና ‹‹መ››ለስ
መለስ በመንግስቱ ቆብ ውስጥ ገብተው ይሆን?

በመጀመሪያ የስልጣን ዘመናቸው ዲሞክራት  መስለውን ነበር::
እኛን ብቻ ሳይሆን ምዕራባውያንንም በዚህ ሸውደዋቸዋል::
ምዕራብውያን ታዛዥነታቸውን ስለሚወዱላቸው ብቻ ተቀብለዋቸዋል::
የመለስ ታዛዥነት ለውጭ ኃይሎች ብቻ እንጂ ለአገራቸው ሕዝብ
አይደለም::  መለስ በውጭ ዲፕሎማሲ ጎበዝ የሚመስሉዋችሁ ከሆነ -
አይደሉም:: ሊደራደሩበት የሄዱትን ጉዳይ አሳልፈው በመስጠት
መስማማትን ይመርጣሉ::  ውጪያዊ ተቃውሞ የማይደመጥባቸውም
ለዚያ ነው::

በዴሞክራሲ ጉዳይ "ሙጋቤ የሚለው አፍሪካውያን የምዕራባውያን
ዓይነት ዴሞክራሲ  አያስፈልጋቸውም::" ብሎ ነው ብለው መለስ
ከጋዜጠኛ ጋር ከተሟገቱ በኋላ የዴሞክራሲ  በኢትዮጵያ ተስፋው
ተመናምኗል:: ሙጋቤ  መንግስቱን አስጠልለዋል - አሁን ደግሞ
መለስም  የርሳቸውን የዴሞክራሲ ቲዎሪ እየዘመሩ ነው::
መንግስቱና መለስ እያደር የሚያመሳስላቸው ነገር ተበራክቷል፡፡ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ነጋሶ ጊዳዳ ‹‹የነጋሶ መንገድ›› በተሰኘው ግለታሪካቸው እንደነገሩን የሕወሓት ተገንጣይ ቡድን ተሸንፎ ሲወጣ የነመለስ ቡድን (በተለይ አቶ መለስ) ‹‹ጃኬታቸውን አስወልቀን ሸኘናቸው›› እያሉ ሲፎክሩ ነጋሶ መለስን ‹‹መንግስቱን፣ መንግስቱን መሰልከኝ›› ብለዋቸዋል፡፡ እውነት ነው፤ (መ)ንግስቱና (መ)ለስ (መ)ንትያ ናቸው፡፡ እስኪ በዝርዝር እንመልከተው…

Tuesday, October 25, 2011

“አሰብ የማን ናት?”ን በጨረፍታ


በ260 ገጾች ተቀንብቦ የተጻፈው የዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም ‹‹አሰብ የማን ናት?›› ዶ/ሩን የሚያስመሰግን፣ ኢትዮጵያውያንን የሚያነቃቃ ነው፡፡ መጽሃፉን እያነበብኩ እያለሁ ይሰማኝ የነበረው ስሜት በመዳን ላይ ያለ ቁስል ዳርዳሩን ሲያኩት የሚሰጠውን ዓይነት ስሜት ነበር፡፡ (የምታውቁት ካላችሁ)

የመጽሃፉ መግቢያ፣ የመጀመሪያው አንቀጽ ‹‹ኢትዮጵያውያን በተለያዩ የታሪክ ወቅቶች በአገር ውስጥ ብቅ ያሉ አምባገነን መሪዎች የጫኑባቸውን በደሎች ሰው ሰራሽም ሆኑ ተፈጥሮ የወለደቻቸውን ችግሮች በትዕግስት ያስተናገዱ ሲሆን፤ ኢትዮጵያውያን በትዕግሰት የማይመለከቱት ነገር ቢኖር የድንበር መደፈርን ነው ማለት ይቻላል፡፡›› ይላል፡፡

የመጽሃፉ ዓላማ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አሰብ የኢትዮጵያ መሆኗን አውቆ የባሕር በራችንን ማስመለስ ብሔራዊ ግዴታችን እንደሆነ ለማስታወስ መጣር መሆኑም በመግቢያው ላይ ተገልጧል፡፡

Thursday, October 20, 2011

“ደረሰኝ ሳይቀበሉ፥ ሒሳብ አይክፈሉ”

ሰሞኑን ጉምሩክ ከሚሰሩ ሰዎች የሰማሁት ዜና የተለመደ ዓይነት ቢሆንም፥ እንደተለመደው ከመገረም አልዳንኩም፡፡ ጉምሩክ የላካቸው አሥር ጥንዶች አሥር ስጋ ቤቶች ውስጥ ገብተው ቁርጥ እና ጥብሳቸውን ከበሉ በኋላ ከአሥሩ ስጋ ነጋዴዎች አንዱ ብቻ ደረሰኝ ሲያቀርብ ቀሪዎቹ ዘጠኙ ያለደረሰኝ ሒሳብ በመቀበል ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ስታትስቲክስ ውሸታም ነው ቢባልም፣ በዚህ ስሌት እኮ 90 በመቶ የሚሆኑት የሥጋ ነጋዴዎች ታክስ ያጭበረብራሉ ማለት ነው፡፡

ይህንን ዜና ስትሰሙ ለማን አዘናችሁ፣ ወይም በማን አዘናችሁ? ነጋዴዎቹ ምነው ቀድመው መረጃ ቢያገኙ ወይም ምን ዓይነት መንግስት ነው ያለው ብላችሁ ከተማረራችሁ፥ ለፍርድ የቸኮላችሁ ይመስለኛል፡፡ ነጋዴዎቹስ ቢሆኑ ለሕጉ ለምን አይገዙም?

በኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ያልተመለሱ ሕዝባዊና መንግስታዊ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ሁሉም በእኩል ደረጃ አሳሳቢዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ችግሮች ውስጥ አንዱ የሕግ የበላይነት ጉዳይ ነው፡፡ እኔ እንደማስበው በሕግ የበላይነት ጉዳይ ሁላችንም እንስማማለን፡፡ ልዩነታችን በአተገባበሩ ላይ ነው፡፡ ሌላው በዚሁ ማዕቀፍ ውስጥ ያለው ጥያቄ የሕግ የበላይነት ከማን የሚለው ነው - ከሕዝቡ፣ ከመንግስት ወይስ ከሁለቱም?

Tuesday, October 11, 2011

ኢትዮጵያውያን ለምን ዲቪ አይሞሉ?

ባለፈው ዓመት በዚህ ሰሞን ዲቪ ለኢትዮጵያውያን ስሞታ ይስ ስጦታ? የሚል መጣጥፍ ጽፌ ነበር፡፡ በዚያ ጽሁፍ ብዙ ወጣት ኢትዮጵያውያን ልባቸው ከሃገራቸው ውጪ ነው በማለት በማሕበረሰቡ የቁም ቅዠት፣ በአገሪቱ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁኔታ ፈርጄ ‹‹ኢትዮጵያውያንን እንደበረሃ አሸዋ ከተበተኑበት የሚሰበስባቸው ማን/ምን ይሆን?›› የሚል ጥያቄ አስፍሬ ነበር የደመደምኩት፡፡

የስደት እና የዲቪ ጉዳይ ዛሬም ስላላባራ (በቅርቡ የሚያቧራም ስለማይመስል) በዚህ ሐሳብ ዙሪያ አሁንም እንድጽፍ የሚጎተጉተኝ ስሜት አላጣሁም፡፡ በዚያኛው ጽሁፍ ኢትዮጵያውያን ለምን ይሰደዳሉ ብልም ከዓመት በኋላ ተገቢ ሁኖ ያገኘሁት ጥያቄ ግን ‘ለምን አይሰደዱ?’ የሚለውን ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን ለምን ይሰደዳሉ ለሚለው ጥያቄ በርካታ መልሶችን በቀላሉ ማግኘት ይቻላል፡፡ ዋና፣ ዋናዎቹ ምክንያቶች ኢኮኖሚያዊ ቀውስ፣ ፖለቲካዊ ነፃነት ማጣትና የተሻለ ትምህርት ፍለጋ ናቸው፡፡ ከተማሩ በኋላ መመለስ ልምድ ባይሆንም፡፡ (አወይ የዋህነት! ከተማሩ በኋላ መመለስ ቀርቶ፤ ለሴሚናር፣ ለዎርክሾፕ፣ ለዘገባ ወይም ለጉብኝት ሄዶ መመለስስ የታለና?!)

Friday, October 7, 2011

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና አንዳንድ አካላት


የዕድገትና የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ አንድ ዓመቱን ጨርሷል፡፡ ኢትዮጵያ እንደተጠበቀው በዓመት ከ11 እስከ 15 በመቶ የማደግ ሕልሟን አሳካች ወይስ ችግር አለ? በቅርቡ የምንሰማው ይሆናል፡፡ በርግጥ ‹‹ከዕቅዱ በታች ፈፅሞ የማያውቀው መንግስታችን›› ዘንድሮም የሁለት ዲጂት እንደሚያስመዘግብ መጠራጠር ከአሸባሪነት ያልተናነሰ ሃጢያት ነው የሚሆነው፡፡

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና UNECA
ስለትራንስፎርሜሽኑ የመጀመሪያ የስኬት ዓመት ከሰሞኑ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀብድ ቢጤ መስጠት ጀማምሯል፡፡ ሰሞኑን የምዕራባውያን ኢኮኖሚ እየፈረሰ ለቻይናዎች እጁን መስጠቱን የሚያትት ወሬ ካወሩልን በኋላ እንደ UNECA የአገሪቱ ዳይሬክተር ከሆነ ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት 10 በመቶ ታድጋለች፡፡ የUNECA ባለስልጣን እንዲህ ለማለት ከደፈሩ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንማ ኢትዮጵያን በሦስት ዲጂትም ሊያሳድጋት ይችላል የሚል ሐሳብ ያዘኝና ተውኩት፤ ምክንያቱም UNECA የሚጠቀምበት መረጃ ለካስ ከኢትዮጵያ መንግስት የተገኘ ነው፡፡

የትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድና መለስ ዜናዊ

Friday, September 30, 2011

የአፋልጉኝ ማስታወቂያ ለተቃዋሚዎች


መጀመሪያ ጭብጨባ

አንድነት ፓርቲ በቅርቡ ተቃዋሚዎች/የተቃዋሚ ደጋፊዎች በቂ የመረጃ ምንጭ የላቸውም በማለት በየሣምንቱ ማክሰኞ፣ በ5 ብር ገበያ ላይ የምትውል ‹‹ፍኖተ ነፃነት›› የተሰኘች ጋዜጣ ማሳተም ጀምሯል፡፡ አንዱአለም አራጌ ሲናገር እንደሰማሁት ‹‹በጋዜጣዋ ላይ የኢሕአዴግ ደጋፊና አባላትም ቢሆኑ መጻፍ ይፈቀድላቸዋል፤ አንድነት እንደ ኢሕአዴግ የመናገር ነፃነትን የማፈን ፍላጎት የለውም፡፡››

ከዚህ በተጨማሪም ፓርቲው በየሣምንቱ እሁድ ማለዳ በተጋባዥ ምሁራን ጽሁፍ አቅራቢነትና በተሳታፊዎች መካከል የሚካሔድ የውይይት ፕሮግራም ጀምሮ ነበር፡፡ (የእነ አቶ አንዱአለም በ‹‹አሸባሪነት›› ተጠርጥሮ መታሰር ይህንን ጠቃሚ ልምድ እስከወዲያኛው ያስቀረው ይሆን?)

በሌላ በኩል (የኔ favorite ባይሆንም እንኳን) ኢዴፓ የዓለም ሊበራል ፓርቲዎችን ጉባኤ በ2004ዓ.ም. በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ሊያካሒድ ጎንበስ ቀና እያለ መሆኑ የሚያስመሰግን ነው፡፡ እንዲህ ሰበብ እየፈለግን የምናቆለጳጵሳቸው ተቃዋሚዎች ግን በደመስማሳው ስንመለከታቸው መንግስት አንድ ውሳኔ ባሳለፈ ቁጥር የፕሮፓጋንዳ መግለጫ ከመስጠት ባሻገር (ያውም ከሰጡ) ባለፈው ምርጫ ካየናቸው በኋላ የት እንደገቡ ጠፍተዋል፡፡

Thursday, September 22, 2011

ሞክሮ መሳሳት እና ከስህተት መማር


እስኪ የዛሬውን ወጋችንን ብዙ በተደመጠ ቀልድ እንጀምረው፡፡ አንዲት ተማሪ ለፈተና ተቀምጣለች፡፡ ጥያቄዎቹን አየቻቸው ‹እውነት› ወይም ‹ሐሰት› ነው መልሳቸው፡፡ ምንም ባለማጥናቷ የቱ እውነት፣ የቱ ሐሰት እንደሆነ አታውቅም፡፡ የመጣላት አማራጭ ሳንቲም ከኪሷ አውጥታ ‹አንበሳ› ሲሆን ‹እውነት›፣ ተቃራኒ ሲሆን ደግሞ ‹ሐሰት› እያለች መመለስ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ፈተናዋን ሰርታ ስትጨርስ በጣም ብዙ ጊዜ ተረፋት ስለዚህ የሰራችው ትክክል መሆን አለመሆኑን ለማረጋገጥ ፈለገች፡፡ ግን ደግሞ ማረጋገጫ መንገድ የላትም፤ ስለዚህ በጀመረችው መንገድ እንደገና ሳንቲም እየወረወረች አንበሳን ለእውነት፣ ጀርባውን ለሐሰት እየመደበች መልሷን ታረጋግጥ ጀመር፡፡

በእንዲህ ዓይነቱ ፈተና ውስጥ ሁለት መልስ ብቻ በመኖሩ፥ ያለሳንቲምም ቢሆን ሞክሮ መሳሳት፣ ሞክሮ ለመማር ነው፡፡ (በፈረንጅ አፍ Trial and Error Learning ይባላል፡፡ በአማርኛ ልተረጉመው ፈልጌ ነበር፤ ከበደኝ እንጂ! ‹ሞክሮ በመሳሳት መማር› ብለው ትክክል ነው እንዴ?) ግን ደግሞ በሕይወት ዓለም እልፍ መንገዶች አሉ፤ የትኛው መጨረሻው እንደሚያምር ለማወቅ ወይ በሁሉም መንገዶች ተራ፣ በተራ መሄድ አሊያም [ወደኋላ የምንመካከርበትን ጉዳይ ማድረግ] ያስፈልጋል፡፡ በሁሉም መንገዶች እየሄድን መጨረሻቸውን እንይ እንዳንል ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ ከችግሮቹ አንዱ፡- ለሙከራ የጀመርነው መንገድ መጨረሻው ባያምርስ? እሺ፡- መጨረሻው ሰላም ሆኖ መድረሻውን ስላልወደድነው ብቻ መመለስ ብንፈልግ የምንመለሰው እንዴት ነው? ከሁሉም የሚያሳዝነው ግን ሁሉንም መንገዶች ለመሞከሪያ በቂ ጊዜ የለንም፤ ሕይወት አጭር ናት፡፡

ዓላማቸው ግልጽ ባልሆነ የሐሳብ ድሪቶዎች ይህንን ያህል ካደከምኳችሁ ይበቃል፡፡ የዚህን ጽሁፍ ዓላማ ለማብራራት ግን አሁንም አንድ አንቀፅ ያስፈልገኛል፡፡ ከሰው ጋር ተግባብቶ ለመኖር እየሞከሩ፣ መሳሳት፤ እየተሳሳቱ፣ መማር ይቻል ይሆናል፡፡ በሰዎች ዕጣ ፈንታ ለመወሰን ግን እየሞከሩ መሳሳት፣ እየተሳሳቱ መታረም አይቻልም፡፡ ዕጣ ፈንታ መዳረሻ በመሆኑ ማጣፊያ (undo) የለውም፡፡ በሃገራችን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚወጡ መመሪያዎች እና ውጤታቸው ግራ ቢያጋቡኝ ይህንን መጻፍ ጀመርኩ፡፡

The Return to Rule by Law: The Case of Draft CSO Law in Ethiopia

(Befekadu Hailu) [The original version of this piece is written in Amharic; please read the Amharic version for accuracy.] The Ministry...