Pages

Sunday, October 15, 2017

የባንዲራ ማኒፌስቶ!

ልጅ እያለን፣ ታላላቆቻችን እኛን እርስበርስ እያደባደቡ ሲዝናኑብን እንዲህ ያደርጉ ነበር። ምራቃቸውን መሬት ላይ ሁለት ቦታ ላይ እንትፍ እንትፍ ይሉና፣ "ይቺኛዋ ያንተ እናት፣ ያቺኛዋ ደግሞ ያንተ እናት ናት" ይሉናል። ከዚያም "ማነው የማንን እናት የሚረግጠው?" ሲሉ፣ አንዱ ቀድሞ የሌላኛውን "እናት" (በትፋት የራሰውን አፈር) ከረገጠ ድብድቡ ይጀመራል። የተተፋበትን አፈር የረገጠውን ልጅ ዝም ማለት፣ እናትን አስረግጦ ዝም እንደማለት ነበር የሚቆጠረው። የውርደት፣ የሽንፈት ስሜት አለው። በልጅነት ዐሳባችን የእናታችንን ትዕምርታዊ መገለጫ ማስደፈር እናታችንን ከማስደፈር ዕኩል ስለሚሰማን ወትሮ ከማንደፍረው ሰው ጋር ሳይቀር እንጋጫለን።

የባንዲራ ትዕምርትም እንደዚሁ ነው። ሰንደቅ ዓላማ የአገርና የአገራዊ ፖለቲካ አስተሳሰብ ትዕምርት (‘ሲምቦል’) ነው። ሁለት አገራት ወደጠብ ሲገቡ በሕዝባዊ ተቃውሞ ሰልፎች ላይ ባንዲራ ማቃጠል፣ በፊት በፊት ፋሽን ነበር። አሁንም ድረስ ባንዲራ የማቃጠል ተቃውሞ አለ።

የባንዲራ ትዕምርታዊነት ሰፊ በመሆኑ ቬክሲሎሎጂ የሚል የጥናት ዘርፍ ተቋቁሞለታል። በባንዲራ መከባበርም፣ መናናቅም ይገለጻል። ሕዝባዊ ሐዘን ይገለጽበታል። ደስታ ይበሰርበታል። የአገር ፍቅር ልክ ይመዘንበታል።

“ከብሔራዊ የሰንደቅ ዓላማ ቀን” ባሻገር!

አቶ መለስ "ባንዲራ ጨርቅ ነው” ብለው ሲናገሩ የሳቱት ጉዳይ ይህንን ትዕምርታዊ ውክልናውን ነው። በርግጥ ይህንን አሉ በተባለበት ወቅት አገሪቱ ከአንድ ይፋዊ ሰንደቅ ዓላማ ወደ በርካታ ባንዲራዎች እየተሸጋገረች ስለነበር፣ "ባንዲራ ጨርቅ" ብቻ ከሆነ ያንን ሁሉ ለውጥ ለምን ማድረግ እንዳስፈለጋቸው መጠየቅ ነበረባቸው። አቶ መለስ ይህንን ብዙ ሕዝብ የሚያስከፋ ‘የአፍ ወለምታ’ የባንዲራ ቀን እንዲከበር በማድረግ ነው ለማረም የሞከሩት። የመጀመሪያውን ክብረ በዓልም ራሳቸው ባንዲራ እየሰቀሉ ነው ያስጀመሩት። ነገር ግን ንግግራቸው እስከዛሬም በአሉታዊ ሚና ይጠቀስባቸዋል።

ይህ በእንዲህ እያለ - ባንዲራ በኢትዮጵያ፣ በፊት በፊት የአንድነት መገለጫ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ማንፀባረቂያ (ማኒፌስቶ) ሆኗል። በኢትዮጵያውያን የሚውለበለቡት የባንዲራዎች ብዛት የፖለቲካ አመለካከታችንን ያክላል። ልሙጡ አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ እንዲሁም ባለኮከቡ። አልፎ አልፎ ባለ ‘ሞኣ አንበሳውም’ አለ። የገዳው ጥቁር፣ ቀይና ነጭ፣ እንዲሁም የኦሮሚያ ክልሉ ጥቁር፣ ነጭና እና ቀይ (መሐሉ ላይ ዛፍ)። የኦነጉም ባንዲራ አለ። እነዚህ አነታራኪዎቹ ናቸው።

በኢትዮጵያ በ2003 የተሻሻለው የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ አዋጅ ከወጣ ወዲህ (ሌሎቹ ባይጠቀሱም) ቢያንስ ‘ኮከብ የሌለውን’ ባንዲራ ማውለብለብ ተከልክሏል (ለብሶ መታየትን ግን የሚከለክል ሕግ አላየሁም። ቢሆንም አገር ውስጥ ከላይ የጠቀስኳቸውን ባንዲራዎች ይዞ ወይም ለብሶ መገኘት ለቅጣት ወይም እንግልት ይዳርጋል።) ነገር ግን በዳያስፖራ  የተቃውሞ ሰልፎች ላይ እንደየሰልፉ ዓይነት - በተለይ ሁለቱ (‘የኦነግ’ የሚባለውና ልሙጡ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ) ባንዲራዎች የማይቀሩ ናቸው። አሁን አሁን፣ በተለይ የኦሮሚያና የአማራ ክልል መንግሥታት ከሕወሓት ጋር ትከሻ መለካካት ጀምረዋል ከተባለ በኋላ ሕዝባዊ ሠልፎች ላይ ሕጋዊ ዕውቅና የሌላቸውን ባንዲራዎችን ማውለብለብ እዚህም ተለምዷል።

እንደምን በአንድ ባንዲራ እንኳ መስማማት ተሳነን?


፩) አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀዩ ባንዲራ ጳውሎስ ኞኞ ከዘመናዊቷ ኢትዮጵያ አመሠራረት ጋር በዳግማዊ ምኒልክ ግዜ ነው የተጀመረው ቢልም ከዚያ በፊትም ነበረ ብለው የሚከራከሩ አሉ። የንጉሣዊ ስርዓቱ መለያ ‘የሞኣ አንበሳው’ ምስል ግን ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ አገዛዝ ጋር በተያያዘ ነው በብዙዎች የሚታወቀው። ራስ ተፈሪያን ናቸው ከኛ የበለጠ የሚያውለበልቡት ቢባል ማጋነን አይሆንም። ሦስቱ ቀለማት ግን ከቅኝ ግዛት የወጡ አገራት ሳይቀሩ በሞዴልነት የወሰዱት በመሆኑ ‘የነጻነት አርማ’ ነው የሚሉ አሉ። በዚህ አገዛዝ የተጨመረው ኮከብ፣ እንደ ሕገ መንግሥቱ አንቀፅ 3 አባባል የኢትዮጵያ ብሔር፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦችና ሃይማኖቶች “በዕኩልነት እና በአንድነት ለመኖር ያላቸውን ተስፋ የሚያንፀባርቅ ይሆናል”። ነገር ግን ይሆናል የተባለው አልሆነም። ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ዜጎች ባንዲራው ላይ ኮከብ ማየት ያበሳጫቸዋል። በዚህ ባንዲራ እና ላዩ ላይ በሚያርፈው ምልክት ብቻ አውለብላቢዎቹ በሦስት ዋና፣ ዋና ቡድኖች ይከፈላሉ። ባለ ኮከቦቹ - ራሳቸውን የፌዴራል ሥርዓቱ ደጋፊ ሲያደርጉ፣ ተቃዋሚዎቻቸው የኢሕአዴግ ደጋፊ አድርገው ይስሏቸዋል። ልሙጡን አውለብላቢዎቹ ራሳቸውን የኢትዮጵያ አንድነት አቀንቃኝ አድርገው ሲቆጥሩ፣ ተቃዋሚዎቻቸው የፌዴራል ስርዓቱ ተቃዋሚ ያደርጓቸዋል። ባለሞኣ አንበሳዎቹ ራሳቸውን የኢትዮጵያን ታሪክ አክባሪ አድርገው ሲስሉ፣ ተቃዋሚዎቻቸው ያለፈው ስርዓት ናፋቂ አድርገው ይስሏቸዋል። (እዚህ ላይ ባለማወቅ ያገኙትን የሚያውለበልቡት አይጠቀሱም።)

ብዙ አገራት፣ የአገረ መንግሥቱን አርማ ባንዲራ ላይ ማስፈር የመንግሥቱ ሥራ ቢሆንም ዜጎች ግን አርማ የሌለበትን ባንዲራ ያውለበልባሉ። ይህም የዜጎች ባንዲራ (civil flag) ይባላል። የአገረ መንግሥቱ አርማ የሌለበትን ባንዲራ ማውለብለብ ለዜጎች ወታደራዊ ወይም መንግሥታዊ አካል አለመሆናቸውን (ወይም ‘ሲቪል’ መሆናቸውን) የሚገልጹበት መንገድ ስለሆነ ቢያንስ በሕግ ደረጃ መከልከል አልነበረበትም።

፪) በኦሮሚያ ሕዝባዊ ሰልፎች ላይ የኢትዮጵያ ባንዲራ ሲውለበለብ ማየት የተለመደ አይደለም። ይልቁንም የገዳው፣ የክልሉ እና የኦነጉ ባንዲራዎች ናቸው የሚታዩት። የኦነግ የሚባለው አግድም ቀይ፣ አረንጓዴና ቀይ ሆኖ መሐሉ ላይ በቢጫ መደብ አረንጓዴ ዛፍ ያለው ነው። ሆኖም ከዛፉ በስተቀር ባንዲራው ከኦነግ ምሥረታ ይቀድማል የሚሉ አሉ። አሁን ኦነግ በተከፋፈለበት እና በተዳከመበት ሁኔታ፣ ባንዲራው ግን በብዙዎቹ የኦሮሞ ተወላጆች የተወደደ ነው። እንዲያውም ባንዲራው "የተቋቁሞ" (resistance) አርማ እንጂ የኦነግ ባንዲራ አይደለም ብለው የሚከራከሩ የመብት አራማጆች አሉ። የሆነ ሆኖ፣ ይህንን ባንዲራ በኢትዮጵያ ምድር ላይ ሲያውለበልቡ (ወይም እንዲሁ ይዞ መገኘት) በሽብር ያስከስሳል። (እዚህ ጋር የፌዴራል ስርዓቱን የሚቀበሉት ብዙ ኦሮሞዎች ባለ ኮከቡ ባንዲራ ለምን ብዙም ደንታ እንደማይሰጣቸው ግልጽ አይደለም።) ሌላው ግልጽ ያልሆነው ምክንያት የኦሮሚያ ምክር ቤት ለምን በገዳው ባንዲራ (ጥቁር፣ ቀይና ነጭ) ምትክ ጥቁር፣ ነጭና ቀይ ባንዲራ ለክልሉ እንደመረጠ ነው። የገዳ ባንዲራ የሚባለው አባ ሙዳዎች (?) ራሳቸው ላይ የሚጠመጥሙት ሻሽ መልክ ሲሆን፣ በትውፊት ‘ጥቁር ሰማይ/አምላክ፣ ቀይ (ሕይወትን፣ ደምን)፣ እና ነጭ (ሙት መሬትን) ይወክላል በሚል ነው ይባላል።

የሆነ ሆኖ ከነዚህ የባንዲራ ልዩነቶች በመነሳትም፣ አውለብላቢዎቹ የሚያራምዱትን ፖለቲካዊ ማኒፌስቶ በሦስት መፈረጅ ተለምዷል። ‘የኦነጉ’ ባንዲራ አውለብላቢዎች ራሳቸው በማንነታቸው የሚደረግባቸውን ተፅዕኖ የመቋቋሚያ አርማ አድርገው ሲስሉት፣ ተቃዋሚዎቻቸው የተገንጣይ አስተሳሰብ አራማጅ ያደርጓቸዋል። የገዳ ባንዲራን አውለብላቢዎች ራሳቸውን የኦሕዴድ ተቃዋሚ ነገር ግን የኦሮሙማ (ኦሮሞነት) አራማጅ አድርገው ሲስሉ ተቃዋሚዎቻቸው አንዳንዴ ከኦሕዴድ፣ ሌላ ግዜ ከኦነግ ደጋፊ ጋር ያመሳስሏቸዋል። የኦሮሚያ ክልል ባንዲራን የሚያውለበልቡት ራሳቸውን ከገዳ ስርዓቱም፣ ከኦሕዴድ ስርዓቱም ጋር ማስማማት የሚፈልጉት ዓይነት ናቸው፤ ተቃዋሚዎቻቸው ግን የኦሕዴድ ደጋፊ አድርገው ነው የሚስሏቸው። (እዚህም ላይ ባለማወቅ ያገኙትን የሚያውለበልቡት አይጠቀሱም።)

፫) በጣም የሚገርሙት የአማራ እና የትግራይ ክልል  ሰንደቅ ዓላማዎች ናቸው። ሁለቱም ጥቂት ልዩነት ነው ያላቸው። የያዙት ቀለም ቀይና ቢጫ ሲሆን ኮከብ አላቸው። ይሁን እንጂ ታሪካዊ አመጣጡ ከማርክሲስት ሌኒኒስት ርዕዮተ ዓለማቸው ከመፍለቁ በቀር፣ ከክልሎቹ ሕዝቦች ትውፊት ጋር የሚያገናኘው ነገር ምን እንደሆነ አይገባኝም። ሁለቱ ክልሎች ለአረንጓዴ፣ ቢጫና ቀዩ ባንዲራ የተለየ ታሪካዊ ቅርበት ቢኖራቸውም፣ የክልሎቹ ባንዲራዎች እና ይህንን ያወረሷቸው ፓርቲዎች ባንዲራ ግን ከዚህ የራቀ ነው። ከነርሱ ይልቅ የኦሕዴድ (የፓርቲው) እና የኦነግ ፓርቲዎች ባንዲራዎች ለኢትዮጵያ ባንዲራ - አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ቀለም ይዘት አላቸው።

፬) በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሥልጣን ፍትጊያ ውስጥ ሁሌም ተጠቃሾቹ ሦስቱ - ኦሮሞ፣ አማራ እና ትግራይ ናቸው። ልክ እንደዛ የትኛው ባንዲራ ተውለበለበ የሚለው ጉዳይ የሚያጨቃጭቃቸውም እነዚሁኑ ሦስቱን ነው። በተለይም ደግሞ ሁለቱን (ኦሮሞ እና አማራ)። ሌሎቹ ክልሎች ግን የማዕከላዊ መንግሥቱን ውሳኔ ከማፅደቅ በላይ እምብዛም አቅምም፣ ፍላጎትም የሌላቸው ይመስላሉ (ቢያንስ በባንዲራው ጉዳይ)።

የባንዲራ-ፍቅር (ቬክሲሎፊል) ልዩነቱ (በባንዲራ ዓይነትም፣ በአፍቅሮት መጠንም) እየሰፋ በመጣ ቁጥር፣ የተለያዩ የመፍትሔ ሐሳቦች መወርወራቸው አልቀረም። ከነዚህ ሐሳቦች ውስጥ፣ (ሀ) መንግሥታዊ ተቋማት ይፋዊውን እንዲጠቀሙ፣ ዜጎች ግን የፈለጉትን እንዲያውለበልቡ እንዲፈቀድላቸው የሚጠቁሙ፤ (ለ) በተለይ የኦሮሚያ እና የአማራ ክልሎች ሕዝቦች የሚወዱትን ባንዲራ መርጠው እንዲጠቀሙ ማድረግ የሚሉ አሉ። ሁለቱንም የመፍትሔ ሐሳቦችንም የሚቃወሙ አሉ። ነገር ግን የባንዲራ ትዕምርታዊነት ባለበት ዓለም በባንዲራ መስማማት አለመቻል ትልቅ ፖለቲካዊ ቅሌት ነው። ይህንን በአዋጅ በመከልከል፣ በማስገደድ እና በብሔራዊ ቀን በማደናገር አደባብሶ ማለፍ አይቻልም።

“ኧረ በባንዲራው!”

ባንዲራ የሚከበረው ከባዲራው በላይ የሆነን ነገር ስለሚገልጽ ነው። “ለባንዲራ መዋደቅ” ለአገር (ሕዝብ) ከመዋደቅ ዕኩል ተደርጎ ነው የሚወሰደው። ነገር ግን አሁን አሁን “ኧረ በባንዲራው!” ሲባል፣ “በየትኛው ባንዲራ?” ማለት ያለብን እየመሰለ ነው። በፊት በፊት አትሌቶቻችን ውጪ ሲወዳደሩ ወይም የእግር ኳስ ቡድናችን በሰው ሜዳ ሲጫወት፣ የሚውለበለበው አንድ ዓይነት ባንዲራ ነበር። ዛሬ ዛሬ ግን አንድ የኛን አገር ወክሎ የወጣን ቡድን ብዙ የተለያዩ ባንዲራዎችን የያዙ ቲፎዞዎች ሲያውለበልቡለት እያየን ነው። የትኞቹም የባንዲራ አውለብላቢዎች ግን ቡድኖቹን የራሳቸው ማድረግ ቢፈልጉም፣ በባንዲራ ምርጫቸው ግን ሊስማሙ ፈቃደኛ አይደሉም። ይህ የአገር ውስጥ ገመናችን ዓለምዐቀፍ አደባባይ ላይ የወጣበት አጋጣሚ ነው። እናም፣ በጣም ግራ ያጋባል። በባንዲራ ያልታረቁ ሕዝቦች በምንድን ነው የሚታረቁት? መከልከል ይሻላል ወይስ መፍቀድ? የባንዲራ ፍቅር ለስርዓተ ማኅበሩ ፍቅር ሳይኖር ይመጣል? የባንዲራ አንድነቱ ይቀድማል ወይስ የፖለቲካ ስምምነቱ?

No comments:

Post a Comment